በሀዋሳ ከተማ የባህል ስፖርት ይካሄዳል
አዲስ አበባ ግንቦት 7/2006 ዘጠኝ ክልሎችና ሁለት ከተማ አስተዳደሮች ተሳታፊ የሚሆኑበት 12ኛው የባህል ስፖርት ውድድር በሀዋሳ ከተማ እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ ባህል ስፖርት ፌዴሬሽን አስታወቀ፡፡
ውድድሩ ''የህብረተሰቡን ተስፋና ተጠቃሚነትን በባህል ስፖርት ይጎለብታል'' በሚል መሪ ቃል ከግንቦት 10 እስከ ግንቦት 20 እንደሚካሄድ የባህል ስፖርት ሀላፊ አቶ ቢቃሙ ብሩ ተናግረዋል።
አቶ ቢቃሙ እንዳሉት የውድድሩ አላማ ህብረተሰቡን የራሱን ባህል የሚያሳድግበት ፣ የሚያስተዋውቅበት ፣ ባህልና ወግ እርስ በርስ የሚወራረስበት እና የህዝቡን ቅርርብ የሚያጠናክርበት ነው።
ውድድሩ በዘጠኝ የስፖርት አይነት ይካሄዳል ያሉት ኃላፊው የገና ጨዋታ ፣ትግል ፣ ኩርቦ ፣ ገበጣ ባለ 12 ጉድጓድና ባለ 18 ፣ቡብ ፣ሻህ ፣ የፈረስ ጉግስና የፈረስ ሸርጥ የስፖርት ዓይነቶች መሆናቸው ገልጸዋል።
ወንዶች በሁሉም የስፖርት ውድድር ዓይነቶች ተካፋይ እንደሚሆን አስታውቀው ሴቶች ግን ከገና ጨዋታ ውጭ በስምንቱ እንደሚሳተፉ አስረድተዋል።
ክልሎች በቂ ዝግጅት ባለ ማድረጋቸው ምክንያት በቀስትና በሀርቤ ስፖርቶች ዘንድሮ በውድድሩ ላይ አለመካተታቸውን ኃላፊው ገልጸዋል።
11ኛው የባህል ስፖርት ውድድር በትግራይ ክልል መቀሌ ከተማ መካሄዱን ይታወሳል።
ምንጭ፦ ኢዜኣ
Comments
Post a Comment