ሲዳማ እና የጫት ምርቷ

በሪፖርተራችን በጥቻ ወራና የቀረበ

የሲዳማ ጫት ገበያ እንደተለመደው ዘንድሮም ሞቅ ያለ ነው። እንደምታወቀው በተለይ በበጋ ወራት የጫት ገበያው ሞቅታ ከፍተኛ ይሆናል ምክንያቱ በበጋ ወራት የጫት ምርት ኣነስተኛ ስለምሆን ነው። በተቃራኒው በክረምት የጫት ምርት ከፍተኛ ስለምሆን እና ኣብዛኛዎቹ የጫት ኣምራቾች ምርታቸውን በገፍ ይዘው ወደ ገበያ ስለሚወጡ የጫት ዋጋ ይቀንሳል።
የሲዳማ ጫት ምርት በመላው ኣገሪቷ ተፋላጊነቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ በመምጣቱ የተነሳ የሲዳማ ኣርሶ ኣደሮች ሌሎች ለምግብነት የምሆኑ የእርሻ ምርቶችን ማምረት ትተው ማሳቸውን በጫት በመሸፈን ላይ ናቸው። በኣሁኑ ጊዜ በሲዳማ ውስጥ 60 ከመቶ የምሆነው መሬት በጫት በመያዝ ላይ ነው ብባል ውሽት ኣይደለም፤ ምክንያቱም ኣነሰም በዛም በ21ዱም የሲዳማ ወረዳዎች ውስጥ ጫት ይመረታልና።

በጣም የምገርመው ከዚህ በፊት በቡና ምርቱ ይታወቅ የነበረው የኣለታ ጩኮ ወረዳ በኣሁኑ ጊዜ በኣብዛኛው የእርሻ መሬት የጫት የተያዘ ነው። በሲዳማ ውስጥ ባሉት ከዚህ በፊት ጫት በማይመረትባቸው ኣሮሬሳን የመሳሰሉ ወረዳዎችን ጨምሮ በሁሉም ወረዳዎች ጫት በመረቱ ከጫት የምገኘው ገቢ ከሌላው የእርሻ ምርት ከምገኘው ገቢ በላይ በመሆኑ በመሆኑን መገመት ኣያስቸግርም። ለዚህም ይመሰላል ሲዳማ ውስጥ የቡና ተክል እየቆረጡ ጫት እየተከሉ ያሉ ኣርሳ ኣደሮች ቁጥር እየተበራከተ መምጣቱ።

ሲዳማ ለምግብነት የሚሆን ምርት ማምረት ኣለበት ወይስ ካሽ ክሮፕ ወይም የተሻለ ገቢ የሚያስገኙ እንደጫት ኣይነት ምርቶችን ማምረት ኣለበት በምለው ዙሪያ ብዙ ኣከራካሪ ጉዳዮች ልኖሩ ይችላሉ፤ ከዚህም ባሻገር ሰው በገዛ ማሳው የሚያዋጣውን ምርት የማምረት መብት ሰላሌው ክርክር ውስጥ ኣንገባም።

ሲዳማ ውስጥ በርካታ ኣይነት ጫት ይመረታል፤ ኣብዛኛዎቹ የሲዳማ ጫት የተለያየ ስም ያላቸው ሲሆን ስማቸውን የምያገኑት ከምመረቱባቸው ኣካባቢዎች ነው። ለኣብነትም በመላው ኣገሪቱ በከፍተኛ ደረጃ ተፈላጊ የሆነው በለጨ ጫት ስሙን ያገኘው በወንዶ ገነት ወረዳ ውስጥ ከምትገኘው ይህንን ጫት ከምታመርተው በለጨ ከምትባል ቀበሌ ነው።


በርግጥ ከላይ እንደተነሳው የተለያዩ የጫት ኣይነቶች የተለያየ ስያሜዎችን መጀመሪያ መመረት ከጀመሩበት ኣከባቢ የምወስዱ በመሆኑ በሌሎች ኣከባቢዎችን ስመረቱ በመጀመሪያው ስማቸው መጠራታቸውን ይቀጥላሉ። ለምሳሌ ያህል የወንዶ ገነቱ በለጨ ጫት ከሃዋሳ በ15 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው የቱላ ከተማ ኣከባቢ በብዛት ይመረታል፤ ነገር ግን የስም ለውጥ ኣልተረገበትም።

ለማንኛው በሲዳማ ውስጥ የምመረቱ የጫት ኣይነቶ የምከተሉት ናቸው፦ በለጨ፤ ጫንጌ፤ ዳራራ፤ ባሌላ፤ ሲቄ፤ ሞኮኒሳ፤ ኖሌ፤ ሌምቦ፤ ዱሜ፤ ሺሻ እና ሌሎች ይገኙበታል።


በገፊ እየተመረተና እና በየጊዜው ምርቱ እየጨመረ ያለው የሲዳማ የጫት ምርት ለሲዳማ ኢኮኖሚ ያለው ጠቀሜታ ቀላል ኣይደለም፤ በርግጥ ለዚህ ጽሁፍ ሲባል በኣጠቃላይ ከጫት የምገኘውን ገቢ በዞን ደረጃ የምያሳይ መረጃ ባይኖርም ኣምራቹም ብሎም መንግስት ከጫት ምርቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን ግን ኣይካድም። የሲዳማ ጫት ኣምራች ወረዳዎች የጫት ምርታቸውን ለኣገር ውስጥ ገበያ የምቀርበው በሁለት ተከፍሎ ነው።



ለዚህ ጽሁፍ ሲባል ሰሜን ሲዳማ ጫት ኣምራች ወረዳዎች እና ደቡብ ምስራቅ ሲዳማ ጫት ኣምራች ወረዳዎች በማለት ለሁለት መክፈል ይቻላል። ሰሜን ሲዳማ ጫት ኣምራች ወረዳዎች ወንዶ ገነት ወሻ እና ቱላ የገበያ ማዕከል በማድረግ በብዙ ሚሊዮን ብር የምገመት የጫት ገበያ የሚያካህዱ ሲሆኑ፤ የጫት ምርቱ ከጎርቼ፤ ዳሌ፤ ሎካ ኣባያ፤ ባካሶ፤ ሻቤዲኖ፤ ሃዋሳ ዙሪያ፤ ወንዶ ገነት፤ መልጋ፤ ዶሬ ባፋና እና ባርቻ ወረዳዎች ይመጣል። ስርጭቱን ስናይ በነዚህ ማለትም በወንዶ ነገት እና በቱላ የጫት ገበያ ማዕከላት የምሰበሰበው የጫት ምርት በኣብዛኛው ሃዋሳ እና ከሃዋሳ በስተሰሜን ባሉ ከተሞች ኣዲስ ኣበባን ማዕከል ኣድርገው ይሰራጫል።


ከደቡብ ምስራቅ ሲዳማ ጫት ኣምራች ወረዳዎች ማለትም ከኣለታ ወንዶ፤ ኣለታ ጩኮ፤ ዳራ፤ ሁላ፤ቦና፤ ባንሳ እና ኣሮሬሳ ወረዳዎች የምመጣው ጫት ልክ እንደ ሰሜን ሲዳማ የጫት ገበያ ማዕከላት የሌሉት ሲሆን፤ በሁለት መስመር ለብሄራዊ ገበያ ይቀርባሉ። ኣንደኛው መስመር የቦረና ክብረመንግስት መስመር ሲሆን ሌላውና ሁለተኛው መስመር ደግሞ ዲላ ሞያሌ መስመር ነው።

የሲዳማ ጫት ምርት በገፍ ለብሄራዊ ገበያ የምያቀርቡ በርካታ ግለሰቦች እና ድርጅቶች ያሉ ቢሆንም፤ እስከኣሁን ድረስ ባለው መረጃ መሰረት የሲዳማን ጫት ኤክስፖርት በማድረግ ለኣለም ገበያ የሚያቀርብ የሲዳማ ድርጅት ግን የለም።

የሲዳማ ጫት ኣምራቾች ምርቶቻቸውን በተበታተነ መልኩ ለገበያ ማቅረባቸው ልያገኘ የምገባውን ገቢ የቀነሰባቸው ሲሆን፤ ነጋዴዎቹ ደግሞ በመንግስት በጫት ላይ የተጣለው ቀረጥ ኣላፈናፊን ብሏቸዋል። ጥቻ ወራና ያናገራቸው የጫት ነጋዴዎች እንደምሉት ከሆነ ለኣንድ ኪሎ ጫት ሰባት ብር ቀረጥ በመክፈል ላይ ናቸው።


ከሲዳማ የጫት ምርት የምገኘው ገቢ በተቀኛጄ መልኩ ለዞን ኢኮኖሚያዊ ግንባታ እንድውል እና የጫት ኣምራች ሲዳማውያን ኢኮኖሚያዊ ህይወት በማሻሻል ረገድ ጠቀሜታ እንዲኖረው የዞኑ መንግስት የጫት ገበያ ማዕከላትን በመገንባት እና ለጫት ኣምራቾች በገንዘብ ኣያያዝ እና ኣጠቃቀም ዙሪያ የኣቅም ግንባታ ስልጠናዎችን ቢያመቻች መልካም ነው። 

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር