ባለስልጣኑ የዕቅዱን ከ20 በመቶ በላይ ብልጫ ያለው ገቢ ሰበሰበ

አዋሳ ሚያዝያ 08/2005 ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከተለያዩ የገቢ ምንጮች ከዕቅዱ ከ20 በመቶ በላይ ብልጫ ያለው ግብር በማሰባሰብ የከተማውን አጠቃላይ ወጪ መሸፈን መቻሉን የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ባለስልጣን ገለጸ፡፡ በንግድ ስራ የተሰማሩ ሁሉም ድርጅቶች የሽያጭ መመዝገቢያ መሳሪያ መጠቀም እንዳለባቸው አስጠንቅቋል፡፡ የባለስልጣኑ ስራ አስኪያጅ አቶ ፍቃዱ ፍስሐ ሰሞኑን ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እንደገለጹት ከሐምሌ 2004 ወዲህ ባሉት ዘጠኝ ወራት ከ385 ሚሊዮን ብር የሚበልጥ ገቢ ተሰባስቧል፡፡ የመደበኛና ማዘጋጃ ቤት አገልግሎትን ጨምሮ ቀጥታና ቀጥታ ካልሆነ እንዲሁም ታክስ ካልሆኑ ገቢዎች የተሰበሰበው የገቢ ግብር የዕቅዱን ከ20 በመቶ በላይና ካለፈው አመት ተመሳሳይ ጊዜ በከፍተኛ ደረጃ ብልጫ እንዳለው ገልጸዋል፡፡ ከዕቅድ በላይ ማከናወን የተቻለው በከተማ አስተዳደርና በስሩ በሚገኙ ስምንቱ ክፍለ ከተሞች አመራሩና ሰራተኛው ከሙስናና ኪራይ ሰብሳቢነት የጸዳ አሰራር እንዲከተሉ የተጠናከረ ክትትልና ቁጥጥር በመዘርጋት ለግብር ከፋዩ ህብረተሰብ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት መሰጠርት ግልጽ፣ ፈጣንና ተጠያቂነት የሰፈነበት ስርዓት እንዲኖር በመደረጉ ነው ብለዋል፡፡ የሀዋሳ ከተማ ሰፊ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ የሚካሄድበትና ከዚህ የሚመነጨውን የገቢ ግብር አቅም አሟጦ ለመጠቀም በተደረገ ጥረት አፈጻጸሙ ከምንግዜውም የተሻለ ጥሩና አመርቂ ደረጃ ላይ መድረሱን ስራ አስኪያጁ አስረድተዋል፡፡ በዚህ ገቢ የከተማው አስተዳደር ከመንግስት ይደረግለት የነበረውን ድጎማ በማስቀረት ለካፒታል ፕሮጀክቶችና ሰራተኛ ደመወዝና ስራ ማስኬጃን ጨምሮ የከተማውን አጠቃላይ ወጪ በራሱ ለመሸፈን መቻሉን ገልጸዋል፡፡ የከተማው አሰተዳደር የገቢ ግብር በየአመቱ እየጨመረ ባለፈው በጀት አመት 250 ሚሊዮን ብር በማሰባሰብ መደበኛና ካፒታል ወጪን መሸፈን መቻሉን አመልከተው ዘንድሮም ለማሰባሰብ የታቀደውን 429 ሚሊዮን ብር በማሰካት የወጪ ፍላጎትን ለማሟላት እንደሚቻል ገልጸዋል፡፡ በከተማው 11ሺህ የደረጃ ሀ፣ ለ እና ሐ ግብር ከፋዮች እንዳሉም ገልጸዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የሽያጭ መመዝገቢያ መሳሪያ ያላቸው ነጋዴዎች 1ሺህ 177 ብቻ መሆኑን ስራ አስኪያጁ አመልክተው መሳሪያ መጠቀም ለመንግስት ብቻ ሳይሆን ለነጋዴው የሚበጅ በመሆኑ ሁሉም የንግድ ድርጅቶች መሳሪያውን ገዝተው የመጠቀም ህጋዊ ግዴታ እንዳለባቸውና ይህንን በማያድረጉ ላይ ህጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድ አስጠንቀቀዋል፡፡ ከከተማው ግብር ከፋይ ነጋዴዎች መካከል አንዳንዶቹ በሰጡት አስተያየት የገቢ ግብር ሰብሳቢ መስሪያ ቤት የሚሰጣቸው አገልግሎት ከቀድሞ የተሻለ ቢሆንም አሁንም አልፎ አልፎ የቢሮክራሲ ውጣ ውረዶች በመኖሩ መታረም እንዳለባቸው አስታውቀዋል፡፡http://www.ena.gov.et/Story.aspx?ID=7086&K=1

Comments

Popular posts from this blog

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር