በቡና አላላክ ላይ የወጣው አወዛጋቢ መመርያ ተሻረ
ንግድ ሚኒስቴር ከህዳር 1 ቀን 2004 ዓ.ም. ጀምሮ ሌላ የተለየ ፈቃድ ከሚኒስቴሩ ካልተሰጠ በስተቀር የኢትዮጵያ ቡና በብትን በኮንቴይነር እንዲላክ ያወጣውን አወዛጋቢ መመርያ ማንሳቱን አስታወቀ፡፡ መመርያው ተግባራዊ እንዲሆን በተወሰነ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ነው የተሻረው፡፡ የንግድ ሚኒስትሩ አቶ ከበደ ጫኔ ባለፈው ሐሙስ የኢትዮጵያ ቡና ላኪዎች ማኅበር የቦርድ አባላትን ሰብስበው ካነጋገሩ በኋላ፣ ቡና በብትን ብቻ ይላክ የሚለው መመርያ ተቀልብሶ በጆንያና በብትን መላክ እንደሚቻል መፈቀዱን ነግረዋቸዋል፡፡ ቡና ላኪዎቹ በበኩላቸው ምንም እንኳ በብትን መላኩ በሚያስገኘው ጠቀሜታ ላይ ጥያቄ ባይኖራቸውም፣ ገዢዎች እስኪቀበሉትና ፍላጎት ኖሯቸው በብትን መቀበል መፈለጋቸውን እስኪያስታውቅ፣ ለብትን አላላክ ሥርዓት የሚያስፈልጉ መሠረተ ልማቶች እስኪሟሉ ድረስ ግን በብትንም በጆንያም መላክ ሊፈቀድ እንደሚገባ ጥያቄ አቅርበው ነበር፡፡ በብትን የመላክ መመርያው የተነሳው እነዚህን እውነታዎች ከግምት በማስገባት እንደሆነ ለመረዳት ተችሏል፡፡ መመርያው ከተነሳ በኋላ በብትን መላክ እስኪለመድና ተቀባይነት እስኪያገኝ ድረስ በጆንያ መላኩ እንደ ሽግግር ወቅት ተደርጎ ቢፈቀድም፣ ይህ የሽግግር ወቅት የተባለው በጊዜ ገደብ አለመቀመጡን ከንግድ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡ ለመመርያው መውጣት ሲሰጡ ከነበሩ ምክንያቶች አንዱ ሁሉም ባለድርሻ አካላት አምነውበት ተቀባይነት ያገኘ አሠራር በመሆኑ፣ የዝግጅት ጊዜው አምና ተጠናቆ ዘንድሮ ሙሉ ለሙሉ ወደ ትግበራ ሊገባበት እንደተቻለ መሆኑን ንግድ ሚኒስቴር ለሁሉም ላኪዎች ያሰራጨው ደብዳቤ ያመለክታል፡፡ በሚኒስትር ዴኤታው አቶ ያዕቆብ ያላ ተፈርሞ የወጣው መመርያ እንደሚያትተው፣ ቡናን በብትን በኮንቴይነር ውስጥ አሽጎ መላክ የኢ