የሃዋሳ ከተማ ኣስተዳደር ግለሰቦችን ያለፍቃዳቸው ከቤት ንብረታቸው ባያፈናቅላቸው ምን ይለዋል?

ገዥው ፓርቲ በሚከተለው የከተሞች ልማት ፖሊስ የተነሳ በኢትዮጵያ በርካታ የከተማ ኣስተዳደሮች በየከተሞች ዙሪያ የምገኙትን ገጠራማ ቀበሌዎችን በመዋጥ ላይ ናቸው። በቅርቡ የኣዲስ ኣበባ ከተማ ኣስተዳደር በኣከባቢው የሚገኙትን ገጠራማ ትናንሽ የኦሮሚያ ከተሞችን በልማት ስም ከስሩ ኣስገብቷል።

በርግጥ ትናንሽ ገጠራማ ከተሞችና ቀበሌዎች በትላልቅ ከተሞች ስዋጡ ይህ ለመጀመሪያ ግዜ ኣይደለም። እንዳውም የኣዲስ ኣበባ ከተማ ኣስተዳደር ከእኛዋ ከሃዋሳ ከተማ ልምድ የወሰደ ነው የሚመስለው። ከኣመታት በፊት የሃዋሳ ከተማ ኣስተዳደር በዙሪያው በሲዳማ ዞን ስር ይተዳደሩ የነበሩትን 14 ቀበሌያት በቱላ ክፍለ ከተማ ስር ማጠቃለሉ ይታወሳል።

በጊዜው የደኢህዴን ካድሬዎች ቀበሌያቱ ከሃዋሳ ከተማ ኣስተዳደር ሰር ከተጠቃለሉ ብዙ ጥቅሞች እንደሚያገኙ በመስበክ የየቀበሌያቱን ነዋሪዎች መቆሚያ እና መቀመጫ በማሳጣት እንዲጠቃለሉ እንዳደረጉ ይታወቃል። በርግጥ በርካታ ሰዎች በጉዳዩ ላይ ደሰተኛ ባይሆኑም ለልማት እና ለለውጥ ጉጉ ስለነበሩ ደጋፋቸውን ከመስጠት ኣልተቆጠቡም። እንዳውም የቀበሌያቱን ከሃዋሳ ከተማ ኣስተዳደር ስር መሆንን ኣስመልክተው ከብት ኣርደው ደግሰዋል።

የሆነ ሆኖ፤ በኣሁኑ ጊዜ የቀበሌያቱ ነዋሪዎች በካድሬዎቹ የተገባላቸው የልማት ስራ ኣለመሰራቱን ይናገራሉ። በርግጥ ኣንዳንድ የልማት ስራዎች እየተሰሩ ያሉ ቢሆኑም እየተሰሩ ያሉት የልማት ስራዎች በሌሎች ክፍለ ከተሞች እየተሰሩ ካሉት ጋር የሚወዳደሩ ኣይደሉም ይላሉ። እንዳውም፤ የቀበሌዎቹ ከከተማ ኣስተዳደር ስር መሆናቸውን ተከትሎ በተለይ ከመሬት ይዞታ ጋር በተያያዘ በርካታ ችግሮች ኣጋጥሞቸዋል።

በየቀበሌያቱ ያለው መሬት ተጠንቶ ፕላን እስኪሰራ ድረስ ቤት መገንባት በመከልከሉ የየቀበሌያቱ ነዋሪዎች በወግ ባህላቸው መሰረት የመሬት ይዞታቸውን ለልጆቻቸው ኣውርሰው ቤት መገንባት ኣልቻሉም። ከዚህም ባሻገር የከተማው ኣስተዳደር የመሬት ይዞታችንን ሸንሽኖ ለሌላ ይሰጥብና፤ መሬታችንን በመንግስት እንቀማለን በምል ስጋት ሳይቀድሜን እንቅዴም ኣይነት ኣስተሳሰብ በርካታዎቹ የየቀበሌያቹ ነዋሪዎች የመሬት ይዞታቸውን በህገወጥ መንገድ ለጸጉረ ልውጦች በመሸጥ ላይ ናቸው። ለኣብነትም ያህል በዳቶ ኦዳሄ ቀበሌ ከጥቁር ውሃ ኣንስቶ እስከ ሃዋሳ ሴራሚክ ፋብሪካ ጀርባ ያለው በርካታ ኪሎ ሜትሮችን ያካለለ መሬት በህገ ወጥ ፕላን በሌላቸው ቤቶች ተሞልተዋል።

የቤቶቹ ግንባታ የኣካባቢውን ብሎም የከተማዋን ገጽታ ከማበላሸቱ በላይ ሃብታም የሃዋሳ ከተማ ነዋሪዎች ከድሃው የሲዳማ ተወላጅ በቀላል ዋጋ መሬትን በመግዛት የመሬት ወረራ እያካሄዱ ነው። መንግስት መሬትን መሸጥ እና መለወጥ ከልክሎ እያለ የድሃ ሲዳማ ኣርሶ ኣደሮች የመሬት ይዞታ በሃብታሞች ስወረር የከተማው ኣስተዳደር ጆሮ ዳባ ልበስ ከማለቱ በላይ ሰሞኑን እንደተሰማው ከሆነ ግለሰቦችን ያለ ፍቃዳቸው ከቤት ንብረታቸው እንድነሱ በማስገደድ ላይ ነው።

ሰሞኑን ከማህበራዊ መረብ የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው ኣቶ ሁሴን ከድር የተባሉ የከተማዋ ነዋሪ ለ22 ኣመታት ከኖሩበት እና ቤትና ንብረት ካፈሩበት የመሬት ይዞታቸው በከተማ ኣስተዳደር እንድለቁ ተገደዋል።

‹‹ … ለንብረቴና መኖሪያ ቤቴ ተመጣጣኝ ካሳ የማይሰጠኝ ከሆነ ሕይወቴን አጠፋለሁ›› 
አቶ ሁሴን ከድር ይባላሉ:: 1985 .ም ጀምሮ በሀዋሳ ከተማ በታቦር ክፍለ ከተማ በፋራ ቀበሌ ልዩ ቦታ አዲሱ ገበያ አጠና ተራ አጠገብ ከሁለት ሚስቶቹና 12 ልጆቹ ጋር መኖሪያ ቤት ሰርተው ይኖራሉ:: 
ለአቶ ሁሴን ከድር ከ22 ዓመታት በኋላ ከመኖሪያ ቤታቸው እንደሚነሱ/እንደሚፈናቀሉ ከሀዋሳ ከተማ አስተዳደር የማስፈራሪያ ጥር በዚህ ዓመት የተለያዩ ጊዜያት ይደርሳቸዋል :: አቶ ሁሴንም እንደት ይሆናል? መቼ ይሆናል? እያሉ ስጠባበቅ ይቆያሉ:: አቶ ሁሴን ግን ለንብረቴና ለመኖሪያ ቤቴ ተመጣጣኝ ካሳ የማይከፈለኝ ከሆነ ማንም በንብረቴና በመኖሪያ ቤቴ ላይ ስልጣን የለውም እያለ ቆይቷል::
የሆነው ሆኖ የህዝብ ስሜት የማይረዳውና ገበረውን በማፈናቀል መሬትን በቸርቸር የሚታወቀው የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር በየካቲት 05/2007 .ም የአቶ ሁሴን ከድር መኖሪያ ቤት ከእነ ንብረታቸው ሊያፈርስ የታዘዘው ዶዜር መኪና ወደ ቦታው በደረሰ ጊዜ የአቶ ሁሴን ከድር ውሳኔያቸውን በመቃወም በራሱ ይዞታ ውስጥ በሚገኘው ዋንዛ ዛፍ ላይ ወጥተው ተመጣጣኝ ካሳ ሳይሰጠኝ መኖሪያ ቤቴን ይሁን ንብረቴን የሚትንኩ ከሆነ ሕይወቴን አጠፋለሁ በማለት ከየካቲት 05/2007 .ም ጀምሮ በወጣበት ዛፍ ላይ ይገኛል:: የከተማው አስተዳደር ግን ድርግቱን በዝምታ እየተመለከተ ይገኛል::የመሬት ወረራ ይቁም!!

ይህን መሰል ታሪኮች ከከተማዋ ነዋሪዎች ዘንድ በተደጋጋሚ የምሰሙ ከመሆናቸው በላይ በኣሁኑ ወቅት ኣሳሳብ ደረጃ ላይ ደርሰዋል። ስለዚህ የከተማው ኣስተዳደር የኣገሪቱ ሕገ መንግስት ለዜጎች ያጎናጸፈውን ቤትንብረት የማፍራት እና በነጻነት የመኖር መብት ልያስጠበቅ እንጅ ልጥሰው ኣይገባም።


Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር