ባህልን የመጠበቅ የመንግሥት ግዴታ

አገራችን ኢትዮጵያ የብዙ ባህሎች ባለቤት ናት፡፡ የብሔርና የሃይማኖት ብዙኅነት ያበዛቸው የተለያዩ ባህሎች የኢትዮጵያውያን መታወቂያ ናቸው፡፡
ኅብረተሰብን ኅብረተሰብ ከሚያስብሉት ምክንያቶች አንዱ ባህል ሲሆን፣ ባህሉ የማይታወቅለት ኅብረተሰብ በሌሎች አገሮችም የመታወቁ ነገር አነስተኛ ነው፡፡ አንዲት አገር ለምትከተለው ሁለንተናዊ የዕድገት አቅጣጫ ባህል የራሱ የሆነ አዎንታዊም ሆነ አሉታዊ ተፅዕኖ ይኖረዋል፡፡ በዚህ ጽሑፍ የምንመለከተው አወንታዊ ተፅዕኖ ያላቸውን ባህሎች የሕግ መሠረት ነው፡፡ እነዚህ ባህሎች ለኅብረተሰቡ ቀጣይ ሕልውና መሠረት የሆኑ፣ የአገሪቱን ልማት የሚያግዙና በዓለም አቀፍ ተቀባይነት ባላቸው መስፈርቶች ለግለሰቦች ጠቃሚ የሆኑ ናቸው፡፡
በዚህ ሳምንት እየተከበረ ያለውን የመስቀል በዓል መነሻ በማድረግ በዓላትን ተከትለው የሚታዩ ባህሎችን የሕግ መሠረት መመልከት የዚህ ጽሑፍ ዓላማ ነው፡፡ በዓላት ብዙ ብዙ ክፍል ቢኖራቸውም በአገራችን ባህል ላይ ሰፊ ተፅዕኖ ያደረጉት ሃይማኖታዊ በዓላት ስለመሆናቸው በድፍረት መናገር ይቻላል፡፡ ቁሳዊ የባህል ክፍሎችን ብንመለከት አለባበስ፣ አመጋገብ፣ ለጌጥ የምንጠቀምባቸው ዕቃዎች፣ በዓላቱ የሚከበሩባቸው ቦታዎች ወዘተ. ሃይማኖታዊ መሠረት አላቸው፡፡ የመስቀልን በዓል መነሻ አድርጎ ከሚታዩት ባህሎች ውስጥ በአልባሳት ላይ የሚታዩ ጥልፎች፣ በሰውነት ላይ የሚቀረፁ ጌጦች፣ በደረትና በጆሮ የሚንጠለጠሉ የመስቀል ጌጦች ይገኙበታል፡፡ በደቡብ ብሔሮችና ብሔረሰቦች የተለመዱት የመስቀል በዓል አከባበሮችን ተከትሎ የሚታዩት የአመጋገብ ባህል ተጨማሪ አስረጅ ነው፡፡ ግዙፋዊ ያልሆኑም ባህሎች ከሃይማኖት በመነጩ ባህሎች ይስተዋላል፡፡ ሕዝቡ በኅብረት በመሆን በየሰፈሩ ትናንሽ ደመራ መደመሩ፣ ለንግድ ወጥተው የነበሩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ወደ አካባቢያቸው ተመልሰው የመስቀል በዓልን ማክበራቸው የዚሁ ማሳያ ነው፡፡ በሌሎች የሃይማኖት በዓላትም ሕዝባዊ ባህሎችን እናስተውላለን፡፡ ‹‹ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ›› ‹‹በገና ጨዋታ አይቆጡም ጌታ›› በሚሉት ብሂሎች ውስጥ የሚታዩ የአደባባይ ትዕይንቶች የባህል ነፀብራቅ ናቸው፡፡ በዓላቱ የብሔሮች ዘፈን፣ ጭፈራ፣ አለባበስ፣ ቋንቋ፣ አመጋገብ፣ ወዘተ. የሚታይባቸው ቋሚ ዓውደ ርዕይ ሆነዋል፡፡
ሕግ የኅብረተሰቡን አኗኗር የሚመራ፣ የሚገዛና የሚያስተዳድር እንደመሆኑ መጠን የኅብረተሰቡንም ባህል አይረሳም፡፡ የባህል መብት በሕግ ዕውቅና ካገኙ መብቶች አንዱ ነው፡፡ በዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት አስተምህሮ የሰብዓዊ መብቶች የሲቪል፣ የፖለቲካ፣ የማኅበራዊ፣ የኢኮኖሚና የባህል መብቶች ተብለው እንደሚከፈሉ ከዓለም አቀፍ ሕግ መረዳት ይቻላል፡፡ ከእነዚህ መብቶች አንዱ የባህል መብት ነው፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዓላማም ይህንን ዓለም አቀፍና ብሔራዊ የሕግ ጥበቃ ያገኘውን የባህል መብት ምንነትና ይዘት ወሰንና ጽንሰ ሐሳባዊ ተግዳሮት መቃኘት ነው፡፡
የባህል ትርጉም
የባህል መብት ‹‹ባህል›› ከሚለው ጽንሰ ሐሳብ የሚመነጭ ሲሆን ባህል ብዙ ትርጉም አለው፡፡ አስቢዮን አይዴ የተባለው የሰብዓዊ መብት ምሁር ለባህል ሦስት ትርጉም ይሰጠዋል፡፡ የመጀመሪያው ‹‹Culture is the accumulated material heritage of mankind, either as a whole or part of particular human groups, including but not limited to monuments and artifacts›› የሚለው ነው፡፡ በዚህ ትርጉም መሠረት በዘመናት ሒደት የተፈጠሩ የሕዝብ ቅርሶች በሙሉ ባህል ሊባሉ ይችላል፡፡ ሁለተኛው ትርጉም የባህል አፈጣጠር ሒደት ላይ ትኩረት የሚሰጥ ሲሆን ምሁሩ ‹‹A process of artistic and scientific creation›› በሚል ይገልጸዋል፡፡ ሦስተኛውና ባህልን በሚያጠኑ ባለሙያዎች የሚታወቀው ሰፋ ያለ የባህል ትርጉም ነው፡፡ ይህም ‹‹Culture is the sum total of the material and spiritual activities and products of a given social group which distinguishes from other similar group›› በሚል ይገልጻል፡፡ በዚህ ትርጉም መሠረት ባህል የአንድ ኅብረተሰብ (ቡድን፣ ብሔር ወዘተ.) ከሌላው የሚለይበት መለያ ሲሆን ቁሳዊም ሆነ መንፈሳዊ ሥራዎችን ያጠቃልላል፡፡ የአንድ ኅብረተሰብ አኗኗር፣ እምነት፣ ቋንቋ፣ አመጋገብ፣ በዓል አከባበር፣ ወዘተ. እና ቁሳዊ መሣሪያዎች በሙሉ ባህል ተብለው ሊጠሩ ይችላሉ፡፡
የባህል መብት
የመብት መሠረቱ ሕግ ነው፡፡ ባህልና ሕግንም የሚያገናኛቸው ይሄው ነው፡፡ ሕግ ባህልን የሚጠብቀው የባህል መብትን ሕጋዊ ጥበቃ በመስጠት ነው፡፡ ዓለም አቀፍና ብሔራዊ ሕግጋት ለባህል መብት ጥበቃና ዋስትና ይሰጣሉ፡፡ ከተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብት ሰነዶች ውስጥ ባህልን እንደ መብት ዕውቅና በመስጠት ጥበቃ ደንግገዋል፡፡ ሁሉ አቀፍ የሰብዓዊ መብት መግለጫ (UDHR) በአንቀጽ 27 የማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ ስምምነት (ICESCR) በአንቀጽ 15፣ በሴቶች ላይ የሚፈጸሙ ማንኛውም ዓይነት መድሎን ለማስወገድ በተደረገው ስምምነት (CEDAW) አንቀጽ 13 (c)፣ በሕፃናት መብት ስምምነት አንቀጽ 13፣ የዘር መድልኦን ለማስቀረት በወጣው ስምምነት አንቀጽ 5(e) [vi] የተወሰኑት ድንጋጌዎች ናቸው፡፡ በአፍሪካ ደረጃም የአፍሪካ የሰዎችና የሕዝቦች መብቶች ቻርተር በአንቀጽ 17 እና 29 ላይ ስለ ባህል መብት ደንግጓል፡፡ በእነዚህ ስምምነቶች መሠረት ማንኛውም ሰው አናሳ ቡድኖች፣ ሕፃናትና ሴቶችን ጨምሮ በባህል የመሳተፍ፣ ባህላቸውን የማስፋፋትና የማሳደግ መብት አለው፡፡ አንዳንዳቹ ሰነዶች ለጥቃት የተጋለጡ የኅብረተሰብ ክፍሎችን በመለየት የደነገጉበት ምክንያት በኅብረተሰቡ ተፅዕኖ የባህል መብታቸው እንዳይጣስባቸው በማሰብ ነው፡፡  
ብሔራዊ ሕግጋትን በተመለከተ የአገራችን ሕገ መንግሥት በተለያዩ ድንጋጌዎች ለባህል መብት ዕውቅና ይሰጣል፡፡ የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 39(2) መሠረት ማንኛውም የኢትዮጵያ ብሔር፣ ብሔረሰብና ሕዝብ በቋንቋው የመናገር፣ እንዲሁም ታሪኩን የመንከባከብ መብት አለው፡፡ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 41(9) መሠረት ደግሞ መንግሥት የባህልና የታሪክ ቅርሶችን የመንከባከብና ለሥነ ጥበብና ለስፖርት መስፋፋት አስተዋጽኦ የማድረግ ኃላፊነት እንዳለበት ተደንግጓል፡፡ በአንቀጽ 91 ደግሞ መንግሥት መልካም ባህሎችንና ልምዶችን በእኩልነት እንዲጎለብቱና እንዲያድጉ የመርዳት ኃላፊነት እንዳለበት ተደንግጓል፡፡ ሕገ መንግሥቱን መሠረት አድርገው የወጡ ሕግጋትም ለባህል መብትና ተጨማሪ ጥበቃ ይሰጣሉ፡፡ ለአብነት በቤተሰብ ሕግ ለባህል ጋብቻ የተሰጠው ዕውቅና፣ በፈጠራና በአዕምሮ ንብረቶች ሕግ ለባህል የተሰጠው ጥበቃ፣ በቅርስ ጥበቃ አዋጅ ግዛፋዊና ግዙፋዊ ላልሆኑ ቅርሶች የተቀመጠውን የሕግ ጥበቃን ማንሳት ይቻላል፡፡ 
የመብቱ ይዘት
ለባህል መብት ጥበቃ የሚሰጡትን የሕግ ሰነዶችን የመረመረ የባህል መብት ይዘትን በቀላሉ መረዳት ይችላል፡፡ በእነዚህ ሕግጋት ከተገለጹት የባህል መብቶች አራቱን እንጥቀስ፡፡ የመጀመሪያው የማንኛውም ሰው በባህላዊ ሕይወት የመሳተፍ መብቱ ነው፡፡ ሁለተኛው ማንኛውም ሰው በሳይንስ ዕድገትና ለውጥ ከሚገኙ ጥቅሞች ተጠቃሚ የመሆን መብቱ ነው፡፡ ሦስተኛው ግለሰቡ በሳይንስ፣ በኪነ ጥበብና በሥነ ጽሑፍ ላመነጨው የባህል ሥራ ተገቢውን የሞራልና የኢኮኖሚ ጥቅም የሚያገኝበት መብት ነው፡፡ አራተኛው ደግሞ ሳይንሳዊና የፈጠራ ሥራዎችን በተመለከተ ጥናት የማድረግ መብት ነው፡፡ የእነዚህ መብቶች ወሰን ሰፊ መሆኑን ለመረዳት ከሌሎች ሰብዓዊ መብቶች ጋር ያላቸውን ተዛምዶ መመልከት በቂ ነው፡፡ በዚህ ረገድ የመማር መብት በራሱ የባህል መብት አካል ነው፡፡ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት ባህልን የማሳወቅ፣ የመግለጽና የማስፋፋት መብትን ይጨምራል፡፡ ባህልና ሃይማኖት የቀረበ ቁርኝነት ስላላቸውም የባህል መብት በሃይማኖት ነፃነት መብት የሚደግፍ ይሆናል፡፡ የመሰብሰብና የመደራጀት መብትም በኅብረተሰቡ የእርስ በርስ ግንኙነት የሚፈጸሙ በመሆናቸው ከባህል መብት ጋር ቅርብ ትስስር አላቸው፡፡ 
የመብቱ ባለቤት ማነው?
በተባበሩት መንግሥታት የወጡት የሕግ ሰነዶች የባህል መብት የግለሰብ መብት እንደሆነ ያስቀምጣሉ፡፡ እነዚህ ሰነዶች መብቶችን ግለሰባዊ ብቻ በሚያደርገው ምዕራባዊ ባህል ተፅዕኖ ሥር የወደቁ በመሆናቸው ባህልንም የግለሰብ መብት ብቻ አድርገው ይቆጥራሉ፡፡ የዓለም አቀፍ የሲቪልና የፖለቲካ ቃልኪዳን አንቀጽ 27ን ብንወስድ የብሔር፣ የሃይማኖትና የቋንቋ አናሳ ቡድን አባላት ባህላቸውን ከመከተል፣ ከመግለጽና ሃይማኖታቸውን ከመተግበር ወይም የራሳቸውን ቋንቋ ከመጠቀም ሊከለከሉ እንደማይገባ ይደነግጋል፡፡ በዚህ ድንጋጌ መሠረት የመብቱ ተጠቃሚ (ባለቤት) ግለሰቡ እንጂ የአናሳው ቡድን አይደለም፡፡ የባህል መብት ባህርይ ግን ግለሰቦች በቡድን ሆነው የሚጠቀሙበት ነው፡፡ ቡድኑ የኅብረት ሕልውናውን ካጣ የግለሰቡ መብት ሊወሰን ወይም ሊነፈግ ይችላል፡፡ 
ባህልን እንደ ቡድን መብት ዕውቅና የሚሰጠው የአፍሪካ የሰዎችና የሕዝቦች መብቶች ቻርተር ነው፡፡ ይህ ቻርተር ማንኛውም ሰው በባህል የመሳተፍ መብት እንዳለው በአንቀጽ 17 ከመግለጹ ጎን ለጎን በአንቀጽ 29 እያንዳንዱ ግለሰብ በኅብረተሰብ ውስጥ ሲኖር አዎንታዊ የአፍሪካ ባህሎችን የመጠበቅና የማሳደግ ግዴታ ተጥሎበታል፡፡ ስለዚህ አፍሪካዊ ባህልን መጠበቅ እንደ ግዴታ ከተቀመጠ አንፃራዊ መብት ያለው አካል (ኅብረተሰብ) አለ ማለት ነው፡፡ የአገራችንም ሕገ መንግሥት እያንዳንዱ ብሔር ባህሉን የመከተል፣ የማሳደግና የማሰፋፋት መብት እንዳለው ስለሚገልጽ መብቱ የቡድን መብት ስለመሆኑ ገላጭ ነው፡፡ 
ከሁለቱ የተለያዩ አስተምህሮዎች በመነሳት አስታራቂውን ሐሳብ መረዳት ይቻላል፡፡ ባህል የግለሰብም የቡድንም መብት ነው፡፡ የግለሰብ የባህል መብትና የኅብረተሰብ የባህል መብት አንድ በሆነበት አጋጣሚ የመብቱ አፈጻጸም ተግዳሮት እንደሚገጥመው ማሰብ አስቸጋሪ አይሆንም፡፡ ግለሰቦች በሉላዊነት (Globalization) ተፅዕኖ ባህልን ወደ ጎን ቢያደርጉ ከብዙኃኑ ተቃውሞ ይደርስባቸዋል፡፡ በሌላ በኩልም በኅብረተሰቡ ተሰሚነት የሚኖራቸው ግለሰቦች ከእነሱ አስተሳሰብ ጋር የማይሄደውን ባህል ለማፈን በመሞከር የኅብረተሰቡን የባህል መብት የሚነኩበት አጋጣሚ ሊኖር ይችላል፡፡ አንዳንድ ባህልም (ለምሳሌ ያለዕድሜ ጋብቻ) የግለሰቦችን የሰብዓዊ መብት የሚጥስበት ሁኔታ ይኖራል፡፡ እንዲህ ዓይነት ተቃርኖ መፍትሔ የሚያገኘው የባህል መብትን የማስከበር ግዴታ ያለበት መንግሥት ግዴታውን ሚዛናዊ በሆነ መልኩ ሲወጣ ነው፡፡ ሕገ መንግሥቱም መሠረታዊ መብቶችንና ሰብዓዊ ክብርን የሚቃረኑ ባህሎችን እንደማይታገስ ግልጽ አድርጓል፡፡ የሕገ መንግሥቱን አንቀጽ 91(1) ይመለከቷል፡፡ 
የመንግሥት ግዴታ
ሰብዓዊ መብትን በማስፈጸም ረገድ መንግሥት ያሉበት ሦስት መሠረታዊ ግዴታዎች ለባህል መብትም ተፈጻሚ ይሆናሉ፡፡ መንግሥት የባህል መብትን የማክበር፣ የመጠበቅና የማሟላት ግዴታ አለበት፡፡ በተለይ የባህል መብት በተለምዶ ‹‹ሁለተኛው ትውልድ መብቶች›› ከሚባሉት ምድብ የሚገኝ እንደመሆኑ መጠን መንግሥት የባህል መብት በሒደት እንዲሟላ ያለውን ሀብት በመጠቀም ከፍተኛ ጥረት ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ 
በባህል የመሳተፍ መብትን ለአብነት በመውሰድ የመንግሥትን ግዴታ ስንመለከት ጉዳዩ የበለጠ ይገለጻል፡፡ የመጀመሪያው መንግሥት ግለሰቦች ወይም ቡድኖች የመረጡትን ባህላዊ አመለካከት ሲያንፀባርቁና ሲያሳድጉ ሊያከብርላቸው ይገባል፡፡ ይህ ግዴታ መንግሥት ሐሳብን የመግለጽ መብትን ከማክበር ግዴታው ጋር ይመሳሰላል፡፡ ሁለተኛው መንግሥት መብትን የሚጠቀመው ሰው ወይም ቡድን በሦስተኛ ወገን (ከመንግሥት ውጭ ባለ ሰው ወይም አካል) እንዳይከለከል ወይም እንዳይገደብ የመጠበቅ ግዴታ አለበት፡፡ እንደሚታወቀው የአንዱ ባህል ላንዱ ላይመች የሚችልበት አጋጣሚ ይኖራል፡፡ በሃይማኖት አመለካከት የሚኖረው ልዩነትም እንደዚሁ ነው፡፡ የባህል መብት አፈጻጸም ግጭት እንዳያስከትል መንግሥት ጥበቃ ሊያደርግ ይገባል፡፡ አንዳንዴም ለሁሉ በታወቀ ሕግና መስፈርት መሠረት የባህል ነፃነቱን ማጥበብ ወይም መገደብ ይጠበቅበታል፡፡ ሦስተኛው የመንግሥት ግዴታ ግለሰቦች ወይም ቡድኖች በባህላቸው እንዲሳተፉ ማገዝና ሁኔታዎችን ማሟላት ነው፡፡ የዓለም አቀፍ የማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ ስምምነት ኮሚቴ መንግሥት ማሟላት ያለበትን በአጠቃላይ አስተያየቱን (General comment) ዘርዝሯል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ለባህል ማስፋፊያና ለኅብረተሰብ ተሳትፎ በጀት መመደብ፣ ባህልን የሚያስፋፉ ተቋማዊ አደረጃጀቶች እንዲኖሩ ማድረግ፣ የባህል ማዕከል፣ ሙዚየም፣ ቤተ መጻሕፍት፣ ቴአትር፣ ሲኒማ፣ ዕደ ጥበብ ወዘተ. ማስፋፋትና ተገቢውን የሚዲያ ሽፋን መስጠት ይገኙበታል፡፡ 
ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው የሕግ ጠበቃና አማካሪ ሲሆኑ፣ በኢሜይል አድራሻቸው   getukow@gmail.com  ማግኘት ይቻላል፡፡ 

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር