የግብርና ሚኒስቴር የገጠር መሬት የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ በድጋሚ ሊሰጥ ነው


ግብርና ሚኒስቴር ለሁለተኛ ጊዜ በአራት ክልሎች ውስጥ ለሚገኙ 50 ሚሊዮን ማሳዎች በካዳስተር ካርታ የተደገፈ የገጠር መሬት ይዞታ ማረጋገጫ ሰርተፊኬት ሊሰጥ ነው፡፡
የካዳስተር ካርታ ሥራውን የሚያካሂዱት የኢትዮጵያ ካርታ ሥራ ኤጀንሲና የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት ኤጀንሲ ናቸው፡፡ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ስለሺ ጌታሁን፣ የኢትዮጵያ ካርታ ሥራ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሡልጣን መሐመድና የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ብርጋዴር ጄነራል ተክለብርሃን ወልደአረጋይ የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርመዋል፡፡

ነገር ግን የግብርና ሚኒስቴር ለዚህ ፕሮጀክት የሚያስፈልገውን ፋይናንስ በእጁ ባለማስገባቱ ሥራው እንዳልተጀመረ ምንጮች ገልጸዋል፡፡ ግብርና ሚኒስቴር የሚያስፈልገውን ገንዘብ የዓለም ባንክ እንዲያቀርብለት ጥያቄ አቅርቧል፡፡ የዓለም ባንክ ገንዘቡን በቅርቡ እንደሚለቅ ምንጮችም ገልጸዋል፡፡

ገንዘቡ እንደተለቀቀ ደኅንነት ኤጀንሲ ማሳዎቹን የአየር ፎቶ ያነሳል፡፡ ያነሳውንም ፎቶ ለካርታ ሥራ ኤጀንሲ ያስረክባል፡፡ ካርታ ሥራ ኤጀንሲ የማሳዎቹን ካርታ እንደሚሠራና ለሚኒስቴሩ እንደሚያስረክብ ታውቋል፡፡ ቀደም ባሉት ዓመታት መንግሥት በየክልሉ በባህላዊ የአሠራር ዘዴ በመጀመርያ ደረጃ የገጠር መሬት የይዞታ ማረጋገጫ ሰርተፊኬት በማዘጋጀት 90 በመቶ ለሚሆኑ አርሶ አደሮች ማደሉ ታውቋል፡፡

ነገር ግን ቀደም ሲል የቀረበው ካርታ የተጠናከረ መረጃ የማይሰጥ በመሆኑና በመጀመርያ ደረጃ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ላይ የነበሩበትን ክፍተቶች በማስተካከል እንደ አዲስ መረጃ የሚሰጥ ካርታ መስጠት እንደሚገባ ታምኖበታል፡፡ የገጠር መሬት አስተዳደር ሥርዓቱን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተደገፈ ለማድረግ የካዳስተር የመሬት መረጃ ማዘጋጀት አስፈላጊ ሆኖ ተኝቷል ተብሏል፡፡

አዲሱ ሁለተኛ ደረጃ የገጠር መሬት ምዝገባና ቅየሳ የሚይዛቸውን መስፈርቶች በሚመለከት የግብርና ሚኒስቴር አራት ነጥቦችን ያስቀምጣል፡፡ የመጀመርያው የመሬቱ ትክክለኛ ስፋት፣ አቅጣጫና የሚገኝበትን መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ በቀላሉ መለየት በሚያስችል መንገድ ይዘጋጅ ይላል፡፡ በሁለተኛ ደረጃ እያንዳንዱ የገጠር መሬት ይዞታ የሚለይበት ልዩ የማሳ መለያ ኮድ ይኖረዋል፡፡

ሦስተኛ ለገጠር መሬት ልውውጥና ማስተላለፍ አመቺ የሆነ መረጃ ሥርዓት ይዘረጋለታል፡፡ የመጨረሻው ነጥቡ ይዞታውን በሚያሳይ የካዳስተር ካርታ እያንዳንዱ የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ሰርተፊኬት ይኖረዋል፡፡ ሚኒስቴሩ ገንዘቡን እንዳገኘ ወደ ሥራ የሚገባ ሲሆን፣ ሥራው ከተጠናቀቀ በኋላ በትግራይ፣ በአማራ፣ በኦሮሚያና በደቡብ ክልሎች የሚኖሩ አርሶ አደሮች በድጋሚ ተመዝግበው የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ይሰጣቸዋል ተብሏል፡፡   

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር