ተቃዋሚዎቹ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር መነጋገር ይፈልጋሉ
ሰላሣ ሦስት የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በዚህ ዓመት የሚደረገው የአካባቢ ምርጫና ወደፊትም የሚካሄዱት ምርጫዎች እንደ 2002 ዓመተ ምኅረቱ ከሆኑ ለአገሪቱ ህልውናም አስጊ ናቸው አሉ። ፓርቲዎቹ ከዚህ አኳያ መንግሥት እንዲያነጋግራቸው ለጠቅላይ ሚኒስትር ፅሕፈት ቤት ጥያቄ እንደሚያቀርቡ አስታውቀዋል። ባለፈው ወር አዳማ ከተማ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የ2005 ዓ.ም የአባባቢ ምርጫን አስመልክቶ መርኃግብሩን ካሣወቀ በኋላ እነዚህ ፓርቲዎች ላቀረቡት የጋራ ጥያቄ “አጥጋቢ መልስ አልሰጠም” ሲሉ ሰላሣ ሦስቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ያቋቋሙት ጊዜያዊ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ አሥራት ጣሴ ለቪኦኤ ገልፀዋል፡፡ አቶ አሥራት ጣሴ በኢትዮጵያ የሚካሄዱት ምርጫዎች ነፃ፣ ፍትሐዊ፣ ሕጋዊና ተቀባይነት ያላቸው እንዲሆኑ ከተፈለገ ያለፈውን መንገድ መድገሙ ዋጋ የለውም፣ የበለጠ ችግርም ውስጥ ይከትተናል ብለዋል ፓርቲዎቹ፡፡ ይህ የፓርቲዎቹ ብቻ ዕምነት እንዳልሆነ የጠቆሙት አቶ አሥራት ጣሴ በ2002 ዓ.ም የተካሄደውን ሃገርአቀፍ ምርጫና ኢሕአዴግ 99.6 ከመቶ አሸንፌበታለሁ ያለበትን ምርጫ ዓለምአቀፍ ታዛቢዎች አይቀበሉትም” ብለዋል፡፡ ዝርዝሩን ከመለስካቸው አምኃ ዘገባ ያዳምጡ፡፡