አሥራ አምስት የመንግሥት ሆስፒታሎች የልቀት ማዕከል ሊሆኑ ነው
በታደሰ ገብረ ማርያም በመላ አገሪቱ የሚገኙና በአጠቃላይ የ15 ሚሊዮን ብር ተሸላሚ የነበሩ 15 ምርጥ የመንግሥት ሆስፒታሎችን ከፍተኛና ጥራት ባለው የሕክምና ቴክኖሎጂ በማደራጀት፣ የልቀት ማዕከል እንዲሆኑ የማድረግ እንቅስቃሴ በመከናወን ላይ መሆኑ ታወቀ፡፡ እስካሁን በተካሄደው እንቅስቃሴ አዲስ አበባ ከተማ ለሚገኝ አንድ ምርጥ ሆስፒታል ኤምአርአይ የተባለ ዘመናዊ የሕክምና መሣርያ የቀረበለት መሆኑን፣ በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የሜዲካል ሰርቪስ ዳይሬክቶሬት ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ ምንጮች በተለይ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የትኛውንም የአካል ክፍል ጥራት ባለው ምስል የሚያሳየው የተራቀቀ ቴክኖሎጂ የቀረበውም ለቅዱስ ጳውሎስ ስፔሻላይዝድ አጠቃላይ ሆስፒታል ነው፡፡ በተለያዩ ክልሎች የሚገኙ ሌሎችም ምርጥ ሆስፒታሎች አቅም በፈቀደ መጠን በየተራ የዚሁ የተራቀቀ ቴክኖሎጂ ባለቤት የሚሆኑበት ጊዜ ሩቅ እንደማይሆን ተጠቁሟል፡፡ በመላ አገሪቱ ከሚገኙ 119 የመንግሥት ሆስፒታሎች መካከል፣ 15ቱ ብቻ ምርጥ ተብለው ሊለዩ የቻሉት የተለያዩ ደረጃዎች ያሉትና የተገልጋዩን እርካታ ማዕከል ያደረገ መስፈርት በማውጣት መሆኑን ምንጮች ጠቅሰው፣ የመጀመርያው መስፈርት የሆስፒታሎቹን አገልግሎትና የአፈጻጸም ሁኔታን የሚመለከት መሆኑንና በመስፈርቱ 30 ሆስፒታሎች መመረጣቸውን አስረድተዋል፡፡ በሁለተኛ ደረጃ የተቀመጠው መስፈርት ተግባራዊ የሆነው የሰላሳዎቹን ሆስፒታሎች የሕክምና አገልግሎት አሰጣጥን በአካል ተገኝቶ በማየትና በመገምገም ሲሆን፣ በዚህ ዓይነቱም አካሄድ 15 ሆስፒታሎች የሚፈለገውን ደረጃና መስፈርት አሟልተው በመገኘታቸው፣ ‹‹ምርጥ ሆስፒታሎች›› ተብለው መመረጣቸውን ከምንጮች ማብራሪያ ለመዳት ተችሏል፡፡ ‹‹የኢትዮጵያ ሆስፒታሎች ትብብር ለጥራት›› በሚል ፕሮጀክት አማካይነት መስፈር