ክልሎች ከፌዴራል መንግሥት በሚጋሯቸው ገቢዎች ላይ ጥያቄ አነሱ
በዮሐንስ አንበርብር ክልሎች ከፌዴራል መንግሥት ጋር የሚጋሯቸው የተለያዩ የገቢ ዓይነቶች መከፋፈያ ቀመር ጊዜው ያለፈበትና አሁን ያለውን የዕድገት ደረጃ ያላገናዘበ በመሆኑ እንዲሻሻል ጥያቄ አቀረቡ፡፡ የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት ለፌዴራል መንግሥቱ ከሚሰጣቸው ሥልጣኖች አንዱ ከክልል መንግሥታት ጋር ያለውን የጋራ ገቢ እንዲሰበስብና ለክልሎቹ የሚገባቸውን ድርሻ እንዲያስተላልፍ ነው፡፡ በዚህም መሠረት የፌዴራል መንግሥትና የክልሎች የጋራ ገቢዎች የሚባሉት በሕግ ተወስነው ተለይተዋል፡፡ እነዚህም በፌዴራል መንግሥትና በክልሎች የጋራ ባለቤትነት ከተመሠረቱ የልማት ድርጅቶች የሚገኝ ገቢ፣ በክልል የተመሠረቱ ኃላፊነታቸው የተወሰነ የግል ማኅበራት (ፒኤልሲ) እና በክልሎች የሚገኙ የተለያዩ የተፈጥሮ ሀብቶችን ለማውጣትና ለመጠቀም ፈቃድ የተሰጣቸው ድርጅቶች ከሚከፍሉት ሮያሊቲ የሚገኝ ገቢ ናቸው፡፡ ከእነዚህ ዘርፎችና የገቢ ዓይነቶች የሚገኘውን ሀብት ክልሎች ከፌዴራል መንግሥት ጋር የሚከፋፈሉት በ1989 ዓ.ም በፌዴሬሽን ምክር ቤት ፀድቆ በሥራ ላይ እንዲውል በተደረገው ቀመር አማካይነት ነው፡፡ የፌዴሬሽን ምክር ቤት በትናንትናው ዕለት ባደረገው ስብሰባ በዚህ ቀመር ላይ በዋነኝነት ተወያይቷል፡፡ የምክር ቤቱ የድጎማ፣ የበጀትና የገቢዎች ድልድል ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ የክልሎችን ጥያቄ በመንተራስ፣ በዚህ ዓመት የገቢ ማከፋፈያ ቀመሩን ለመፈተሽ ዕቅድ ይዟል፡፡ የኮሚቴው ሰብሳቢ የሆኑት የደቡብ ክልል ፕሬዚዳንቱ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት ሪፖርት፣ ቀመሩ አሁንም በሥራ ላይ የሚገኝ ቢሆንም ቀመሩ ግን በቂ ግንዛቤ ያልተጨበጠበት እንደሆነ፣ ባለድርሻ አካላትና ክልሎች በቀመሩ ላይ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት እንዲሰጣቸውና እንዲሻሻል ተደጋጋሚ ጥሪ ማቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡ በአሁ