የሥልጣን መተካት በሕገ መንግሥቱ
የዚህ ሰሞን የአገራችን ድባብ ተለውጧል፡፡ ሚዲያው በሐዘን ዜና፣ ሕዝቡም በትካዜ ተውጧል፡፡ በአንድ ሳምንት ውስጥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንና የኢትዮጵያ ሕዝብ መሪዎቹን አጥቷል፡፡ ፓትርያርኩም ጠቅላይ ሚኒስትሩም ከነበራቸው አገራዊና አኅጉራዊ ተሰሚነት አንፃር ዜና ዕረፍታቸው አስደንጋጭ ነበር፡፡ በየሚዲያው የምንሰማው የእንጉርጉሮ የዋሽንት ድምፅ፣ በየመንገዱ የተመለከትናቸው ጥቁር አልባሳት፣ የሐዘን መግለጫዎችና ለቅሶዎች ሁሉንም የኩነቱ አካል አድርጎታል፡፡ ‹‹ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ . . . ›› እንዲል ሰዎች ከሞታቸው ጋር የሚኖሩ ቢሆንም፣ መልካም ለሠሩት ወይም ለሚሠሩት የሥራ ጊዜ ቢያገኙ መልካም ነበር፡፡ ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ግን የሥራው መቀጠል፣ የተተኪ አመጣጥ ወዘተ. እኛው ጋ የሚቀሩ ሀቆች ናቸው፡፡ ለዚህም ነው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ‘ዓቃቤ መንበረ ፓትርያርክ’ የኢትዮጵያ መንግሥትም ‘ጊዜያዊ የጠቅላይ ሚኒስትር’ የሾሙት፡፡ የፕትርክናው አመራረጥ አካሄድ በቃለ አዋዲ የሚመራና ለሲኖዶሱ ደንብ የማውጣት፣ ኮሚቴ የማዋቀርና ምርጫውን የማስፈጸም ሥልጣን የተሰጠ ቢሆንም፣ ሥራው የተወሰኑ ተግዳሮቶች እንዳሉት ይታመናል፡፡ የቤተ ክርስቲያኗን አንድነት መጠበቅ፣ አካሄዱን በተቀደሰ መንፈስ መምራት፣ ነገሮችን በጥበብና በጥንቃቄ መፈጸም ግቡን ያሳምረዋል፡፡ የመንግሥትም ጠቅላይ ሚኒስትሩን የመሾም ወይም የመተካት አካሄድ የሚኖረው የሕግ ክርክር ሊኖር እንድሚችል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሕመም ላይ በነበሩበት ጊዜ በሪፖርተር ጋዜጣ የተለያዩ አምዶች ላይ ሲስተናገዱ የነበሩ የአቋም ልዩነቶች አመላካች ናቸው፡፡ ክርክሮች ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ዜና ዕረፍት በኋላም የሚነሱ በመሆናቸው ሕገ መንግሥቱን መሠረት አድርጎ እልባት መስጠቱ አማራጭ የለውም፡፡ በዚህ ጽሑፍ የሚስተናገደ