ፖለቲካ እና ኩሽ ኩሸቲክ
ክፍል ፩ የኩሽና የኩሸቲክ ጉዳይ የፖለቲካ መነጋገሪያ ከሆነ ሰነበተ። እውነታውን መርምሮ ከማወቅ ይልቅ እዚህም እዚያም ለጊዜያዊ ፍጆታ በሚመስል የታሪክ መሠረት የሌለው ትርክት በዘፈቀደ ሲሰጥ ይስተዋላል። ይህን ጉዳይ ፈረንጆች ሳይቀሩ ታዝበውታል፣ “ዛሬ የኢትዮጵያ ፖለቲከኞች የኩሸቲክ ሕዝብ ከሴሜቲክ ሕዝብ በላይ የአገሪቱ ባለመብት እንደሆኑ አጥብቀው ያሰምሩበታል” (ብሬየር 2007:460)። ለዚህ ሦስት መሠረታዊ ምክንያቶች ማቅረብ ይቻላል። አንደኛ፣ የዘመናችን የኩሸቲክ ቋንቋ ተናጋሪዎችን ከጥንታዊ የኩሽ ሕዝቦች ጋር አለቦታቸው ማዛመድ፤ የቋንቋና የሕዝብ ግንኙነትን በውል አለመለየትና ስለቋንቋዎቹ የቅርብ ጊዜ ጥናቶች የደረሱበትን በአግባቡ አለመረዳት ችግር ነው። ሁለተኛው፣ በቀደምት ጸሐፊዎች የቀረቡ ግልፅ ያልሆኑ፣ በተወሰነ ደረጃም የሚያምታቱና አሳማኝ ታሪካዊ መረጃ የሌላቸው፣ እንዲሁም ታሪክና እምነት አለመንገዳቸው እየተደባልቁ የቀረቡባቸው ትርክቶች መቅረባቸውም ጭምር ሊሆን ይችላል። ሦስተኛው፣ ስለኩሽ ስርወ መንግሥትና ስለኩሸቲክ ቋንቋዎች ቀደም ባሉት ጊዜያት ብዙም አለመታወቁ ነበር። ስለኩሸቲክ ቋንቋዎች የእርስ በርስ ግንኙነትና አጠቃላይ የዘር ምደባ በበቂ ሁኔታ አይታወቅም ነበር። አሁንም በአርኪ ሁኔታ ታውቋል ማለት አይቻልም። ለዚህ የተለያዩ ድምዳሜ ላይ የደረሱ የቅርብ ጊዜ ጥናቶችን ማየቱ ብቻ በቂ ነው። ስለጥንታዊው የኩሽ ስርወ መንግሥትም ያለው ሁኔታ ተመሳሳይ ነው። የግብፅ ታሪክ ጥላ የሆነበት ይመስላል። ስለዚህ ስርወ መንግሥት አሁንም ብዙ ታውቋል ማለት አይቻልም። ለዚህ በርካታ ምክንያቶች አሉ። አንደኛው፣ ጽሑፍ በኩሽ ስርወ መንግሥት የጀመረው ዘግይቶ መሆኑና እሱም ቢሆን ይዘቱ አለመታወቁ ነው። ሁለተኛው ዘረኝነት ነው። የኩሽ መንግሥት በማያጠያ...