የትናንቱ ጐዳና ተዳዳሪ የዛሬው ብሔራዊ ቡድን ፈርጥ
በደረጀ ጠገናው ብራዚል ለዛሬው የእግር ኳስ ስፖርቷ፣ ክብሯንና ማንነቷን የገነባችው ትናንት ከየጐዳናውና ጉራንጉሩ ትመለምላቸው በነበሩ የኳስ ፈርጦቿ አማካይነት መሆኑ የአደባባይ ሚስጢር ነው፡፡ ከእነዚህ የምንግዜም ዝነኛ የኳስ ክዋክብት መካከል ጋሪንቻና ሌሎችም በርካታ ቁጥር ያላቸው ብራዚላውያን ታዳጊዎች ይጠቀሳሉ፡፡ ገና በለጋ ዕድሜያቸው የሕይወት ውጣ ወረድ ገፈት ሊጋፈጡ የተገደዱት ጋሪንቻና ሌሎቹም የቱንም ያህል እግር ኳስን ቢወዱም፣ የቱንም ያህል ችሎታና ክህሎቱ ቢኖራቸውም በተለይ ጋሪንቻ ‹‹እግረ ደጋን›› እየተባለ ፈላጊ አልነበረውም፡፡ እግሩ ያነክሳልና ለእግር ኳስ አይመጥንም እየተባለ ብዙ ተንከራቷል፡፡ የኋላ ኋላ ግን የኳስ አምላክ ትክከለኛውን የኳስ ግጣም አገናኘና ጋሪንቻ በብራዚል ሜዳዎች ብቻ ሳይሆን በዓለም ዋንጫ መድረኮች ሁሉ ገነነባቸው፡፡ እንደ ጋሪንቻ ሁሉ ሌሎችም ከብራዚል ጐዳናዎች የተገኙ የእግር ኳስ ጠበብት ሮናልዶ ናዛሪዮ ሊዊስ ዴሌማ፣ ሮናልዲኒሆ ጐቹን ጨምሮ ለዓይን የሚታክት በርካታ ፈርጦች ልጥቀስ ይቻላል፡፡ ለመነሻ ያህል ስለብራዚላውያን የጐዳና ፈርጦች አወሳን እንጂ ልናወራ ያሰብነው፣ የኢትዮጵያ ጐዳናዎችም የጨርቅ ኳስን ከእግራቸው አፋቅረው የመንገደኞችን ቀልብ እየገዙ ኳስን የሚያንከባልሉ ጥቂት አይደሉምና የምንለውን ለማለት ነው፡፡ በርካቶች ግን ፈላጊ እያጡ ችሎታቸውን አይቶ ተገቢ ቦታ የሚሰጣቸው ባለማግኘታቸው እየደበዘዙ ሲጠፉ ቆይተዋል፡፡ በዚህ ዘመን ግን አንድ ያልተጠበቀ ጮራ በድንገት ፈንጥቋል፡፡ አስገዳጁና እንዲያም ሲል በጐዳና የጨርቅ ኳሶች ላይ ሲሾሩ የቆዩት የታዳጊ ወጣት እግሮች ቦታቸውን እንዲያገኙ ግድ ብሏል፡፡ በአሁኑ ጊዜም የአገርን ባንዲራ አስከብረው የባላንጣ ውጋት እየሆነ እግሮቹ ምትሀት እያሳዩ ይገኛሉ፡