ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በአየር ንብረት ለውጥና በምግብ ዋስትና ላይ ያተኮረ የምርምርና የትምህርት መርሀ ግብር መጀመሩን አስታወቀ
የሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ከጀርመኑ ሆኸንየም ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በአየር ንብረት ለውጥና በምግብ ዋስትና ላይ ያተኮረ የምርምርና የድህረ ምረቃ ትምህርት መርሃ ግብር መጀመሩን አስታወቀ፡፡ የአየር ንብረት ለውጥ በምግብ ዋስትና ላይ በሚያሳድረው ተጽዕኖና መፍትሄዎች ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ እየተካሄደ ነው፡፡ የዩኒቨርሲቲው የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንት ዶክተር ተስፋዬ አበበ እንደገለጹት፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እየተደረገ ያለው ጥረት በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት ተግዳሮት እየገጠመው ነው። "ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ሰፊ ጥናትና ምርምር ማድረግና በዘርፉ የተማረ የሰው ኃይል ማፍራት ያስፈልጋል" ብለዋል። ለእዚህም የሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ከጀርመኑ ሆኸንየም ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር የአየር ንብረት ለውጥ በምግብ ዋስትና ማረጋገጥ ላይ እያሳደረ ያለውን ተፅዕኖ ለመፍታት የሚያስችል ፕሮጀክት ተግባራዊ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። እንደ ምክትል ፕሬዚዳንቱ ገለጻ በፕሮጀክቱ 14 የምርምር ሥራዎች የሚካሄዱ ሲሆን በዩኒቨርሲቲዎቹ 12 ባለሙያዎች የዶክትሬት ዲግሪ ትምህርት እየተከታተሉ ይገኛሉ። በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ዶክተር ስንታየሁ ይግረም በበኩላቸው ፕሮጀክቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ በ2030 ከተያዙ 17 ዘላቂ የልማት አጀንዳዎች መካከል ሰባቱን ለማሳካት የተቀረጸ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ ፕሮጀክቱ በምግብ ዋስትና፣ በአየር ንብረት ለውጥና በትምህርት ላይ ትኩረት ያደረገ መሆኑን የገለፁት አስተባባሪው በጀርመን መንግስት በተመደበ በጀት ተግባራዊ እንደሚደረግ ተናግረዋል። በጀርመን ሆኸንየም ዩኒቨርሲቲ በአየር ሁኔታ ትንበያ የዶክትሬት ዲግሪያቸውን እየሰሩ ያሉት