ጠቅላይ ሚኒስትሩ አርሶ አደርን ጨምሮ ከአርቲስትና ከተማሪ ጋር ለምርጫ ይወዳደራሉ
ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦና ሕዝቦች ክልል በወላይታ ዞን በቦሎሶሶሬ ሁለት የምርጫ ክልል ገዥው ፓርቲን በመወከል ለፓርላማ እንደሚወዳደሩ ታወቀ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሚወዳደሩበት የምርጫ ክልል ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ተፎካካሪ የሚሆኑ ዕጩዎችን ያቀረቡት ፓርቲዎች ደግሞ አዲስ ትውልድ ፓርቲ (አትፓ)፣ መድረክና ሰማያዊ ፓርቲዎች ናቸው፡፡ በእነዚህ ፓርቲዎች አማካይነት ጠቅላይ ሚኒስትሩን ለመፎካከር የቀረቡት ደግሞ አትፓን በመወከል አርቲስት ደስታ ደአ፣ መድረክን የወከሉት አርሶ አደሩ አቶ ተስፋዬ ኃይሌና ሰማያዊ ፓርቲን የወከሉት ተማሪ ቀኙ ሴባ የተባሉ ዕጩዎች ናቸው፡፡ በ1987 እና በ1992 ዓ.ም. በተካሄዱ ምርጫዎች የደቡብ ክልል ምክር ቤት አባል የነበሩት አቶ ኃይለ ማርያም፣ ደቡብ ክልልን በምክትልነትና በፕሬዚዳንትነት አስተዳድረዋል፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ በ1997 ዓ.ም. ለፓርላማ ተወዳድረው የፓርላማ አባል ከሆኑ በኋላ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማኅበራዊ ጉዳዮች አማካሪ፣ የሕዝብ አደረጃጀትና ተሳትፎ አማካሪና በፓርላማ የመንግሥት ተጠሪ ሆነው መሥራታቸው አይዘነጋም፡፡ እንደገና በ2002 ዓ.ም. ተወዳድረው ፓርላማ ከገቡ በኋላ፣ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው ተሹመዋል፡፡ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ከዚህ ዓለም በሞት ከተለዩ በኋላ ከመስከረም 11 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ በጠቅላይ ሚኒስትርነት በማገልገል ላይ ይገኛሉ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሁን ለሦስተኛ ጊዜ ነው ለፓርላማ የሚወዳደሩት፡፡ በዚሁ የምርጫ ክልል ቦሎሶሶሬ ሦስት ደግሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ አቶ ተክለ ወልድ አጥናፉም እንዲሁ ገዥው ፓርቲን ወክለው፣ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለሚደረገው ምርጫ እንደሚወዳደሩ ለ