የጥራት ደረጃ ያጭበረበሩ ሁለት ቡና ላኪዎች በሕግ ሊጠየቁ ነው
- ሌሎች ስድስት ላኪዎች በማስጠንቀቂያ ታልፈዋል -ራሱን የቻለ የመጋዘን አገልግሎት ኢንተርፕራይዝ ሊቋቋም ነው ለውጭ ገበያ የሚቀርብ የቡና ምርት የጥራት ደረጃ በማጭበርበር የወደቀ የጥራት ደረጃ ያለው የቡና ምርት ከአገር ለማስወጣት የሞከሩ ሁለት ቡና ላኪዎች በሕግ እንዲጠቁ መወሰኑን የንግድ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ የሚኒስቴሩ የውጭ ንግድ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ያዕቆብ ያላ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለመንግሥት የወጪ አስተዳደር ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ነው በቡና ላኪዎቹ ላይ ስለተወሰነው ዕርምጃ ያሳወቁት፡፡ በንግድ ሚኒስቴር ቀጥተኛ ክትትል የሚደረግባቸው የግብርና ምርቶች የውጭ ንግድ ማስፋፊያ ሥርዓት አፈጻጸምና ውጤታማነት ላይ በ2004 ዓ.ም. በኦዲት የታየ ችግር በመኖሩ፣ ቋሚ ኮሚቴው ችግሩ በምን ዓይነት መንገድ እየተቀረፈ መሆኑን ለማወቅ ነው ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱን የጠራው፡፡ በ2004 ዓ.ም. ታዩ ከተባሉት ችግሮች መካከል ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ የግብርና ምርቶች የጥራት ደረጃ ጉድለት አገሪቱን በእጅጉ እየጐዳ መሆኑን፣ ወደ ውጭ ገበያ ለማቅረብ ከኢትዮጵያ ምርት ገበያ የሚገዙ የግብርና ምርቶች የኪሎ ጉድለት እንደሚታይባቸው፣ ግዥውን የፈጸሙ ላኪዎች የገዙትን የግብርና ምርት በጥራት ደረጃው እንደማያገኙት፣ ወደ ውጭ እንዲላክ የተዘጋጀ ቡና ዋጋ ውጭ አገር ተሽጦ ከሚገኘው ገቢ የሚንር መሆኑ በ2004 ዓ.ም. በዋና ኦዲተር ጄኔራል የተደረገው የክዋኔ ኦዲት ያስረዳል፡፡ ችግሩን በምን ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ባለፈው ረቡዕ በፓርላማው ቋሚ ኮሚቴ የተጠየቁት ሚኒስትር ዴኤታው አቶ ያዕቆብ፣ አብዛኞቹ ችግሮች መለየት መቻላቸውንና መቀረፋቸውን ገልጸዋል፡፡ ይሁን እንጂ አሁንም ጥቂት የሚባሉ ነገር ግን ተፅዕኖ ፈጣሪ የሆኑ ቡና ላኪዎች የቡና