በልማት “ማሳበብ” ከልማታዊ መንግስት አይጠበቅም!
በመንግስት “ሳንባ” መተንፈስ ለ“ቲቢ” ያጋልጣል ፖለቲካዊ ወጋችንን የምንጀምረው በቀልድ ነው፡፡ ግዴለም ባትስቁም አልቀየማችሁም፡፡ ፈገግ ካላችሁ መች አነሰኝ! (ኑሮ “ሃርድ” ሲሆን ሳቅም ይገግማል አሉ) ይልቅስ ሳልረሳው ቀልዱን ቶሎ ልንገራችሁ፡፡ - ፡፡ አንድ የሰው አገር ሰው (ፀጉረ ልውጥ ማለቴ አይደለም!) ከጅቡቲ እየተጫኑ ወደ አዲስ አበባ የሚገቡትን የመኪኖች መዓት በትዝብት ሲመለከት ይቆይና እነዚህ ሁሉ መኪኖች የት ነው የሚገቡት?” ሲል ይጠይቃል፡፡ የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊም (መሬት ይቅለላቸውና!) “የሌሎቹን አላውቅም…አይሱዙ ግን ገደል ነው የሚገባው” አሉ (አሉ ነው!) በነገራችሁ ላይ… በመዲናዋ የሚርመሰመሰው የመኪና ብዛት እኮ ከነዋሪው እኩል ሊሆን ትንሽ ነው የቀረው፡፡ አንዳንዴ ሳስበው ግን ባለሀብቱም ሆነ ሌላው ትንሽ ገንዘብ እጁ ላይ ከተረፈው ዝም ብሎ መኪና የሚያስጭን ነው የሚመስለኝ። (ጀት ለማስጫን አቅም የለችማ!?) እናላችሁ… የመዲናዋ ተሽከርካሪዎች ከህዝቡ በልጠው መፈናፈኛ ከማጣታችን በፊት “አራርቆ መግዛት” የሚል ፖሊሲ ቢቀረጽ ሸጋ ይመስለኛል፡፡ (“አራርቆ መውለድ” እንደሚባለው) ትራፊክ ፖሊስና መንገድ ትራንስፖርት ጥናት አላደረጉ ይሆናል እንጂ የመኪና አደጋ እንዲህ ህዝብ የሚፈጀው የተሽከርካሪው ቁጥር ያለቅጥ በዝቶ ሊሆን ይችላል እኮ! (“የመኪና ምጣኔ” ሳያስፈልገን አይቀርም!) እኔ የምላችሁ…ባለፈው ሳምንት የኢቴቪ “ዓይናችን” ፕሮግራም ላይ ከመንጃ ፈቃድ አወጣጥና የአሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ ት/ቤቶች አሰራር ጋር በተገናኘ የተጠየቁት የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ ሃላፊ የሰጡትን ምላሽ ሰምታችሁልኛል? ሃላፊዋ የተናገሩትን በአማርኛ ተርጉሞ ለነገረኝ (የገባው ካለ ማለቴ ነው) ወሮታ