የጠቅላይ ሚኒስትሩን የዕድገትና የልማት ጅማሮዎች ኢሕአዴግ ለሕዝብ ግንኙነት ሥራ አልተጠቀመበትም ተባለ
በታምሩ ጽጌ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ከትግል አጋሮቻቸው ጋር በመሆን ደርግን ከጣሉ ማግስት ጀምሮ፣ በአገር ዕድገትና ልማት ሥራ ላይ የተሰማሩ ቢሆንም፣ ኢሕአዴግ ለሕዝብ ግንኙነት ሥራ እንዳልተጠቀመበት አስተያየት ሰጪዎች እየገለጹ ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በ1986 ዓ.ም. በአማራና በኦሮሚያ የተለያዩ የገጠር ቀበሌዎች በመዘዋወር ያደርጉዋቸውን ጉብኝቶች የሚያስቃኝ ዘጋቢ ፊልም ሰሞኑን በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የተመለከቱት አስተያየት ሰጪዎች፣ ኢሕአዴግ በሕዝቡም ሆነ በተቀናቃኝ የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚደርስበትን ትችት የሚያስተባብል ሆኖ እንዳገኙት ተናግረዋል፡፡ ኢሕአዴግ በምርጫ ሰሞን “ልማት፣ ልማት የሚለው ሕዝቡን ለማታለልና ያልሠራውን ሥራ በመደርደር ነው፤” በማለትና በመግለጽ ሲቃወሙት የነበሩትን የውጭና የአገር ውስጥ ድርጅቶች ያስታወሱት አስተያየት ሰጭዎቹ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ እላይ ካለው የመንግሥት ባለሥልጣን እስከታችኛው አርሶ አደር ድረስ ለልማት ሲያደርጉት የነበረውን ጥረት ለሕዝብ ይፋ አለመደረጉ ለትችት እንዳጋለጠው ገልጸዋል፡፡ ሰሞኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሥልጣን ዘመናቸው የሠሩዋቸውን የቅርብ ጊዜና ከድል ማግስት ያደርጓቸው የነበሩትን የዕድገትና የልማት እንቅስቃሴዎች የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ሲያስተላልፍ የተመለከቱት አስተያየት ሰጭዎቹ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሠርተዋቸው ያለፉት ሥራዎች የበለጠ የሚያስወድዳቸውና ይቃወማቸው የነበረውን ሁሉ ተቃውሞውን እንዲያነሳ የሚያደርጉ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ኢሕአዴግ በተለይ በምርጫ ሰሞን እታች ወርዶ ቢሠራ ከዓለም አቀፎቹ ሂዩማን ራይትስ ዎች፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናልና ከሌሎች አገር አቀፍ ድርጅቶች ትችት ከመዳኑም በተጨማሪ፣ አብዛኛዎቹን የአገሪቱን ዜጐች የኢሕአዴግ ደጋፊ ሊያደርግ የሚያስችለው እንደነበር አውስተዋል፡