Sidama Bunna flying high
12ኛው ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ታላቁን የቡና ደርቢ በይርጋለም ዛሬ አስተናግዶ ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ቡናን 1ለ0 በመርታት በሊጉ አናት ላይ የሚያቆየውን ውጤት አስመዝግቧል። ሲዳማ ቡና በሜዳው እና በደጋፊው ፊት ያደረገውን ጨዋታ በበላይነት መወጣቱ በ5 የነጥብ ብልጫ የሊጉ መሪ እንዲሆን አስችሎታል። ሁለቱ ቡድኖች የመጀመሪያውን የጨዋታ ጊዜ ያለምንም ጎል ቢያጠናቅቁም ከእረፍት መልስ ሲዳማ ቡና ወሳኟን ጎል አስቆጥሯል። ጎሏም የሲዳማ ቡናን ጠንካራ ግስጋሴ ያስቀጠለች ሆናለች። ሲዳማ ቡና በ12 ጨዋታዎች 26 ነጥብ ይዟል። ኢትዮጵያ ቡና በአንጻሩ ነጥብ በመጣሉ ሊጉን ለመምራት የሚያደርገውን ጉዞ አስቸጋሪ አድርጎበታል። ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ወልድያ ተጉዞ ወልድያ ከነማን 3ለ0 በመርታት ወደ ሊጉ አናት ተጠግቷል። ጊዮርጊስ በመጀመሪያው ግማሽ አንድ እንዲሁም በሁለተኛው ግማሽ ሁለት ጎሎችን ከመረብ በማሳረፍ ነጥቡን በ11 ጨዋታዎች ወደ 21 በማሳደግ ሲዳማን በቅርብ ሩቅ ይከተላል። ተጋጣሚው ወልድያ ከነማ ደግሞ በወራጅ ቀጠናው መሰንበቱን አረጋግጧል። በሜዳው ሙገር ሲሚንቶን 1ለ0 ያሸነፈው ወላይታ ድቻ 20 ነጥብ በመያዝ በሊጉ ሶስተኛ ደረጃን መያዝ ችሏል። አዳማ ላይ የጎንደሩን ዳሽን ቢራ በተመሳሳይ 1ለ0 የረታው አዳማ ከነማ ወደ ሊጉ መሪዎች የሚያስጠጋውን ውጤት አስመዝግቧል። በወራጅ ቀጠናው የሚገኘውን እና አሰልጣኙን ያሰናበተው ሀዋሳ ከነማ ደግሞ ኤሌክትሪክን 2ለ1 በማሸነፍ የዓመቱን ሁለተኛ ድል አስመዝግቧል። ትናንት በተካሄዱ ሁለት የአበበ ብቂላ ስታዲዮም ጨዋታዎች ደግሞ መከላከያ ከንግድ ባንክ እንዲሁም ደደቢት ከአርባምንጭ በተመሳሳይ 1ለ1 በሆነ ውጤት ተጠናቋል። ምንጭ፦ www.ertagov.com