የቡና ንግድ ቀይ መብራት በርቶበታል
ሚኒስትሮች ተሰብስበዋል፡፡ የሚኒስትሮቹ ጠቅላይ አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ስብሰባውን ይመራሉ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ ሚኒስትሮችና ከዚያ በታች በተዋረድ የሥልጣን ዕርከን ላይ የሚገኙ 37 ሹማምንት ለስብሰባው ሲጠበቁ 25ቱ ተገኝተዋል፡፡ በሦስት ሚኒስቴሮች የኤክስፖርት አፈጻጸም ላይ በብሔራዊ ኤክስፖርት አስተባባሪውና የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ ሚኒስትር በአቶ አርከበ ዕቁባይ (የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ይዘዋል) ጠሪነት ለአምስት ሰዓት የዘለቀ ስብሰባ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤት ተካሂዷል፡፡ ስብሰባው ከጥቂት ወራት በፊት የተካሄደ ነው፡፡ ከመነጋገሪያ ነጥቦቹ አንዱ የሆነው የንግድ ሚኒስቴር የኤክስፖርት አፈጻጸም ነበር፡፡ ከዚህም ውስጥ ቡና ላይ ትኩረት አድርጎ፣ ሌሎች የግብርና ምርቶችንም ተመልክቷል፡፡ ‹‹በንግድ ሚኒስቴር ክትትል የሚደረግባቸው የግብርና ምርቶች የኤክስፖርት ዕቅድ አፈጻጸም በተያዘው ዕቅድ መሠረት ለማሳካት የተከተልነው የአሠራር ሥርዓትና የማኔጅመንት አመራር ለውጥ ያላመጣው በምን ምክንያትን እንደሆነ አጽንኦት ተሰጥቶት ቢታይ፤›› የሚል መነሻ ያሰፈረው የመወያያ አጀንዳ፣ ከዚህ ቀደም በኤክስፖርት ብሔራዊ አስተባባሪ ኮሚቴው በኩል የተሰጡ ማሳሰቢያዎችና የሥራ መመርያዎች ብዙም ለውጥ እንዳላመጡ ይገልጻል፡፡ ከቀረቡት ዝርዝር ነጥቦች መካከል ለአብነት መጥቀስ ቢያስፈልግ፣ ከዚህ ቀደም ኮሚቴው የኢትጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን፣ የንግድ ሚኒስቴር፣ የግብርና ሚኒስቴርና የፀጥታ አካላት በጋራ ተቀናጅተው በተለይ የቡና ኤክስፖርት ዕቅድ አፈጻጸምን ለማቀላጠፍ ይቻል ዘንድ፣ ቡና በብዛት ወደ ምርት ገበያ እንዲገባ በማድረግ የአቅርቦት መጠኑ እንዲጨምር የሚል መመርያ ሰጥቶ እንደነበር ያስታውሳል፡፡ ሆኖም ግን የተለየ ለውጥ አለመምጣቱን