አዲሱ የጉድጓድ ውሃ መቆፈሪያ ቴክኖሎጂ እና በሲዳማ ዞን ሁላ ወረዳ ነዋሪ የሆነው የአቶ በቀለ ፉኤ ታሪክ
አዲሱ የጉድጓድ ውሃ መቆፈሪያ ቴክኖሎጂ -ለመጠጥ ውሃ አቅርቦት ተደራሽነት አዲሱ የጉድጓድ ውሃ መቆፈሪያ ቴክኖሎጂ 50 ሜትር ጥልቀት ድረስ መቆፈር የሚያስችል ነው፤ ኑሮውን በውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ሥራ ላይ ያደረገው የ 42 ዓመቱ አቶ በቀለ ፉኤ በሕይወት ዘመኑ በርካታ ነገሮችን አይቷል። በተለይም ከሥራው ጋር በተያያዘ ብዙ ፈተና አሳልፏል። ወገቡን በገመድ ታስሮ ቁልቁል የጉድጓድ ውሃ ሲቆፈር መሬት ተደርምሶ አፈር ተጭኖት በሰዎች ዕርዳታ ከሞት ተርፏል። ጥልቀት ያለው ጉድጓድ ቆፍሮ ውስጥ እንዳለ አየር አጥሮት ራሱን ስቷል። ወገቡን ታስሮ ቁልቁል የተላከበት ገመድ ተበጥሶ ሕይወቱ አደጋ ላይ ወድቋል። በደቡብ ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት ሲዳማ ዞን ሁላ ወረዳ ነዋሪ የሆነው አቶ በቀለ እንጀራ ሆኖበት እንጂ የጉድጓድ ውሃ ቁፋሮ ሥራው በሞትና በሕይወት መካከል ያለ ነገር እንደሆነ ያምናል። የእለት ጉርሱን ከመሙላት አልፎ ቤተሰቡን የሚያስተዳድረው በእዚህ ሕይወትን የሚፈትን ሥራ ላይ ተሰማርቶ ነው። ሥራውን ለመተው ፍላጐት አለው። በርካታ ጊዜም የጉድጓድ ውሃ ቁፋሮ ሥራ እንዲሠራላቸው ጥያቄ ያቀረቡለትን ደንበኞቹን ጥያቄ ሳይቀበልም ቀርቷል። « የጉድጓድ ውሃ የሚቆፍሩ አባቶች ልጆቻቸውን ስመው ነው ቁፋሮ የሚጀምሩት። እኔም ልጆቼን ስሜ ተሰናብቼ ብዙ ጊዜ ሥራዬን ጀምሬያለሁ። ፈተና እያለፍኩ እዚህ ደርሻለሁ። አሁን እግዚአብሄር የተመሰገነ ይሁን ለእጅ ውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ወደጉድጓድ መግባት ቀርቶልኛል » ሲል ይናገራል። አሁን የአቶ በቀለ ሥራ አስጊነት ምን ዋስትና አግኝቶ ነው በቀለ ለአምላኩ ምሥጋናውን ለማቅረብ የበቃው ? ብለን ስንጠይቅ ቀላል በሆነ ቴክኖሎጂ በእጅ የሚሠራ የውሃ ጉድጓድ ለመቆፈር የሚያስችል መሣሪያ በመፈጠሩ ነው።