ኢኮኖሚውና ቢዝነሱ ‹‹ግሉኮስ›› ያስፈልገዋል
ኢኮኖሚያችንና የቢዝነስ እንቅስቃሴያችን እየፈዘዘ ነው፡፡ ቀዝቀዝ ብሏል፡፡ አተነፋፈሱ ጥሩ አይመስልም፡፡የገንዘብ እንቅስቃሴ እንደነበረው አይደለም፡፡ ክፍያዎች እየዘገዩ ናቸው፡፡ በባንኮችና በደንበኞች መካከል ጠንካራ ግንኙነት የለም፡፡ ባንኮቹ በተለይም የግል ባንኮች እየተዳከሙ ናቸው፡፡ በዚህ ምክንያት የገንዘብ እንቅስቃሴ ሙትት እያለ ነው፡፡ በውጭ ምንዛሪ ችግርና እጥረት ምክንያት በጣም የሚያስፈልጉ ዕቃዎች እንደተለመደው ከውጭ እየገቡ አይደለም፡፡ በጥቂቱ የመጡ ካሉም ዋጋቸው የማይቻል እየሆነ ነው፡፡ መንግሥት ራሱ የሚያስፈልገውን ፋይናንስ በሚፈልገው መጠንና ፍጥነት እያገኘ አይደለም፡፡ በፕሮጀክቶች ሒደትና አተገባበር የሚፈለገውን ያህል ዕድገት እያረጋገጠ አይደለም፡፡ ይህ ማለት ዕድገት ቆመ አይደለም፡፡ ዕድገት አሁንም አለ፡፡ በተፈለገው ጊዜ ሊዳሰስና ሊጨበጥ የሚፈለገው የገንዘብ መጠን ግን በእጁ እየገባ አይደለም፡፡ የውጭ ኢንቨስተሮች አስፈላጊውን ፈጣን መስተንግዶና አስተዳደር እያገኘን አይደለም እያሉ እያማረሩ ነው፡፡ የጀመርነው ኢንቨስትመንት ተቋረጠ፣ አሸንፋችኋል ከተባልን በኋላ እንደገና ጨረታ ይወጣል ተባልን፣ አቁሙ ተብለናል፣ መልስ የሚሰጠን አጣን እያሉ እያማረሩ ናቸው፡፡ ገንዘብ መደበቅና ማሸሽ እየተለመደ ነው የሚል አጀንዳ ወደ መድረክ እየመጣ ነው፡፡ ባንክ ከማስቀመጥ ይልቅ በእጅ መያዝ እየተመረጠ ነው፡፡ አገር ውስጥ ከማስቀመጥ ይልቅ ውጭ መላክ ተመራጭ ሆኗል እየተባለ ነው፡፡ አገር ውስጥ ባለው የውጭ ምንዛሪ ክምችት ላይ ተጨማሪ ጉልበት ሊፈጥር የሚገባው የውጭ ምንዛሪ ግኝትም ውጭ እንዲቀር እየተደረገ ነው፡፡ የገባ ካለም በጥቁር ገበያ እንደገና እንዲወጣ እየተደረገ በመሆኑ አገሪቱ ተጠቃሚ መሆን አልቻለችም፡፡ እኔ ንፁህ