አደናጋሪው የሕግ ቋንቋ ጉዳይ…
በውብሸት ሙላት የሕግ ቋንቋ በብዙ መልኩ የተቀዣበረ ነው፡፡ ቀዥባራነቱን አንዳንዶች እንደ ውበት ይወስዱታል፡፡ ሌሎች ደግሞ የሕግ ባለሙያዎች ብቻ እንደሚያውቁት የአስማት/የመተት ቋንቋ አድርገው ይቆጥሩታል፡፡ ሌላም ሌላም ይሉታል፡፡ ለማንኛውም በእንግሊዝኛ ተናጋሪ አገሮች ዘንድ የግልጽ ቋንቋ ተሟጋቾች እየተበራከቱ በመምጣታቸው የሕግ ማኅበረሰቡ ግልጽ ቋንቋ ይጠቀሙ ዘንድ የሚያበረታቱ፣ እንዲጠቀሙ የሚሞግቱ የቋንቋና የሕግ ባለሙያዎች እየተበራከቱ መጥተዋል፡፡ በአገራችን ግን ስለዚህ ጉዳይ ስለመነሳቱ ይህ ጸሐፊ አያውቅም፡፡ በመሆኑም ስለሕግ ቋንቋ አንዳንድ ነገሮችን አንስተን እንወያያለን፡፡ መነሻ ወግ አንድ በዕድሜ ገፋ ካሉ የእግሊዝኛ ቋንቋ መምህርና ደራሲ ጋር እያወጋን ነው፡፡ በሕይወታቸው ሦስት ጊዜ የእንግሊዝኛ አንድ ጊዜ የአማርኛ የፍትሐ ብሔር ሕግ ኮድ (መጽሐፍ) ገዝተዋል፡፡ አራቱንም መጻሕፍት ለሕግ ባለሙያዎች ሰጥተዋቸዋል፡፡ የስጦታቸው ምክንያት በልገስና ስሜት ሳይሆን ከገዟቸው በኋላ ሲያነቧቸው ሊገቧቸው ስላልቻሉ በብስጭት ነው፡፡ በእልህ ገዟቸው በብስጭት ሰጧቸው፡፡ እስካሁን ለምን ያነበቧቸው እደማይገቧቸው ግልጽ አልሆነላቸውም፡፡ አንድ የጓደኛዬ ጓደኛ ከሚንስትር መለስ ባለ ደረጃ ቱባ ባለሥልጣን ነው፡፡ ከቱባ ባለሥልጣን ሚስቱ ጋር በመጣላቱ በፍች ትዳራቸውን ሊያፈርሱ ሆኖ በሚስቲቱ አመልካችነት ጉዳዩ ተጀምሮ የፍችው አቤቱታ መጥሪያ ይደርሰዋል፡፡ በአቤቱታው የመጀመሪያ ገጽ የክሱ መግለጫ በሚለው ክፍል ላይ እንዲህ የሚሉ ዓረፍተ ነገሮች ተቀምጠዋል፡፡ “1. በሕግ ችሎታ የለሽም አልተባልኩም፡፡ 2. ጉዳዩ በይርጋ አልታገደም፤” የሚሉ ዓረፍተ ነገሮች ናቸው፡፡ ይህ ሁለተኛ ዲግሪ ያለው ቱባ ባለሥልጣን ሚስቱ እንፋታ ብላ ባቀረበችው አቤቱታ ላይ ከላይ የ