የዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ፈተናዎችና የሦስቱ ተዋንያን ሚና ሲገመገም
በጋዜጣው ሪፖርተር የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ የጀመረውን ውይይት ኅዳር 30 ቀን 2005 ዓ.ም. አስቀጥሎ ነበር፡፡ በተጠቀሰው ቀን ያካሄደው የውይይት ርዕስ ‹‹ወቅታዊው የአገራችን የፖለቲካ ሁኔታና የፖለቲካ ፓርቲዎች የመሰባሰብ ሚና›› የሚል ነበር፡፡ በዚህ ውይይት ላይ የፓርቲው የፖለቲካ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ሙላቱ ጣሰው ለፓርቲው አባላት የመወያያ ጽሑፍ አቅርበዋል፡፡ እሳቸው በኢትዮጵያ ሁሉም ዓይነት የዜጎች መብቶች የሚከበሩበትና ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል የሚኖርበት ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመገንባት፣ ባለፉት ዓመታት በተከታታይ የተደረጉት ጥረቶች ሁሉ ውጤት አላመጣም ይላሉ፡፡ በውይይቱ ላይ እነዚህ ሁሉ ጥረቶች ለምን ለውጥ እንዳላመጡ አቶ ሙላቱ ሲያብራሩ፣ ሦስት ተዋናዮችን በተወሰነ ደረጃ መመልከት አስፈላጊ መሆኑን በመጠቆም ማስረዳታቸውን ቀጠሉ፡፡ ሦስቱ ተዋንያን የተባሉት ገዥው ፓርቲ፣ ተቃዋሚዎችና ሕዝብ ናቸው፡፡ ገዥው ፓርቲ ገዥውን ፓርቲ (ኢሕአዴግ) ከትናንት እስከ ዛሬ ብለው አጠር አድርገው በተነተኑበት ክፍል የራሱን አገር አስገንጥሎ ዕውቅና የሰጠ፣ የአገሪቱን የባህር በር የዘጋ፣ የአገሪቱን ሉዓላዊነት ጥያቄ ውስጥ ያስገባ፣ የአገሪቱን ብሔራዊ ጥቅሞች አሳልፎ የሰጠና ፍትሐዊ የሀብት ክፍል የሌለበት አምባገነናዊ ሥርዓት ማስፈኑን፣ በጦርነት ወቅት የወረሳቸውን ንብረቶችና ሀብቶች በእጁ ይዞ የፓርቲ ኩባንያዎችን እያስፋፋ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ‹‹የገዥው ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች የአገሪቱን ሀብት በመቆጣጠር ላይ ናቸው፡፡ አገራችን ከበቂ በላይ ለም መሬትና ዓመቱን ሙሉ የሚፈሱ ወንዞች እያሏት፣ በምግብ ሰብል ራሳችንን ባለመቻላችን ሕዝባችን ለከፍተኛ ረሃብ ተዳርጓል፤›› ያሉት አቶ ሙላቱ