ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በይርጋዓለም ከተማ አዲስ ካምፓስ ከፈተ
ሀዋሳ (ኢዜአ)፦ የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የቅበላ አቅሙን ለማሳደግ በይርጋዓለም ከተማ በ55 ሚሊዮን ብር ወጪ ያስገነባው አዲሱ የአዋሳ ካምፓስ ትናንት ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀመረ፡፡ ካምፓሱን መርቀው የከፈቱት የደቡብ ክልል ርዕሰ መስተዳድርና የዩኒቪርሲቲው አስተዳደር ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ናቸው፡፡ የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ዮሴፍ ማሞ በምረቃው ሥነ ሥርዓት ላይ እንደገለጹት፤ የዩኒቨርሲቲውን የቅበላ አቅም ለማሳደግ ከሚካሄዱ የማስፋፊያ ግንባታዎች አንዱ አካል የሆነው አዲሱ የአዋሳ ካምፓስ በ65 ሄክታር ቦታ ላይ ያረፈ ነው፡፡ በ2002 ዓ.ም ተጀምሮ በአሁኑ ወቅት የተጠናቀቀው ይኸው ካምፓስ ለ800 ተማሪዎች የመኝታ አገልግሎት የሚሰጥ ዘመናዊ ህንፃ ፣ የመማሪያና ሌሎችም ክፍሎችን የያዘ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ካምፓሱ በአሁኑ ወቅት በአካውንቲንግ፣ በማኔጅመንት፣ በኢኮኖሚክስና፣ በኮፕሬቲቭስ ዘርፍ በመጀመሪያ ዲግሪ የተቀበላቸውን 580 ተማሪዎችን በመመዝገብ ለማስተማር መዘጋጀቱን ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም በዚሁ አዲስ ካምፓስ በ38 ሚሊዮን ብር ወጪ የተጀመሩ የአስተዳደር ቢሮዎች፣ የተማሪዎች መመገቢያ፣ ቤተመጻሕፍትና የመምህራን መኖሪያ ግንባታ በቅርቡ ተጠናቆ ለአገልግሎት እንደሚበቃ ዶክተር ዮሴፍ አመልክተው፤ የካምፓሱን የቅበላ አቅም በማገናዘብ ሌሎች የማስፋፊያ ግንባታዎች ለማካሄድ 320 ሚሊዮን ብር መመደቡን ጠቁመዋል፡፡ አዲሱን ካምፓስ እንዲከፈት ድጋፍ ላደረጉ ለክልሉ፣ ለሲዳማ ዞን፣ ለዳሌ ወረዳና ለይርጋዓለም ከተማ አስተዳደር፣ ለአካባቢው ማህበረሰብና ለሌሎችም ባለድርሻ አካላት ምስጋና አቅርበዋል፡፡ የደቡብ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እና የዩኒቨርሲቲው ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ካምፓሱን መርቀው ከከፈቱ በኋላ እንደ