ቡና በብትን እንዲላክ የወጣው መመርያ ነጋዴዎችን አደናግጧል
ከኅዳር 1 ቀን 2004 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ እንዲደረግ በንግድ ሚኒስቴር የወጣው መመርያ፣ ቡና በብትን በኮንቴይነር እንዲላክ የሚያሳስብ ነው፡፡ ቡናው በብትን መላኩ የሚያመጣው ጠቀሜታ ቢኖርም አነስተኛ ላኪዎችን፣ የቡና ደረጃዎችንና በይበልጥ ደግሞ የውጭ አገር የቡና ገዢዎችን ነባራዊ ሁኔታና ፍላጎት ከግምት ያላስገባ መሆኑን በመጥቀስ ነጋዴዎች ተችተውታል፡፡ አንዳንዶችም በአጠቃላይ የአገሪቱ የቡና ኤክስፖርት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ የሚያሳርፍ መሆኑን በመግለጽ መመርያው በቶሎ እንዲሻሻል ጠይቀዋል፡፡ ነጋዴዎች ከዚህ ቀደም በጆንያ እየሞሉ በኮንቴነር የሚልኩበት አሠራርን በብትን ኮንቴይነሩ ውስጥ በሚዘጋጅ የብትን ቡና መሙያ ከረጢት ተዘጋጅቶለት እንዲላክ በመመርያ መወሰኑ አንዳንድ ነጋዴዎችን አስደንግጧል፡፡ አንዳንዶችም በጆንያ የላኩት ቡና ከጂቡቲ ወደብ ተመላሽ እንደተደረገባቸው ለሪፖርተር የደረሱ ጥቆማዎች ያመለክታሉ፡፡ የቡና ጥራት መጓደል እንደ ጃፓን ያለውን ሰፊ ገበያ ካሳጣ በኋላ መንግሥት የተለያዩ ዕርምጃዎችን እየወሰደ ቆይቶ፣ ለጥራት ብቻ ሳይሆን ለቡና ደኅንነትና ለወጪ ቁጠባ ተገቢ ነው ያለውን የቡና አላላክ ዘዴን በመመርያ ለውጧል፡፡ ቡና በብትን ቢላክ ሊያስገኝ የሚችለውን ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ በመተንተን የብትን ቡና አላላክን የሚያቀነቅኑት አቶ ግርማ ቡታ ናቸው፡፡ በአካካስ ሎጂስቲክስ ኩባንያ የኤክስፖርትና የመርከብ አገልግሎት ኃላፊ የሆኑት አቶ ግርማ፣ ምንም እንኳ በብትን ቡናን መላኩ በሌላው ዓለም የተለመደና ኢትዮጵያ እጅግ ኋላ የቀረችበት ቢሆንም፣ ንግድ ሚኒስቴር የሚመለከታቸውን ባለድርሻ አካላት ሳያወያይ መመርያውን ማውጣቱ በተለይ በጆንያ መላክ ያለባቸውን ነጋዴዎች እንደሚጐዳቸው አስረድተዋል፡፡ በብትን መላክ ማለት በኮንቴይነር ውስጥ በሚዘጋጅ ትልቅ