የሃዋሳ ዩንቨርሲቲ ግማሽ ቢሊየን ብር በሚሆን ወጭ አዲስ የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሊያስገነባ ነው
አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 26 (ኤፍ ቢ ሲ) የሃዋሳ ዩንቨርሲቲ ግማሽ ቢሊየን ብር በሚሆን ወጭ አዲስ የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሊያስገነባ ነው። በአሁኑ ወቅት የኢንስቲትዩቱን ግንባታ ለማስጀመር የሚያስችል ቅድመ ዝግጅት የተጠናቀቀ ሲሆን ስራውም በአንድ ወር ውስጥ ይጀመራል ተብሏል። ግንባታው የተማሪዎች ማደሪያና የመማሪያ ክፍሎችን ጨምሮ ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ ህንፃዎችን ያካተተ ነው። በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ የኢንስቲትዩቱ ግንባታ ሲጠናቀቅ 17 ሺ የነበረውን የዩኒቨርሲቲውን የተማሪዎች ቅበላ አቅም ወደ 30 ሺ ከፍ እንደሚል በዩንቨርሲቲው የግንባታ ዘርፍ ዳይሬክተር አቶ ደንበሹ ኔኤሬ ለኤፍ ቢ ሲ ተናግረዋል። እንደ ባልደረባችን ጥላሁን ካሳ ዘገባ የሃዋሳ ዩንቨርሲቲ ባለፉት 3 አመታት በ480 ሚሊየን ብር ሲያካሂድ የነበረውን የማስፋፊያ ግንባታ ሙሉ በሙሉ አጠናቋል።