የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በመጪው የትምህርት ዘመን ከአምስት ሺ በላይ አዲስ ተማሪዎችን ለመቀበል ዝግጁ መሆኑን አስታወቀ
አዲስ አበባ፣ ሀምሌ 16 2003 (ኤፍ ቢ ሲ) የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በመጪው የትምህርት ዘመን ከአምስት ሺ በላይ አዲስ ተማሪዎችን ለመቀበል ዝግጁ መሆኑን አስታወቀ። ዩኒቨርሲቲው በትምህርት ዘመኑ ከሚቀበላቸው ተማሪዎች 70 በመቶዎቹን በሳይንስና ቴክኖሎጂ ቀሪዎቹ ደግሞ በማህበራዊ ሳይንስ ዘርፎች ለማሰልጠን ነው የተዘጋጀው። አዲስ ለሚቀበላቸው ተማሪዎች በ540 ሚሊዮን ብር ከተጀመሩት 33 ነባር የማስፋፊያ ፕሮጀክቶች አብዛኛዎቹ ተጠናቀው ለአገልግሎት መዘጋጀታቸውንም ገልጿል። በየትምህርት ዘርፉ የሚያስተምሩ መምህራንና መጻህፍት ማሟላትን ጨምሮ ሌሎችም ለመማር ማስተማሩ ስራ የሚያስፈልጉ ዝግጅቶች ተጠናቀዋል። ዩኒቨርሲቲው ለተጨማሪ የማስፋፊያ ፕሮጀክቶች ግንባታ ማስፈጸሚያም ከ470 ሚሊዮን ብር በላይ መመደቡንም አስታውቋል። ዩኒቨርሲቲው በአሁኑ ወቅት በመደበኛና በተከታታይ የትምህርት ፕሮግራሞች 23 ሺ የሚጠጉ ተማሪዎችን በማስተማር ላይ እንደሚገኝ የኢዜአ ዘገባ ያመለክታል።