የኢትዮጵያ ካርታ ስራ ኤጀንሲ የሰራውን የሲዳማዋ በንሳን ጨምሮ የአስር ከተሞችን ካርታ አስረከበ
ሀዋሳ መስከረም 29/2010 የኢትየዮጵያ ካርታ ስራ ኤጀንሲ በደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል ለሚገኙ 10 መካከለኛ ከተሞች ካርታ ሰርቶ አስረከበ፡፡
ኤጀንሲው ካርታውን ያስረከበው ትናንት በሀዋሳ ከተማ ለክልሉ ከተማ ልማትና ቤቶች ቢሮ ነው፡፡
ርክክቡ የተካሄደው ለአስሩ ከተሞች የቅየሳ፣ የጥራት ቁጥጥር፣ የመስመርና ሌሎች ጉዳዮችን ማሳያ በማካተት ካርታ ለመስራት መጋቢት 2008 ዓ.ም ከክልሉ ጋር በተፈጸመው ውል መሰረት መሆኑን በኤጀንሲው የፕላንና ፕሮጀክት ዝግጅትና ግምገማ ዋና ዳይሬክተር አቶ ተፈሪ ዋቅቶላ ገልጸዋል፡፡
የካርታው ስራ 179 ስኩዌር ኪሎ ሜትር የሸፈነ ሲሆን ከ14 ሚሊየን በላይ ብር ወጪ ተደርጎበታል ዳይሬክተሩ እንዳመለከቱት፡፡
የክልሉ ከተማና ቤቶች ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ይልማ ሱንታ በርክክቡ ወቅት እንደገለጹት ካርታው ለከተሞች እድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ አለው፡፡
ካርታው የተሰራላቸው ከተሞች አለታ ወንዶ፣ ሺንሺቾ፣ ዱራሜ፣ አረካ፣ ለኩ፣ ዳዬ በንሳ፣ ሀደሮ፣ ሳውላ፣ ተርጫና ይርጋጨፌ ናቸው ፡፡
ምንጭ፦ ኢዜኣ
Comments
Post a Comment