የአፈ ጉባዔው ስንብት

አፈ ጉባዔ አባዱላ ገመዳ በኢትዮጵያ ባልተለመደ ሁኔታ ሥልጣናቸውን በፈቃዳቸው ለመልቀቅ ጥያቄ ማቅረባቸውን ይፋ ከተደረገ በኋላ በርካታ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት፣ የውጭ ከፍተኛ ዲፕሎማቶችና ሌሎችም የስንብት ሰላምታ ሰኞ መስከረም 29 ቀን 2010 ዓ.ም. ከቀትር በኋላ በፓርላማ ሲያቀርቡላቸው ተስተውሏል፡፡
የአፈ ጉባዔው ስንብትአፈ ጉባዔ አባዱላ ሥልጣናቸውን ለመልቀቅ ጥያቄ ማቅረባቸውን ቅዳሜ መስከረም 27 ቀን 2010 ዓ.ም. ሪፖርተር በድረ ገጹ መዘገቡ የሚታወስ ሲሆን፣ በማግሥቱ እሑድ መስከረም 28 ቀን 2010 ዓ.ም. አመሻሽ ላይ ግን ራሳቸው አፈ ጉባዔው ለአገር ውስጥ ሚዲያዎች ይፋ አድርገዋል፡፡
‹‹አሁን በደረስኩበት ደረጃ በዚህ ኃላፊነት ለመቀጠል የማያስችሉኝ ሁኔታዎች ስላሉና ፍላጎቱም ስለሌለኝ ለመልቀቅ ድርጅቴንና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን ጠይቄያለሁ፤›› ሲሉ አፈ ጉባዔው ተናግረዋል፡፡
በማግሥቱ የሕዝብ ተወካዮችና የፌዴሬሽን ምክር ቤቶች ሦስተኛ ዓመት የሥራ ዘመናቸውን በጋራ ስብሰባ በጀመሩበት ወቅት፣ አፈ ጉባዔ አባዱላ ስብሰባውን በማስጀመር ሲመሩ ነበር፡፡
የሁለቱ ምክር ቤቶች የጋራ ስብሰባ ከተጠናቀቀ በኋላ አፈ ጉባዔ አባዱላ ገመዳን ከመድረክ በስተጀርባ የሚሰናበቱ የምክር ቤቱ አባላት፣ ለረጅም ዓመታት ላበረከቱት ጉልህ አስተዋጽኦ ሲያመሠግኗቸው ተሰምቷል፡፡
የአገሪቱ የሃይማኖት አባቶች፣ የውጭ ዲፕሎማቶች፣ እንዲሁም ከፍተኛ ባለሥልጣናት ማለትም የብአዴን አመራሮችና የክልል ፕሬዚዳንቶች ሲሰናበቷቸው ተስተውሏል፡፡
አፈ ጉባኤው ለመልቀቅ ምክንያት የሆናቸውን ወደፊት እንደሚገልጹ ቢያስታውቁም፣ የተለያዩ መላምቶች እየተወሱ ነው፡፡ ከእነዚህም መካከል በሶማሌና በኦሮሚያ ክልሎች መካከል የተከሰተው ግጭት ሊሆን ይችላል የሚሉ አሉ፡፡ በሌላ በኩል በቴሌቪዥን በሰጡት መግለጫ የመከፋት ገጽታ ይታይባቸዋል የሚሉ ደግሞ በዚህ ኃላፊነት ለመቀጠል የሚያስችሉኝ ሁኔታዎች የሉም ማለታቸውን፣ ካሁን በኋላ የፌዴራል መንግሥት ኃላፊነት ለመቀበል እንደማይፈልጉ ማሳያ ነው ይላሉ፡፡ ይህም ሆኖ ግን እሳቸው ወደፊት እገልጸዋለሁ የሚሉትን በትዕግሥት መጠበቅ ይሻላል የሚሉም አልጠፉም፡፡
አፈ ጉባዔ አባዱላ ከዚህ በኋላ የምክር ቤቱ አባል ሆነው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል፡፡ በምክር ቤቱ የሥራ ዘመን ከሚቀርቡ የመጀመርያዎቹ አዋጆች መካከል ኦሮሚያ በአዲስ አበባ ላይ ያላትን ሕገ መንግሥታዊ ጥቅም መወሰን መሆኑ ይታወቃል፡፡
ምንጭ፦ ሪፖ ተር 

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር