የሲዳማ ማይክሮ ፋይናንስ ተቋም በዝቅተኛ ኑሮ የሚገኙ ሰዎችን ሕይወት እየታደገ መሆኑን አንድ ጥናት አመለከተ
ሀዋሳ ነሀሴ 6/2009 የሲዳማ ማይክሮ ፋይናንስ ተቋም በዞኑ በዝቅተኛ ኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ሕይወት ለማሻሻል የሚያደርገው ጥረት አበረታች መሆኑን አንድ ጥናት አመለከተ።
ጥናቱ በሀዋሳ እና በሊቨርፑል ዩኒቨርሲቲዎች ትብብር የተካሄደ ሲሆን ተቋሙ ያለበትን የመረጃ አያያዝና የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ጉድለት ፈትሾ ለመፍታት መትጋት እንደሚጠበቅበት ምክረ ሀሳብ ለግሷል፡፡
ጥናቱ በሲዳማ ዞን በሚገኙ ስምንት ወረዳዎች የተካሄደ ሲሆን 397 የማይክሮ ፋይናንስ ተቋሙ ተጠቃሚ አባላትን በመረጃ ሰጭነት አሳትፏል።
የሀዋሳ እና በእንግሊዝ የሊቨርፑል ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ቡድን መሪ ዶክተር ከንባታ ባንጋሶ ጥናቱን መሰረት በማድረግ እንደገለጹት ተቋሙ በዞኑ የሚገኙ ድሆችን ሕይወት የማሻሻል ሚናውን በአግባቡ እየተወጣ ነው፡፡
የተቋሙ አብዛኞቹ ተጠቃሚዎች "ተቋሙ ለድሆች የወገነ ውሳኔ እንደሚሰጥና በሚያገኙት የብድርና ቁጠባ አገልግሎት ዓመታዊ ገቢያቸው ከ20 እስከ 30 ሺህ ብር እንደሚደርስ ምላሽ ሰጥተዋል " ሲሉ መግለጻቸውን ተናግረዋል፡፡
ተጠቃሚቹ በሚወስዱት የገንዘብ ብድር ሰርተው ከመለወጥ ባለፈ በማህበራዊ ኑሮአቸውና በኢኮኖሚ ደረጃቸው መሻሻል በማሳየታቸው በማህበረሰቡ ዘንድ ያላቸው ተቀባይነት ከፍ እያለ መምጣቱን ጥናቱ አሳይቷል ።
ብድር ከጠየቁ ተጠቃሚዎች ውስጥ 97 ከመቶ የሚሆኑት ብድር ማግኘታቸውንና የመመለስ አቅማቸውም 98 በመቶ መድረሱን ጥናቱ አሳይቷል።
በተጨማሪም 84 በመቶ የሚሆኑት የአገልገሎቱ ተጠቃሚዎች ወንዶች መሆናቸው በሴቶች ተሳትፎ ክፍተት ያለበት መሆኑ ጥናቱ መጠቆሙን ገልጸዋል።
የሲዳማ ማይክሮ ፋይናንስ በ1998 ዓ.ም ዳግም የተቋቋመና አንድ ሺህ አባላት እንዳሉት ታውቋል።
ምንጭ
Comments
Post a Comment