ከሬዲዮና ከቴሌቪዥን በተጨማሪ ድረገፆችን ለመቆጣጠር አዲስ ህግ ተዘጋጀ ተባለ

በኢንተርኔት የሚሰራጩ ፅሁፎችን፣ ምስሎችንና ቪዲዮዎችን ለመቆጣጠር ታስቧል 
የግል የሬዲዮ ጣቢያዎች ፈርሰው ከመንግስት ቻናል እንዲከራዩ ለማድረግ ታቅዷል

     የሬዲዮና የቴሌቪዥን ስርጭቶችን ለመቆጣጠር ከስምንት ዓመት በፊት በታወጀው ህግ ላይ አዳዲስ ቁጥጥሮችን የሚጨምርና እንዲሁም የኢንተርኔት ስርጭቶችንና ድረገፆችን የሚያካትት ህግ ተዘጋጀ፡፡ 
ከተለያዩ የሚዲያ ተቋማት ጋር ከትናንት በስቲያ ሃሙስ ውይይት የተካሄደበት ረቂቅ ህግ፣ ነባሩ አዋጅ ውስጥ የሰፈሩ የባለቤትነትና የፈቃድ አሰጣጥ ቁጥጥሮችን የሚዘረዝር ሲሆን፤ በኩባንያ መልክ እንጂ በግለሰብ የሬዲዮ ወይም የቴሌቪዥን ድርጅት ማቋቋም እንደማይቻል ይጠቅሳል፡፡ የዝምድና ወይም የጋብቻ ግንኙነት ያላቸው ሰዎች ለብቻቸው ባለአክሲዮን የሆኑበት ኩባንያ ፈቃድ እንደማይገኝም ተደንግጓል፡፡ 
ምንም እንኳ እስከዛሬ ተግባራዊ ባይሆንም በ1999 ዓ.ም በወጣው ህግ፣ የግል የቴሌቪዥን ጣቢያ ለማቋቋም ፈቃድ እንደሚሰጥ ተገልፆ የነበረ ሲሆን፤ አሁን በተረቀቀው ህግ ግን የቴሌቪዥን ጣቢያ በግል ማቋቋም እንደማይቻል ይደነግጋል፡፡ 
መንግስት የቴሌቪዥን ማሰራጫ ኔትዎርክ እንደሚዘረጋ የሚገልፀው ይሄው አዲስ አዋጅ፤ የግል ኩባንያዎች ከመንግስት ቻናል እየተከራዩ ለመስራት ማመልከትና ፈቃድ መጠየቅ ይችላሉ ይላል፡፡ 
የግል ኩባንያዎች ለጊዜው የራሳቸው የሬዲዮ ጣቢያ ለማቋቋም ፈቃድ የሚያገኙበት እድል ሊኖር እንደሚችል አዲሱ ህግ ይጠቁማል፡፡
 ወደፊት ግን በግል ባቋቋሙት የማሰራጫ ጣቢያ ሳይሆን ከመንግስት የማሰራጫ ጣቢያ ቻናል እየተከራዩ እንዲሰሩ ይደረጋል ተብሏል፡፡ ለዚህም መመሪያ እንደሚዘጋጅ በረቂቁ ህግ ተጠቅሷል፡፡  
በረቂቁ ህግ ከተካተቱ 60 አንቀፆች መካከል አብዛኞች በሬዲዮና በቴሌቭዥን ስርጭት ቁጥጥር ላይ ያተኮሩ ሲሆን፤ በኢንተርኔት የሚሰራጩና በድረገፅ የሚቀርቡ መረጃዎችን ለመቆጣጠር የታቀዱ ሦስት አንቀፆች ተጨምረውበታል፡፡ የሬዲዮና የቴሌቪዥን የግል ድርጅቶች ስለዲሞክራሲና ስለ ኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች የመዘገብ ግዴታ በህጉ የተጣለባቸው ሲሆን፤ በኢንተርኔትና በድረገፅ የሚሰራጩ መረጃዎች እንዲህ አይነት ግዴታ ባይኖርባቸውም ትክክለኛነታቸው ያልተረጋገጡ መረጃዎችን ማቅረብና ሌሎች በአንቀፅ 33 የተዘረዘሩ ድርጊቶችን ከፈፀሙ ተጠያቂ እንደሚሆኑ ረቂቅ ህጉ ይገልፃል፡፡ 
አመፅና፣ ግጭትና ጦርነት መቀስቀስ፣ እንዲሁም የሰውን ስምና ነፃነትን የሚያጠፋ መረጃ ክልክል መሆኑን የሚዘረዘረው አዲሱ ህግ፤ ምን ማለት እንደሆነ በግልጽ ባይብራራም የሃይማኖትን፣ የዘርን፣ የፆታን ክብር መንካት ክልክል ነው ይላል፡፡ 
በደፈናው ስነምግባርን የሚፃረርና የልጆችን አስተሳሰብ ወደአልተፈለገ አቅጣጫ እንዲያዘነብል መገፋፋትም ህገወጥ መሆኑን ይገልፃል፡፡
 እንደ ፌስቡክ እና ቲዊተር የመሳሰሉትን ጨምሮ አብዛኞቹ ድረገፆች በውጭ አገር የሚገኙ በመሆናቸው እንዴት ሊቆጣጠራቸው እንዳሰበ ሲጠቁም፣ በፅሁፍ ማስጠንቀቂያ እንደሚሰጥና ድረገፁ ከሚገኝበት አገር መንግስት ጋር በመተባበር እርምጃ እንደሚወስድ ህጉ ይገልፃል፡፡ 
ብዙዎቹ ድረገፆች በሚገኙበት በአሜሪካ “ሃሰት አሰራጨህ ወይም ወዳልተፈለገ አቅጣጫ ትገፋፋለህ” የሚል የአስተሳሰብ ቁጥጥር እንደሌለ ይታወቃል፡፡  
ወሬው የኣዲስ ኣድማስ ጋዜጣ ነው

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር