የእንግሊዝ መንግሥት ለኢትዮጵያ ያዘጋጀውን የደኅንነት ማኔጅመንት ፈንድ አቋረጠ

‹‹ፈንዱ የተቋረጠው ከአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ጋር በተገናኘ አይደለም›› ዲኤፍአይዲ
በእንግሊዝ መንግሥት ገንዘብ ለኢትዮጵያ የደኅንነት ኃላፊዎች ይሰጥ የነበረው የደኅንነት ማኔጅመንት ፕሮግራም ተቋረጠ፡፡
ሪፕሪቭ የተባለ ነፃ የሕግ አገልግሎት የሚሰጥ የእንግሊዝ ኩባንያና ሌሎች የሰብዓዊ መብት አቀንቃኞች፣ ካለፈው ዓመት አጋማሽ ጀምሮ የእንግሊዝ መንግሥት ይህንን ፕሮግራም እንዲያቋርጥ ግፊት ሲያደርጉ ነበር፡፡ 
እነዚህ ወገኖች ይህንን ግፊት የጀመሩት የኢትዮጵያ መንግሥት በልማት ምክንያት ዜጐችን ከመኖሪያ አካባቢያቸው ያፈናቅላል በሚል ክስ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የግንቦት ሰባት ጸሐፊ የሆኑት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በየመንና በኢትዮጵያ የፀጥታ ኃይሎች፣ ባለፈው ሐምሌ 1 ቀን 2006 ዓ.ም. ወደ ኤርትራ ለመጓዝ የመን ሰንአ አውሮፕላን ማረፊያ በቁጥጥር ሥር ውለው ወዲያውኑ ለኢትዮጵያ መንግሥት ከተላለፉ በኋላ፣ በእንግሊዝ መንግሥት ላይ ጫናው እንዲጠናከር ሲጥሩ ነበር፡፡
አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ አሁን ያለውን የኢትዮጵያ መንግሥት በኃይልም ሆነ በተገኘው አማራጭ ለመለወጥ የሚታገለው የግንቦት ሰባት አመራር ይሁኑ እንጂ፣ ዜግነታቸው እንግሊዛዊ መሆኑ ተጨማሪ ግፊት ይፈጥራል ብለውም ነበር፡፡
እሳቸው በቁጥጥር ሥር ከዋሉ በኋላ በእንግሊዝ መንግሥት ላይም ሆነ በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ከፍተኛ ግፊት ከሚያደርጉት መካከል፣ መቀመጫውን ለንደን ያደረገው ነፃ የሕግ አገልግሎት የሚሰጠው ተቋም የሆነው ሪፕሪቭና የአውሮፓ ኅብረት የሰብዓዊ መብት ኮሚቴ ይገኙበታል፡፡
የሪፕሪቭ የሕግ ዳይሬክተር ቲኔክ ሀሪስ በነሐሴ ወር ለእንግሊዝ መንግሥት ዓለም አቀፍ ትብብር ሚኒስትር ጀስቲገን ግሪንግ በጻፉት ደብዳቤ፣ ‹‹የእንግሊዝ ዜግነት ያለውን ግለሰብ ላገተውና ቶርቸር በማድረግ ለሚጠረጠረው የኢትዮጵያ መንግሥት ኃላፊዎች ይህንን ፕሮግራም መስጠት ተገቢ ነው ወይ? ተገቢ ነው ብለው ካላመኑ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እስካልተፈቱ ድረስ ምን ዕርምጃ ሊወስዱ እንደሚችሉ ቢያሳውቁን?›› በማለት ጥያቄ አቅርበው ነበር፡፡
የአውሮፓ ኅብረት የሰብዓዊ መብት ጉዳዮች ኮሚቴ ባለፈው መስከረም ወር ባካሄደው ጉባዔው በአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እስር ላይ የእንግሊዝ መንግሥት ምንም ዓይነት ጫና አለማሳደሩን በመውቀስ አስፈላጊ ነው የተባለ ውሳኔ በኢትዮጵያ ላይ ለማሳለፍ የሁለት ወራት ጊዜ ቀጠሮ ወስዶ መበታተኑን መዘገባችን ይታወሳል፡፡
ይህ ጫና ባለበት በአሁኑ ወቅት የእንግሊዝ መንግሥት ዲፓርትመንት ፎር ኢንተርናሽናል ዴቨሎፕመንት (ዲኤፍአይዲ) ለኢትዮጵያ የደኅንነት ኃላፊዎች ይሰጥ የነበረውን የደኅንነት ማኔጅመንት ፕሮግራም አቋርጧል፡፡ 
ፕሮግራሙ የተመረጡ የኢትዮጵያ የደኅንነት ኃላፊዎች በእንግሊዝ አገር በደኅንነት ማኔጅመንት የማስትሬት ዲግሪያቸውን እንዲሠሩ የሚያግዝ ነበር፡፡ 
የፕሮጀክቱ አጠቃላይ ወጪ ወደ 70 ሚሊዮን ፓውንድ ሲሆን፣ ለመጀመሪያው ዙር ፕሮግራም ሁለት ሚሊዮን ፓውንድ ያስፈልግ ነበር፡፡ 
ለዚህ ዓመት ተይዞ የነበረው የሁለት ሚሊዮን ፓውንድ ወጪ ለአጠቃላይ ፕሮግራሙ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
የዲኤፍአይዲ የኢትዮጵያ ቢሮ ጉዳዩን በተመለከተ ከሪፖርተር በኢሜይል ለቀረበለት ጥያቄ ፕሮግራሙ መቋረጡን አረጋግጧል፡፡ ነገር ግን ምክንያቱ ከአቶ አንዳርጋቸው ጋር ግንኙነት እንደሌለው አስታውቋል፡፡ 
‹‹ፕሮግራሙ የተቋረጠው የእንግሊዝ መንግሥት ለፕሮግራሙ የሚያወጣውና የሚያገኘው ምላሽ (ኢንቨስትመንት ሪተርን) የሚጣጣሙ ባለመሆናቸው ነው፤›› በማለት በደፈናው መልሷል፡፡

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር