የኢትዮጵያን ቡና ዘመናዊ በሆነ መንገድ ለውጪ የሚያቀርብ ድርጅት ስራ ሊጀምር ነው
አዲስ አበባ ፣ መጋቢት 23 ፣ 2006 (ኤፍ.ቢ.ሲ.) የኢትዮጵያን ቡና ዘመናዊ በሆነ መንገድ ለውጪ ገበያ የሚያቀርብ ድርጅት በይፋ ስራ ሊጀምር ነው።
''ሜላንዥ ኮፊ ሮሰተር'' የተባለው ይህ ድርጅት የተፈጨ የኢትዮጵያ ቡና ዘመናዊ በሆነ መንገድ ለዓለም ገበያ የሚያቀርብ ሲሆን፥ በቅርቡ በይፋ ስራ እንደሚጀምርም ነው የተነገረው።
በሙከራ ደረጃ ባለፈው ዓመት ወደ ስራ መግባቱን የሚናገሩት የድርጅቱ መስራችና ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ካሳ፥ ስታርባክሰ በሚባለው አለም አቀፍ የቡና ገዢ ድርጅት ለበርካታ አመታት በሀላፊነት ሲሰሩ መቆየታቸውን ገልፀዋል።
ድርጅቱ የአገሪቱን ጥራቱን የጠበቀ ቡና በመግዛት እ.ኤ.አ. የ2013 ምርት በሆኑ ዘመናዊ የመቁያና የመፍጫ መሳሪያዎች በመጠቀም አለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ቡና ወደ ውጭ አገራት እየላከ ይገኛልም ብለዋል።
በተለይም ለበርካታ አመታት ከኢትዮጵያ ተጓጉዞ በስታርባክስ ድርጅት ውስጥ የሚገዛው የኢትዮጵያ ቡና መጠን በግዢ ከሌሎች አገራት ያነሰ መሆኑ ድርጅቱን ለሟቋቋም እንዳነሳሳቸው ተናግረዋል።
ወደ አገራቸው በመምጣትም በ3 ሚሊዮን ብር ሜላንዥ ኮፊ ሮስተር የተባለ ድርጅት መስረተዋል።
አቶ ሰለሞን ደርጅቱ በአመት 20 ሺህ ቶን ቡና ወደ ውጭ ለመላክ እቅድ እንዳለውና ባለፉት ስድስት ወራት 5 ሺህ ቶን ቡና መላኩን አስታውቀዋል።
ድርጅቱ ለአገሪቷ የውጭ ምንዛሪ በማምጣትና ቡናን በአለም ገበያ ሽያጭ ከፍ በማድረግ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ የጠቆሙት ዳይሬክተሩ፥ ቡናን ከማቅረብ በተጨማሪም የቡናውን ጣእም ደረጃውን በጠበቀ ሁኔታ ለተጠቃሚዎች እንዲቀርብ ስልጠና እየሰጠ ነው ብለዋል።
ዳይሬክተሩ አክለውም ድርጅቱ የፊታችን ሀሙስ ስራውን ለህዝብ እንደሚያስተዋውቅ ተናግረዋል።
ምንጭ ፦ ኢዜአ
Comments
Post a Comment