ሂውማን ራይትስ ዎች በኢትዮጵያ የፖለቲካ ምህዳሩ ይበልጥ ጠቧል አለ

መንግስት፤ ተቋሙ የተቃዋሚዎች የፕሮፖጋንዳ ማስፈፀሚያ ነው
“በኢትዮጵያ የነፃ ሚዲያ ህልውና አደጋ ላይ ነው”
“በኤርትራ የመብት ጥያቄ ማንሳት ነውር ሆኗል” ብሏል

የኢትዮጵያ መንግስት የዜጐችን  ሰብአዊ መብት በስፋት ይጥሳል በማለት ተደጋጋሚ ወቀሳና ስሞታ የሚያቀርበው ሂውማን ራይትስ ዎች የተሰኘው አለማቀፍ የመብት ተቋም፤  ሰሞኑን ይፋ ባደረገው አመታዊ ሪፖርቱ፣ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ነፃነት ይበልጥ መጥበቡንና የነጻ ሚዲያ ህልውና አደጋ ላይ መውደቁን ገለፀ፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ የተቋሙን ሪፖርት ያጣጥላል፡፡ በአገሪቱ ውስጥ የፖለቲካ ነፃነትና የፖለቲካ እንቅስቃሴ የማካሄድ እድል (የፖለቲካ ምህዳር) እየጠበበ የመጣው ከምርጫ 97 በኋላ መሆኑን የገለፀው ሂውማን ራይትስ ዎች፤ ከዚያ ወዲህ በመንግስት የፀደቁትን የፀረ - ሽብር እና የበጐ አድራጐት ማህበራት አዋጆችን በምሳሌነት ጠቅሷል፡፡ በፀረ - ሽብር አዋጁ መነሻነት ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች ሽብርተኛ ተብለው እንደታሠሩና እንደተፈረደባቸው የተቋሙ ሪፖርት ጠቅሶ፣ በህጋዊና ሰላማዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች በፍርሃት እንዲሸበቡ ተደርገዋል ብሏል፡፡ 
ጋዜጠኞች የፀረ-ሽብር አዋጁን በመፍራት የሙያ ተግባራቸውን እንዳያከናውኑ መታፈናቸውን ሲገልጽም፤ የአዋጁ አንቀፅ እየተጠቀሰ እሥራት የተፈረደባቸው ጋዜጠኞች መኖራቸውንም አውስቷል፡፡
በኢትዮጵያ ጐልተው የሚታዩት የሰብአዊ መብት ጥሰቶች የፖለቲካ ምህዳር መጥበብና የኘሬሶች አፈና ቢሆኑም፤ ሌሎች የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችም መሻሻል አላሣዩም ብሏል ሪፖርቱ፡፡ 
በማረሚያ ቤት ያሉ እሥረኞች በገለልተኛ አካላት እንዳይጐበኙ መከልከል፣ ያልተፈረደባቸው ግለሰቦችን አስሮ ማቆየትና ለፍርድ ቤት አቤቱታ እንዳይቀርቡ ማገድ፤ ያልተፈረደባቸውን ሰዎች በብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ በሚሠራጩ ፕሮግራሞች ላይ እንደ ወንጀለኛ መፈረጅ… በአገሪቱ ከሚታዩ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ውስጥ የሚካተቱ መሆናቸውን ሪፖርቱ ዘርዝሯል፡፡  
ሠላማዊ ሠልፍ የማካሄድ፣ የመብት ጥያቄ የማቅረብና ተቃውሞን የማሰማት መብቶችንም ፈትሼያለሁ የሚለው ሂውማን ራይትስ ዎች፤ ጥያቄ ባቀረቡና ሰላማዊ ሰልፍ ባካሄዱ ሙስሊሞች ላይ እንግልት፣ ድብደባና እሥር ተፈጽሟል ብሏል፡፡ በተቃዋሚ ፓርቲዎች የተጠሩ ሠላማዊ ሠልፎችም  በአፈና ውስጥ የተካሄዱ መሆናቸው በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡
በአለማቀፍ ደረጃ ከፍተኛ የመብት ጥሰት ይፈጸምባቸዋል ከተባሉት አገራት መካከል ኤርትራ በቀዳሚዎቹ ተርታ ውስጥ እንደምትመደብ ተቋሙ ገልፆ፤ ጋዜጠኞች ለእሥራት እና ለእንግልት፤ ብዙ ዜጐችም ለስደት መዳረጋቸውን ዘርዝሯል፡፡ 
በኤርትራ የመብት ጥያቄ ማንሣት ነውር ሆኗል ያለው ይሄው ሪፖርት፤ የኤርትራ ሁኔታ ከሁሉም የአፍሪካ ሀገራት እጅግ በጣም አሣሣቢ ነው ብሏል፡፡
ሃሣብን በነጻነት መግለጽ፣ መደራጀትና የፈለጉትን አቋም መያዝ ለኤርትራውያን እንደማይፈቀድ በመጥቀስም፤ ከፍርድ ቤት ትዕዛዝ ውጪ ሰዎች እየተያዙ ይታሠራሉ፤ እስር ቤት የታጐሩ  ጋዜጠኞች፣ ፖለቲከኞችና ሌሎች ዜጐች  ያለምንም ፍርድ ከ10 ዓመት በላይ ሆኗቸዋል ብሏል፡፡ 
የኢትዮጵያ መንግስት ሂውማን ራይትስ ዎች የሚያወጣቸውን ሪፖርቶች ሙሉ ለሙሉ እንደማይቀበል በተደጋጋሚ ያስታወቀ ሲሆን፤ ተቋሙ ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር በመቀናጀት የሚሠራ ነው፤  የተቃዋሚ ሃይሎች የኘሮፖጋንዳ ማስፈጸሚያ ነው ሲል ይከሳል፡፡
ሰሞኑን የተሰራጨውን አመታዊ ሪፖርት በተመለከተ የጠየቅናቸው የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል፤ “ሂውማን ራይትስ ዎች የሚያወጣው ሪፖርት ተአማኒነት የሌለውና ገጽታን ለማጠልሸት ያለመ ነው” ብለዋል፡፡ 
ተቋሙ ሀገር ውስጥ ሣይገኝ ወይም መርማሪዎቹን ሣይልክ፣ ኬንያናና ሌላ ሀገር ተቀምጦ ከተቃዋሚዎች በሚቃርመው ያልተጣራ ተባራሪ ወሬ ላይ ተመስርቶ፣ ከመንግስት ምላሽ ሳይጠይቅ የሚያወጣው መናኛ ሪፖርት ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ፈጽሞ አይገልጽም ብለዋል ሚኒስትር ዴኤታው፡፡
ተቋሙ የኢትዮጵያን መንግስት ለማጥላላት  አቅዶ የሚሠራ ነው ያሉት አቶ ሽመልስ፤ የተቋሙ የምስራቅ አፍሪካ ወኪል አቶ ዳንኤል በቀለ፣ ህገ-መንግስቱን የማፍረስ ነውጥ በማስነሳት የተከሰሱና የተፈረደባቸው፣ ይቅርታ ጠይቀው ቢለቀቁም በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ቂም የቋጠሩ በመሆናቸው ሪፖርታቸው ገለልተኛ ሊሆን አይችልም ብለዋል። ይህ ሲባል ግን ሀገራችን ታዳጊ ሀገር እንደመሆኗ ችግሮች አይኖሩም ማለት አይደለም ያሉት ኃላፊው፤ የኘሬስ ነጻነትና የጋዜጠኞች መብት ሙሉ ለሙሉ ተጠብቆ ኘሬሱ እንዲጠናከርና  እንዲስፋፋ እየተደረገ ነው፣ ከባለሙያዎች ጋርም እየተመካከርን በጋራ እየሠራን ነው ብለዋል፡፡
http://www.addisadmassnews.com/index.php?option=com_k2&view=item&id=13619:%E1%88%82%E1%8B%8D%E1%88%9B%E1%8A%95-%E1%88%AB%E1%8B%AD%E1%89%B5%E1%88%B5-%E1%8B%8E%E1%89%BD-%E1%89%A0%E1%8A%A2%E1%89%B5%E1%8B%AE%E1%8C%B5%E1%8B%AB-%E1%8B%A8%E1%8D%96%E1%88%88%E1%89%B2%E1%8A%AB-%E1%88%9D%E1%88%85%E1%8B%B3%E1%88%A9-%E1%8B%AD%E1%89%A0%E1%88%8D%E1%8C%A5-%E1%8C%A0%E1%89%A7%E1%88%8D-%E1%8A%A0%E1%88%88&Itemid=180

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር