አዲሱ የጉድጓድ ውሃ መቆፈሪያ ቴክኖሎጂ እና በሲዳማ ዞን ሁላ ወረዳ ነዋሪ የሆነው የአቶ በቀለ ፉኤ ታሪክ

አዲሱ የጉድጓድ ውሃ መቆፈሪያ ቴክኖሎጂ -ለመጠጥ ውሃ አቅርቦት ተደራሽነት


አዲሱ የጉድጓድ ውሃ መቆፈሪያ ቴክኖሎጂ 50 ሜትር ጥልቀት ድረስ መቆፈር የሚያስችል ነው፤
ኑሮውን በውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ሥራ ላይ ያደረገው የ42 ዓመቱ አቶ በቀለ ፉኤ በሕይወት ዘመኑ በርካታ ነገሮችን አይቷል። በተለይም ከሥራው ጋር በተያያዘ ብዙ ፈተና አሳልፏል። ወገቡን በገመድ ታስሮ ቁልቁል የጉድጓድ ውሃ ሲቆፈር መሬት ተደርምሶ አፈር ተጭኖት በሰዎች ዕርዳታ ከሞት ተርፏል። ጥልቀት ያለው ጉድጓድ ቆፍሮ ውስጥ እንዳለ አየር አጥሮት ራሱን ስቷል። ወገቡን ታስሮ ቁልቁል የተላከበት ገመድ ተበጥሶ ሕይወቱ አደጋ ላይ ወድቋል።
በደቡብ ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት ሲዳማ ዞን ሁላ ወረዳ ነዋሪ የሆነው አቶ በቀለ እንጀራ ሆኖበት እንጂ የጉድጓድ ውሃ ቁፋሮ ሥራው በሞትና በሕይወት መካከል ያለ ነገር እንደሆነ ያምናል። የእለት ጉርሱን ከመሙላት አልፎ ቤተሰቡን የሚያስተዳድረው በእዚህ ሕይወትን የሚፈትን ሥራ ላይ ተሰማርቶ ነው። ሥራውን ለመተው ፍላጐት አለው። በርካታ ጊዜም የጉድጓድ ውሃ ቁፋሮ ሥራ እንዲሠራላቸው ጥያቄ ያቀረቡለትን ደንበኞቹን ጥያቄ ሳይቀበልም ቀርቷል። «የጉድጓድ ውሃ የሚቆፍሩ አባቶች ልጆቻቸውን ስመው ነው ቁፋሮ የሚጀምሩት። እኔም ልጆቼን ስሜ ተሰናብቼ ብዙ ጊዜ ሥራዬን ጀምሬያለሁ። ፈተና እያለፍኩ እዚህ ደርሻለሁ። አሁን እግዚአብሄር የተመሰገነ ይሁን ለእጅ ውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ወደጉድጓድ መግባት ቀርቶልኛል»ሲል ይናገራል።
አሁን የአቶ በቀለ ሥራ አስጊነት ምን ዋስትና አግኝቶ ነው በቀለ ለአምላኩ ምሥጋናውን ለማቅረብ የበቃውብለን ስንጠይቅ ቀላል በሆነ ቴክኖሎጂ በእጅ የሚሠራ የውሃ ጉድጓድ ለመቆፈር የሚያስችል መሣሪያ በመፈጠሩ ነው። በቀለ የውሃ ጉድጓድ ለመቆፈር ቁልቁል ወደታች መሬት ውስጥ መግባት አይጠበቅበትም። ከላይ መሬት ላይ በመሆን በአማካኝ እስከ 50 ሜትር የሚደርስ የውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ለማካሄድ የሚያስችል አነስተኛ ቴክኖሎጂ ተፈጠሯል። ቴክኖሎጂውን በኢትዮጵያ እያስተ ዋወቀ የሚገኘው ዓለም አቀፍ የልማት ኢንተርፕራ ይዝ (IDE) ከውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር መሠረተ ልማት ባልተስፋፋባቸው አካባቢዎች ለሚገኙ ማኅበረሰቦች የመጠጥ ውሃን ለማዳረስና አነስተኛ የመስኖ ልማት ለማካሄድ የሚያስችል አቅም ለመፍጠር እየተሠራ ነው።
በኢትዮጵያ የወንዝ፣ የሐይቅና የምንጭ ውሃ በአቅራቢያቸው የማያገኙ ማኅበረሰቦች ለመጠጥና ለሌሎች አገልግሎቶች የሚጠቀሙበትን ውሃ የሚያገኙት ከውሃ ጉድጓድ ነው። የውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ሥራ በእዚህ ጽሑፍ መግቢያ ላይ እንደተገለጸው፤ ለሕይወት አስጊ ነው። ይህንን ስጋት ለመቀነስ የሚያስችል አማራጭ መጥቷል። ጉድጓድ ቆፋሪዎች ወደታች ሳይወርዱ ከላይ ሆነው ለተፈለገው አገልግሎት የሚውል ጉድጓድ መቆፈር የሚችልበት አነስተኛ ቴክኖሎጂ እየተዋወቀ ነው።
2002 መጨረሻ ላይ ተቀርጾ ለቀጣይ አምስት ዓመታት ተፈጻሚ የሚደረገው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ በከተማም ሆነ በገጠር ያለውን የውሃ አቅርቦት ለማሳደግ የሚያስችል ሰፊ ፕሮግራም አስቀምጧል። በዕቅዱ መሠረትም ንፁህ የመጠጥ ውሃን ለማዳረስ እየተሠሩ ያሉ ሥራዎች ውጤታማ እየሆኑ ነው። በተለይም አስፈላጊ የመሠረተ ልማት ባልተዳረሰባቸው አካባቢዎች የውሃ አቅርቦቱን ተደራሽ ማድረግ የተቻለበት አጋጣሚ ተፈጥሯል። በመሠረተ ልማት አለመሟላት የተነሳ የውሃ አቅርቦትን ማዳረስ ባልተቻለባቸው አካባቢዎች የመጠጥ ውሃና ለአነስተኛ መስኖ አገልግሎት የሚውል የውሃ አቀርቦት አቅም ለመፍጠር አይዲኢ እያስተዋወቀው ያለው የእጅ ውሃ ጉድጓድ መቆፈሪያ አነስተኛ ቴክኖሎጂ ፍቱን መድኃኒት ሊሆን ይችላል።
በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር እንዲሁም በአይዲኢ ትብብር እየተዋወቀ ያለውን አነስተኛ ቴክኖሎጂ ለማስፋፋት እንዲያስችል ታስቦ ከአማራ፣ ከኦሮሚያ፣ ከትግራይ፣ ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ እንዲሁም ከደቡብ ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልሎች የተውጣጡ 25 ባለሙያዎች የአሠልጣኞች ሥልጠና ወስደዋል። ሠልጣኞቹ በመጀመሪያ በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ሸዋ ዞን ባቱ ወረዳ ሥልጠና ወስደዋል። ከእዚያም በምዕራብ ሸዋ ዞን ኤጀሬ ወረዳ በሚገኘው ኢናፍቱ ቀበሌ ውስጥ የተግባር ልምምድ አድርገዋል። ሠልጣኞቹ ለ70 ቀናት በወሰዱት ሥልጠና 20 በእጅ የሚሠራ የጉድጓድ ውሃ ቆፍረው ለኅብረተሰብ አገልግሎት እንዲውሉ አድርገዋል። በተለይም የተግባር ልምምድ በወሰዱበት የኢናፍቱ ቀበሌ ፈታኝ ጊዜን አልፈው በአማካኝ ለ110 ቤተሰብ አገልግሎት ሊሰጡ የሚችሉ አራት የጉድጓድ ውሃ ተጠቃሚ እንዲሆን አድርገዋል።
ሠልጣኞቹ የእጅ ጉድጓድ ውሃ ቁፋሮ ለማካሄድ የሚያስችለውና የቀላል ቴክኖሎጂ መሣሪያዎችን እጃቸው ማስገባት ከቻሉ ለመጠጥና ለአነስተኛ መስኖ ሊበቃ የሚችል የውሃ ተቋም ለመመስረት የሚያስችል አቅም እንደፈጠሩ ይገልጻሉ። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የመተከል ዞን የመጠጥ ውሃና የመስኖና ሳኒተሪ ቡድን መሪ የሆኑት አቶ ዓለምገና ቀፀላ በዞናቸው ውስጥ ያለውን የመጠጥ ውሃ ችግር ለመፍታት ቴክኖሎጂውና ሥልጠናው ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ያመለክታሉ።
«ከእዚህ ቀደም በነበረው ልማዳዊ የውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ሥራ ከ15 ሜትር በላይ ጥልቀት ያለው ጉድጓድ ተቆፍሮ አያውቅም። ይህም ቢሆን ሥራውን በሚያከናውኑ ባለሙያዎች ላይ ለሕይወት አስጊ የሆነ ፈታኝ ሁኔታዎችን ማለፍ ግድ ይል ነበር። አሁን ግን በመጣው አዲስና ቀላል ቴክኖሎጂ መቆፈር ይቻላል። ይህንን በተግባር አይተነዋል» ሲሉ የሚገልጹት አቶ ዓለምገና በሪግ ማሽን ቁፋሮ ከሚካሄደው ባልተናነሰ መልኩ ከ20ሺ ብር ባልበለጠ ወጪ ለኅብረተሰቡ የንፁሕ መጠጥ ውሃ አገልግሎት ሊሰጡ የሚችሉ የውሃ ተቋማትን መገንባት የሚቻልበትን ሥልጠና እንዳገኙ ያስረዳሉ።
እንደ አቶ ዓለምገና ገለጻ፤ በተሰጠው የእጅ ውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ሥልጠና መሠረት በርካታ የእጅ ውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ለማካሄድና ኅብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ ምቹ ሁኔታዎች አሉ። በውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ሥራ ላይ የተሰማሩ ባለሙያዎች ሥልጠናውን አግኝተውና በኢንተርፕራይዝ ተደራጅተው ያለምንም ስጋት በአነስተኛ ክፍያ ኅብረተሰቡን የንፁሕ መጠጥ ውሃና የመስኖ ልማት ተጠቃሚ ሊሆን የሚችልባቸው ሁኔታዎች እንደሚመቻቹ ይናገራሉ። በክልሉ መተከል ዞን ውሃ ባልተዳረሰባቸው አካባቢዎች ይህንን ቀላል ቴክኖሎጂ በመጠቀም የመጠጥ ውሃ ለማዳረስ ሥልጠናው የላቀ ሚና እንደሚጫወት ይጠቁማሉ። በተለይም በመንደር ማሰባሰብ ሂደት ላይ የውሃ አቅርቦቱን አስተማማኝ ለማድረግ ይህ ቴክኖሎጂ ጠቀሜታው የጐላ ይሆናል።
ከአምስቱ ክልሎች የተውጣጡ 25 ሠልጣኞች ሥልጠናውን በወሰዱበት የባቱ ወረዳ ያካሄዱት የእጅ ውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ብዙም ፈታኝ ሁኔታ አላጋጠማቸውም። አፈሩ በቀላሉ የሚቆፈር ነበር። በመሆኑም ከሦስት እስከ ሰባት ባሉት ቀናት ውስጥ አንድ ቡድን አንድ የውሃ ጉድጓድ ሙሉ ለሙሉ ያጠናቀቀበት ሁኔታ ነበር። ነገር ግን የተግባር ልምምድ በተደረገበት የኢናፍቱ ቀበሌ የአፈሩ ዓይነት ከባቱ ወረዳ የተለየ ስለነበር አንድ የውሃ ጉድጓድ ለመቆፈርና ለአገልግሎት ለማብቃት ከ10 ቀናት በላይ ፈጅቷል። ሠልጣኞቹ የአፈሩ ሁኔታ ጠንካራ በሆነባቸው አካባቢዎች ተፈትነው አልፈዋል። በመሆኑም በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመኑ የተቀመጠውን የውሃ አቅርቦት ለማሟላት በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ያበረክታሉ ተብሎ ይጠበቃል።
ሠልጣኞች በሥልጠናው ወቅት በእጅ የሚሠራ የጉድጓድ ውሃ ማልማት የሚያስችል ሥልጠና መቅሰማቸውን ይናገራሉ። ከሥልጠናው በኋላ ወደየመጡበት አካባቢ ሄደው በንድፈ ሃሳብና በተግባር የቀሰሙትን ዕውቀትና ክህሎት ተግባራዊ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል። ለእዚህም ዝግጁነት እንዳላቸው አረጋግጠዋል። ነገር ግን ያሰቡትን በማሳካት ሂደት የቅስቀሳና የፋይናንስ አቅርቦት ተግዳሮቶች ሊያጋጥሟቸው እንደሚችሉ ስጋታቸውን ከወዲሁ እየገለጹ ነው።
በንድፈ ሃሳብና በተግባር ልምምድ ወቅት አስፈላጊ የሆኑ ነገሮች በሙሉ ተሟልተውላቸው 20 የውሃ ጉድጓድ መቆፈር የቻሉት ሠልጣኞች የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ወደየመጡበት አካባቢ ሄደው ቴክኖሎጂውን ሲያስፋፉ እገዛ እንዲያደርጉ ላቸው ይጠይቃሉ።
በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የዩኒሴፍ ፕሮጀክቶ ችና የራስ አገዝ ፕሮጀክቶች አስተባባሪ የሆኑት ወይዘሮ ዘውዲቱ ይልማ በቀላል ቴክኖሎጂ መሠረተ ልማት ባልተስፋፋባቸው አካባቢዎች የውሃ አቅርቦቱን አስተማማኝ ለማድረግ የሚደረገው ጥረት ውጤታማ እንዲሆን እየተሠራ እንደሆነ ይጠቁማሉ። ከአይዲኢ በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ የተሰጠው የጉድጓድ ውሃ ቁፋሮ ሥልጠና በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመኑ ማሳካት የታሰበውን የዘርፉን ግብ ለማሳካት እንደሚረዳ የሚገልጹት ወይዘሮ ዘውዲቱ ሠልጣኞቹ ወደየመ ጡበት አካባቢ ሄደው ለመሥራት የሚችሉበት ሁኔታ ከወዲሁ መመቻቸቱን ይናገራሉ።
የውሃና ኢንርጂ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ከበደ ገርባ በበኩላቸው እንደሚናገሩት፤ የከርሰ ምድርንና የገፀ ምድር ውሃን በመጠቀም ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት ውስጥ የቀላል ቴክኖሎጂ የጉድጓድ ውሃ ቁፋሮ በቀጣዮቹ ዓመታት የተሻለ ውጤት ይመዘገብበታል ተብሎ እንደታሰበ ይገልጻሉ። ሰልጣኞች የቀሰሙትን እውቀት በተግባር ለመተርጐም እንዲችሉ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ተገቢውን ድጋፍና ክትትል የሚያደርግ መሆኑንም ይናገራሉ።
ሠልጣኞቹ እንደ ስጋት ያስቀመጡት የበጀትና የቁሰቁስ አቅርቦት ችግር ሊፈታ በሚችልበት ሁኔታ ላይ ከክልሎች ጋር መግባባት ላይ መደረሱን የሚገልጹት አቶ ከበደ፤ «የድጉጓድ ውሃ ቁፋሮ»በሚል የተያዘ በጀት ለእዚህ ዓላማ እንዲውል ከስምምነት ላይ መደረሱን ይጠቁማሉ።
በኢትዮጵያ ውስጥ አሁንም ድረስ የውሃ እጥረት ባለባቸው አካባቢዎች የጉድጓድ ውሃ መፍትሔ ሆኖ አገልግሏል። አሁንም የመፍትሔ አካል እንደሆነ ነው። ይህንን ሁኔታ በተሻለ መልኩ ተግባራዊ ለማድረግ የሚደረገውም እንቅስቃሴ እንዲሁ እንደቀጠለ ነው።
አይዲኢ እያስተዋወቀው ያለው የቀላል ቴክኖሎጂ የጉድጓድ ውሃ ቁፋሮ ሥራ ውጤታማ ሊሆን እንደሚችል ይታሰባል። በተለይም በቴክኖሎጂው እስከ 50 ሜትር ድረስ ጥልቀት ያላቸው የውሃ ጉድጓዶችን አነስተኛ በሆነ ወጪ (እስከ 20ሺ ብርመገንባት መቻሉ በነፍስ ወከፍ ደረጃ ማስቆፈር የሚችልበት ዕድል አለ። በመሆኑም ከመጠጥ ውሃ አቅርቦት ባለፈ አነስተኛ መስኖ ለማካሄድ የሚችልበት ዕድል ያለው በመሆኑ የግብርና ምርትን ለማሳደግ አስተዋጽኦ ይኖረዋል።
በቅርቡ በኣዲስ ዘመን ጋዜጣ ላይ የወጣ ጽሁፍ 

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር