ማጅራት ገትርና መከላከያው፣

የወባን(ንዳድ)ን ያክል ባይሆንም ፤ አፍሪቃ ውስጥ ልጆችንና ወጣቶችን ይበልጥ በመጠናወት ፣ በብዛት ሲገድል የቆየ በሽታ ፤ ማጅራት ገትር ነው። ይሁንና ፤ ይህን ቀሳፊ በሽታ መከላከልም ሆነ መግታት የሚቻልበት ብልሃት ስለመረጋገጡ ከሰሞኑ የወጡ የምርምር
ውጤቶች ማስገንዘባቸው የሚታወስ ነው።ማጅራት ገትር፣ በተለያዩ ክፍላተ ዓለም ቢገኝም ፣ ይበልጥ የተስፋፋውና ሰውም በብዛት ሲፈጅ የቆየው፤ አፍሪቃ ውስጥ ፣ ከሰሐራ ምድረበዳ በስተደቡብ ፣ ከምድር ሰቅ በስተሰሜን ከሞላ ጎደል ፤ በ 5 እና 15 ዲግሪ ከፍተኛ መሥመር መካከል ፣ ከሴኔጋል እስከ ኢትዮጵያና ኤርትራ፣ የሳሔል መቀነት በተሰኘው የክፍለ ዓለሙ ቀጣና በሚገኙ 26 ያህል አገሮች ነው። እነዚህ አገሮች ደግሞ በከፊል ድርቅ የሚያጠቃቸው መሆናቸው የታወቀ ነው። በሽታውን የሚያስተላልፉት ተኀዋስያን ፤ ባክቴሪያዎች የተለያዩ በዓይን የማይታዩ ኢምንት ነፍሳትም መንስዔዎች ሊሆኑ ይችላሉ። ማጅራት ገትር እንደሚታወቀው፤ አንገት እንዳይንቀሳቀስ ቀስፎ የሚይዝ፣ በራስ ምታትና ትኩሳት ታጅቦ ፣ ከማጅራት እስከ ኅብለ -ሠረሠር ፣ ማዕከላዊውን የነርብ አውታር የሚጠናወት በሽታ ነው። አእምሮን እንደመሳት ያደርጋል፤ ያጥወለውላል፤ በበሽታው የተያዘ ሰው ብርሃንና ኃይለኛ ድምፅ በእጅጉ ያውኩታል። አንገትን አግርሮ የማያንቀሳቅሰው፤ ከማጅራት እስከ ኅብለ ሠረሠር ነርቦችን የሚጠናወተው፤ አፍንጫ ፤ ጆሮና ላንቃን የሚያሳምመው በሽታ፤ ሊደነቁር ፤ የሠራ-አካላትን ሊያሽመደምድና ለሞት ሊደርግ የሚችል ሕመም ነው።
በጎልማሦች ዘንድ የህመሙ ዋና መለያ ዘጠና ከመቶ ማለት ይቻላል፤ ብርቱ ራስ ምታት ነው። 70 ከመቶ መንስዔውም በባክቴሪያ ሳቢያ የሚዛመተው የማጅራት ገትር በሽታ አንደኛው ከፊል ነው። በአፍሪቃ በሰፊው የተዛመተውና በየጊዜው እያገረሸ ጉዳት የሚያደርሰው የማጅራት ገትር በሽታ ዓይነት በባክቴሪያ አማካኝነት የሚዛመተው «ሜኒንጎኮካል ሜንንጃይቲስ » በመባል የታወቀው ነው። «ሜንንጃይቲስ ኤ» በመባልም ይታወቃል። የተባበሩት መንግሥት ፣ የዓለም የጤና ጥበቃ ድርጅት፤ ባደረገው ክትትል፤ ካለፈው ዓመት ጥር ወር አንስቶ እስከ ግንቦት ወር 2005 ዓ ም ድረስ፤ በመጅራት ገትር የተያዙት ሰዎች ቁጥር ከ 9,250 እንደማይበልጡ፣ የሞቱት ደግሞ 857 መሆኑን ነው የገለጠው።
ለማጅራት ገትር አሁን ፍቱን መድኀኒት መገኘቱን ያበሠረው፤ የመንግሥት ያልሆነው የማጅራት-ገትር የክትባት ፕሮጀክት፣(Meningitis Vaccine Project) (MVP)በሚል ስያሜ የታወቀው ድርጅት፤ ከ ዐራት ዓመት በፊት በሳሔል መቀነት ፤ ቢያንስ 88,000 ሰዎች ታመው እንደነበረና ከ 5,000 በላይ ህይወታቸውን ማጣታቸውን ያኔ ያካሄደው ጥናት ያስረዳል።
በጠነጠኑት ዓለም አቀፍ ቱጃር ባልና ሚስት፣ ቢል ና ሜሊንዳ ጌትስ የገንዘብ ድጋፍ «ሜድ አፍሪ ቫክ» የተባለውን የክትባት መድኀኒት ያመረተው የማጅራት-ገትር የክትባት ፕሮጀክት የተሰኘው ድርጅት ፤ እ ጎ አ እስከ 2011 ዓ ም ፍጻሜ ድረስ፣ ቻድ ውስጥ በሦስት ክፍላተ ሀገር ፣ በአጠቃላይ ለ 1,8 ሚሊዮን ህዝብ መድኃኒቱን አድሎ ነበር። እናም የህክምና ተመራማሪዎች በዓመቱ የክትባት መድኃኒት የተሰጣቸውን ሰዎች መርምረው፤ ከየመቶሺው ሰው ከሞላ ጎደል የ 2,5 የማጅራት ገትር ዓይነት ህመም ማጋጠሙን በባካቴሪያ የሚተላለፈው «መኒንጃይቲስ ኤ» ግን አንድም ሰው እንዳላገኘው ለመገንዘብ ችለዋል። የክትባቱን መድኀኒት ባገኑት ሰዎች መካከል ፣ በሽታው፤ 98 ከመቶ ካንድ ሰው ወደ ሌላ የሚተላለፍበት አንዳች ዕድል እንደሌለው አረጋግጠዋል ነው የተባለው።
«ሜዲ አፍሪ ቫክ» ሥራ ላይ እንዲውል ፈቀድ ከተሰጠ በኃላ፤ እ ጎ አ በ 2010 ዓ ም ፤ ከሴኔጋል አንስቶ እስከ ኢትዮጵያ፤ ከ 100 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ተክትቧል። የሳሔል መመቀነት በሚሰኘው የአፍሪቃ ክፍል፤ 450 ሚሊዮን ያህል ህዝብ፤
«ሜንንጃይትስ ኤ» የተባለው ማጃራት ገትር የሚያሰጋው ነው ። በአፍሪቃው ክፍለ ዓለም ፤ ከ 80 ከመቶ በላይ የማጃራት ገትር ህመም የሚከሠተው በ «ሜንንጃይቲስ ኤ » አማካኝነት ነው ። ከ 7 ቱ-14 ዓመት ባለ የጊዜ እርከን ውስጥ የዚሁ በሽታ ወረርሺኝ የሚያጋጥም ሲሆን፣ ባለፈው ኃይለኛ ወረርሺን ማለትም እ ጎ አ በ 2009 ዓ, ም፤ የዓለም ጤና ጥበቃ ድርጅት (WHO) እንዳስታወቀው 5,300 ሰዎች በአጭር ተቀጭተዋል። ባለፉት ሦስት ዓመታት፤ በ 10 ሃገራት ከ 100 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ከማጅራት ገትር አደጋ ነጻ እንዲሆን ያበቃው ክትባት ፣ በዩናይትድ እስቴትስ የአንዱ ዋጋ 50 የአሜሪካ ሳንቲም ሲሆን ፣ አፍሪቃም ውስጥ እ ጎ አ ከ 2010 ዓ ም አንስቶ፤ በቡርኪና ፋሶ ማሊና ኒጀር በተመጣጣኝ ዋጋ ሆኗል ለህዝብ የሚቀርበው። በሳሔል መቀነት፤ በአንድና በ ኻያ ዘጠኝ ዓመት የዕድሜ እርከን ላይ ለሚገኙ አፍሪቃውያን የሚሰጠው ክትባት ውጤት እጅግ ያረካቸው፤ በዓለም የጤና ጥበቃ ድርጅት የክትባት ክፍል ዋና ሥራ አስኪያጅ ጓን ማሪ ኦኮዎ በሌ፣ «ይህ የክትባቱን ዘመቻ ገና ላላካሄዱ አገሮች፣ የሚያበረታታ ምልክት ሰጪ ነው በማለት ደስታቸውን ሳይገልጹ አላለፉም።
ብዙዎቹ የአፍሪቃ ክፍለ ዓለምና የሌሎቹም ክፍለ ዓለማት ታዳጊ ሃገራት፣ የተባበሩት መንግሥታት አጠቃላይ ጉባዔ በነደፈው መሠረት፤ የዓእማቱን ግቦች ለማሳካት ጥረት ከሚያደርጉባቸው እቅዶች አንዱ የጤና አጠባበቅ ጉዳይ ነው። የተተለመውን እቅድ በጊዜ ለማሳካት የቀረው ጊዜ አንድ ዓመት ከ ሦስት ወር ባቻ ነው። ጤናን ለመጠበቅ ደግሞ የህዝቡ የኑሮ ደረጃ ከፍ እንዲል ፤ የተመጣጠነ ምግብና መድኃኒት ማግኘት የሚችልበት አቅሙ እንዲጎለብት ለማድረግ ጥረት ማድረጉ የግድ የሚል ነው። ከዚህ ጋር ተያይዞ፣ መድኃኒት ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ ፣ እርግጥ ዓለም አቀፍ ትብብር ያሻል። በሃርቫርድ ዩንቨርስቲ የህክምና ክፍል ፕሮፌሰር አኒታ ቫግነር ይህ ችግር እንዴት ሊቀረፍ እንደሚችል ሲያብራሩ---
«ለህይወት ጠንቅ የሆኑ በዛ ያሉ በአብዛኛው ሁናቴዎች መኖራቸው ቢታወቅም፤ ብዙ ሰዎችን መርዳት የሚችሉ ፍቱን የመድኃኒት ዓይነቶች አሉን። ችግሩ ፤ እነዚህን መድኃኒቶች ሰዎች በቀላሉ ያገኟቸው ዘንድ የሚያስችሉ ሥርዓቶች እስከዚህ አልተዘረጉም።»
መድኃኒት አምራቾች፤ እዚህም ላይ ለምሳሌ ያህል ፣ ሳኖፊ የተባለው የፈረንሳይ ኩባንያ፤ እጅግ አነስተኛ ገቢ ላላቸው አገሮች፤ እጅግ ረከስ ባለ ዋጋ መሸጥ ይቻላል ባይ ነው። በኢንዱስትሪ በበለጸጉት አገሮች ደግሞ ያንኑ መድኃኒት ከፍ ባለ ዋጋ መሸጥ ይቻላል። በሳኖፊ ኩባንያ፤ «መድኃኒት ማግኘት» የተሰኘው መርኀ ግብርም ሆነ ዘመቻ ባልደረባ ፍራንሷ ቦምፓርት ---
«በዓለም አቀፍ የክትባት ዘመቻ ላይ በሚገባ እየተሠራበት ነው። አንድ የክባት መድኃኒት ፣ እንበል በዩናይትድ እስቴትስ ወይም በአውሮፓ በ 50 ዩውሮ ቢሸጥ፤ አፍሪቃ ውስጥ 3 ወይም 4 ዩውሮ ተመጣጣኝ ዋጋው ይሆናል። በአጠቃላይ ይህ ዓይነቱ የአያያዝ ሥርዓት በሚገባ የሚሠራ ነው። ምክንያቱም በመሃሉ፣ ብራዚል፤ ደቡብ አፍሪቃና ታይላንድን የመሳሰሉ አገሮችም አሉ። እነዚህ አገሮችም ከ 10 እስከ 20 ዩውሮ መክፈል ይችላሉ»።
በሌላ በኩል እንዲሁ የመድኃኒት ዋጋ ብቻ ቀንሶ ማቅረቡ ፋይዳ አይኖረውም፤ በመጀመሪያ የበሽታ ዓይነቶችን መርምሮ፤ ለይቶ ማወቅ ነው የሚበጀው የሚሉም አሉ። እናም በዛ ያሉ ነርሶችን ማሠልጠን፤ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው።
በዩጋንዳ ጤና ጥበቃን በተመለከተ የሃገሪቱ ፕሬዚዳንት አማካሪ የሆኑት ዶክተር እስፔሲዮዛ ዋንዲራ -ካዚብዌ ፣ በዩጋንዳ ብዙውን ጊዜ የአንድን በሽታ ዓይነት በትክክል መርምሮና ለይቶ የማሳወቅ ችግር አለ ባይ ናቸው።
«እያንዳንዱ ወረዳ፤ በዝቅተኛ ደረጃ ባለው በዚሁ መስተዳድር ፣ አንድን በሽታ መርምሮ ማወቅ የሚያስችለው ሥነ ቴክኒክ አለን። በመሆኑም ካንሠርን ፤ ወባንም ሆነ የተላላፊ በሽታ ዓይነቶችን ለይተን ማወቅ እንችላለን። በመሆኑም አገሪቱ በመላ የሚያስፈልጋትን የመድኃኒት ዓይነት ለማቅረብ ማቀድ እንችላለን። »
http://www.dw.de/popups/mediaplayer/contentId_17115690_mediaId_17115685

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር