እነ “ሻኪራ” በአሞራ ገደል

የዛሬ ሳምንት ሀዋሳ ነበርኩኝ፡፡ የወትሮዋ ሳቂታዋ ሀዋሳ አልነበረችም፡፡ አኩርፋለች፡፡ ሌላ ችግር ገጥሟት ግን አይደለም፡፡ ክረምቱ ነው ያስኮረፋት፡፡
ዝናቡ፣ ቅዝቃዜውና ደመና የሸፈነው ሰማይ ተጫጭነዋት ነበር፡፡ እንደኔ እንደኔ ሀዋሳ ደርሶ አሞራ ገደልን ሳይጐበኙ መመለስ ካለመሄድ እኩል ነው፡፡ እዚህ ስፍራ ዓሳ እንደጉድ ይበላል፡፡ ያውም ቁጥር - ልክ እንደ ስጋ፡፡ የአሳ ቁርጥ ተመጋቢዎች በእንጨት ግድግዳ በተከበበው ዳስ መሳይ ቤት ውስጥ ግፊያውና መረጋገጡን ተያይዘውታል፡፡ በሀዋሳ ሀይቅ ዳር ባለው በዚህ ስፍራ ሰው ከአንድ ቦታ አሳውን ይገዛና እዛው ዳስ ቤት ውስጥ የአሳውን እሾክ እያስወጣ ቁርጡን በሳህን እየያዘ ማባያውን ለማግኘት ሁለት ጐን ለጐን የተቀመጡ ማባያ አቅራቢዎች ጋር መገናኘት ይጠበቅበታል፡፡ አንዱ “ዳጣ” የተባለው እና ከሚጥሚጣ እንዲሁም ከሌሎች ቅመሞች የተሰራ የሚያቃጥል ማባያ ሲሆን (እኔ በጣም ከማቃጠሉ የተነሳ “እንላቀስ” ብየዋለሁ) ሁለተኛው ትንንሽ ክብ የበቆሎ ቂጣዎች ናቸው፡፡ ሁለት ወጣቶች የአሳ ቁርጥ ከግፊያው ውስጥ ይዘው ወጥተው አንዱ ሌላውን፣ “ሂድና ሲዲ ይዘህ ና፣ ታዲያ ስክራች እንዳይኖረው” ሲል አስጠነቀቀው፡፡ ሲዲ ምንድነው ስል ጠየቅሁት አንዱን ወጣት፡፡ “ሲመጣ ታይዋለሽ” አለና ዳጣ ሊያስጨምር መስከረም ወደ ተባለች ዳጣ ሻጭ አመራ፡፡ እኔም ስክራች እንዳይኖረው የተባለውን ሲዲ በጉጉት መጠበቅ ጀመርኩ፡፡ ለካስ ሲዲ የሚሉት የበቆሎውን ቂጣ ነው፡፡ “ስክራች” የተባለው ደግሞ ያረረ እና የተሰነጣጠቀ እንዳይሆን ለማለት የተጠቀሙበት አገላለፅ ነው፡፡
ከወጣቶቹ የእንብላ ግብዣ ቀረበልኝ፡፡ የአሳ ቁርጥ በልቼ ስለማላውቅ ብፈራም “ሲዲ”ውን በዳጣ ግን አልማርኩትም፡፡ ወጣቶቹ ቁርጡን እየበሉ ሳሉ አንዱ “ሲዲውን በርን (burn) አድርገው” ሲል ሰማሁ፡፡ ደሞ ምን ማለት ይሆን አልኩኝ - ለራሴ፡፡ ለካ ቂጣው ስለላቀ ጨምር እና ግዛ ለማለት ነው፡፡ በሳቅ ታጅቤ አብሬያቸው ቆየሁ፡፡ በአሞራ ገደል ከአሳ ቁርጥ ባልተናነሰ የአቮካዶ ቁርጥም እንደ ጉድ ይበላል፡፡ ታዲያ የአቮካዶም ማባያ ዳጣ ነው፡፡ የሲዲ ሻጮቹ ሴቶች ቁጥር በርካታ ነው፡፡ ተደርድረው “ከእኔ ግዛ፣ ከእኔ ግዛ” ይላሉ፡፡ ከሁሉም ዳጣ በመሸጥ ፋታ አጥታ የምትተጋው ግን መስከረም ናት፡፡
መስከረም ላለፉት አራት አመታት በዚህ ስፍራ ዳጣ በመሸጥ ስራ ላይ መቆየቷን አጫውታኛለች፡፡ በዚህ ስፍራ ጠዋት ጠዋት ዳጣ በጅምላም በችርቻሮም ትሸጣለች፡፡ በአካባቢው ከልጅ እስከ አዋቂ ሁሉም የአሳ ቁርጥ በሊታ ነው፡፡ እርግጥ የተጠበሰ አሳም በስፍራው ይገኛል፡፡ ግን ቁርጥ ተመጋቢው በቁጥር ይልቃል፡፡ የተጠበሰ አሳ ከአሞራ ገደል ይልቅ በፍቅር ሀይቅ በኩል ኦሲስ አሳ መሸጫ ውስጥ ይገኛል፡፡ በዚህ ቦታ የአሳ ሾርባው ተጠጥቶ አይጠገብም፡፡
እነሆ ሌላ ትዕይንት፡፡ የአሳ ቁርጥ ሲሰራ የሚጣለውና ትርፍራፊውን የአሳ ስጋ በፌስታል በመያዝ እና በአካባቢው አባ ኮዳ ተብሎ ለሚጠራው ግዙፍ የወፍ አይነት እየወረወሩ በመስጠት ሌላ ስራ የሚሰሩም ታዳጊዎች አስደምመውኛል፡፡ እንግዳ ሆነው ከሄዱ ይህ ወፍ በረጃጅም ማንቁርቱ ስጋውን ለመያዝና ከተቀናቃኙ ሌላው ጓደኛው ለመቅደም የሚያደርገው ዝላይ አይን ያፈዛል፡፡ ብልጣብልጦቹም ታዳጊዎች “ሂዱና ፎቶ ተነሱ” ብለው ወፉ አካባቢ እንዲቆሙ ይነግሩዎታል፡፡ እርስዎም በዚህ ትዕይንት መሀል አንድ ታሪካዊ ፎቶ ልነሳ ብለው ወፉ ስጋ ለመቅለብ የሚያደርገውን ዝላይ እየተመለከቱ ፎቶ ሲነሱ ይቆዩና እግዜር ይስጥልኝ ብለው ሊሄዱ ሲሉ “እንዴ ጋሼ (እትዬ) አስር ብር ይክፈሉ፤ ይህንንም ስራ የምንሰራው እኮ በማህበር ነው” ብለው እርፍ ይላሉ፡፡ እየሳቁም እየተገረሙም ከፍለው ይሄዳሉ፡፡ ሌሎች በርካታ ትዕይንቶችም በዚህ ስፍራ ይገኛሉ፡፡
እነ ሻኪራ በአሞራ ገደል
አሁን ደግሞ ወደነሻኪራ ልውሰዳችሁ፡፡ በዚህ ስፍራ ካስደነቁኝ ነገሮች ሁሉ የእነ ሻኪራ ጉዳይ ነው፡፡ በ2010 የአለም ዋንጫ በደቡብ አፍሪካ በተካሄደ ጊዜ ሻኪራ በስፍራው ተገኝታ “ዋካ ዋካ ዚስ ኢዝ ታይም ፎር አፍሪካ” የሚል ዘፈን ማቀንቀኗ ይታወሳል፡፡ እነሻኪራ ይህን ዘፈን ከነዳንሱ በዚህ ስፍራ አሳምረው ያቀልጡታል፡፡
የቡድን መጠሪያቸው “እነ ሻኪራ” ይሰኛል፡፡ ሂሩት አሸናፊ፣ ሀይማኖት ቶሳ እና መሰረት ኦሳ፡፡ ሂሩትና ሀይማኖት የ7 ዓመት ህፃናት ሲሆኑ የአንደኛ ክፍል ተማሪዎች መሆናቸውን ነግረውኛል፡፡ መሰረት ደግሞ ዕድሜዋ ስምንት አመት ሲሆን የሁለተኛ ክፍል ተማሪ ናት፡፡ እነዚህ ህፃናት ጐስቋላ ኑሮ እንደሚኖሩ በማየት ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ አለባበሳቸው፣ ፀጉራቸው አጠቃላይ ሁኔታቸው ኑሯቸው ምቾት የራቀው መሆኑን ይመሰክራል፡፡ ከሁለቱ አንዷ ጫማ አልተጫማችም፡፡ ሂሩት ከላይ የለበሰችው አዳፋ ሹራብ ከጠዋቱ ብርድ ሊከልላት አልቻለም፡፡ ሀይማኖት ደግሞ ፀጉሯ ክፉኛ ቆሽሿል፡፡ ጉብኝቴን ጨርሼ ወዳረፍኩበት ለመመለስ ባጃጅ ኮንትራት ስይዝ አጠገቤ ያለ አንድ ወጣት “እነ ሻኪራ ፈረንጆቹ መጡላችሁ” ብሎ ሲነግራቸው ብን ብለው ወደ ፈረንጆቹ ሮጡ፡፡ ፈረንጆቹ የህፃናቱ ፍላጐት የገባቸው አይመስሉም፤ አልፈዋቸው ሄዱ፡፡ እኔ ጠርቼ አናገርኳቸው፡፡ ባለ ባጃጁም እስካናግራቸው እንደሚጠብቀኝ ነግሮኝ፣ የሻኪራን ዘፈን እየዘፈኑ ብር እንደሚቀበሉ ጠቆመኝ፡፡ እነዚህ ህፃናት አማርኛ በደንብ አይችሉም፡፡ ነገር ግን እየተኮላተፉም ቢሆን መግባባት ችለናል፡፡ “የሻኪራን ዘፈን ከነዳንሱ እንበልልሽ” አሉኝ፡፡
“ቀጥሉ” አልኳቸው፡፡
“በወላይትኛ ዳንስ ይሻልሻል ወይስ በራሷ በሻኪራ?” አማረጡኝ፡፡
“በወላይትኛም በሻኪራም እፈልጋለሁ” አልኳቸው፡፡
“ዋካ ዋካ” ተጀመረ፡፡ ዘፈኑ ወዲያው “ዱርሳ ዱርሳ” ወደተሰኘ ሌላ የአካባቢው ዘፈን ተቀየረ፡፡ አከታትለው የትዕግስት ወይሶን “ገደ ገዳ” ቀጠሉ፡፡ ልጆቹ ነገረ ስራቸው አይን ያፈዛል፤ አንጀትም ይበላሉ፡፡ የሚገርመው እኔ ደንሱልኝ ብያቸው እየደነሱ አይናቸውና ልባቸው ሌላ ጋ ነው፡፡ ሌላ የሚያስደንሳቸው ሰው ፍለጋ በሀሳብ ይባዝናሉ፡፡ መቼ ስራውን እንደጀመሩ ስጠይቃቸው በአንድ ቃል “ዱሮ ነው የጀመርነው” ሲሉ መለሱ፡፡
“አሁን ስንት ታስከፍሉኛላችሁ?”
“የፈለግሽውን ስጭን፤ እኛ ይህን ያህል እያልን አንጠይቅም፡፡”
“እዚህ ስትሠሩ፣ ትምህርታችሁስ?” አልኳቸው፡፡
“አሁን ትምህርት ቤት ዝግ ነው፤ ሲከፈት ግን ከትምህርት ቤት በኋላ እየመጣን እንሰራለን” አሉኝ፡፡
እነዚህን ህፃናት በቀን ስንት ብር እንደሚያገኙና ብሩን ምን እንደሚያደርጉት ጠይቄያቸው ነበር፡፡ በቀን እያንዳንዳቸው ከ10 እስከ 40 ብር እንደሚያገኙና ለእናታቸው እንደሚሰጡ ነገሩኝ፡፡ በዚህ የልጅነት እድሜ ወላጆቻቸውን ይደግፋሉ ማለት ነው፡፡ ከእኔ ጋር እያወራን ዕድሜዋ ገፋ ያለ አንዲት ፈረንጅ ስትመጣ አዩና እሷ ጋ ሄደው ለመደነስ ልባቸው ቆመ፡፡ 10 ብር ሰጥቼ ልሸኛቸው ስል የወደፊት ምኞታቸውን ጠየቅኋቸው፡፡ እንደ ሻኪራ ታዋቂ ዘፋኝና ዳንሰኛ መሆን እንደሚፈልጉ ነገሩኝ፡፡ በት/ቤታቸው እንዲህ አይነት እንቅስቃሴ ያደርጉ እንደሆነም ጠይቄያቸው ነበር፡፡ “ት/ቤት እኛ መደነስ እንፈልጋለን ስንል አይፈቀድልንም፤ እዚህ እየመጣን ነው የምንደንሰው” አሉኝና አመስግነውኝ ወደ ፈረንጇ በቀጫጭን እግሮቻቸው ተፈተለኩ፡፡ ፈረንጇም እግዜር ይስጣት ቆማ በተመስጦ ዳንሳቸውን እየተመለከተች፣ ፎቶግራፍ ስታነሳቸው ነበር፡፡ እቺ ፈረንጅ ከእኔ የተሻለ ጉርሻ እንደምትሸጉጥላቸው በልቤ ተስፋ አደረግሁኝ፡፡ ከሁሌም ያሳሰበኝ ግን የወደፊት ዕጣ ፈንታቸው ነው፡፡ እንደምኞታቸው ይሳካላቸው ይሆን? ብዙ ፈተና ይጠብቃቸዋል፡፡ አንድዬ ይርዳቸው፡፡

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር