ትምህርት ሚኒስቴርነት፤ በማማረር ወይስ በማባረር…! ?

ትምህርት ሚኒስቴርነት፤ በማማረር ወይስ በማባረር…! ?
መንጌ የነገረኝ ቀልድ ትቅደም፤
መንጌ ማለት አሉኝ ከምላቸው ጓደኞቼ ውስጥ አንዱ ነው፡፡ እሳት የላሰ የአራዳ ልጅ ነው፡፡ “ካራዳ ልጅ ጋራ አብረው ቢሰደዱ፤ ባይበሉም ባይጠጡ ስንቅ ይሆናል ቀልዱ”  የተባለለት ጨዋታ አዋቂ!
አንድ ሙዝ ነጋዴ ነበር አለኝ መንጌ…
እሺ…
ሙዙ ገበያ ሲያጣ ምን ያደርጋል መሰለህ…
እ…
የተሰቀለውን ያወርደዋል፡፡ መሬት የነበረውን መስቀያው ላይ ያንጠለጥለዋል፡፡ እንደርሱ ብቻ አይደለም፤ “ሙዝ አትፍዘዝ ተንቀሳቀስ…” ሲልም ያበረታታዋል… አለኝ፡፡
እኔ ፋራው የምጠይቀው ጥያቄ ነው እንጂ የሚገርመው… ከዛስ…  አልሸጥ ያለው ሙዝ ይሻጣል….  ወይስ ይንቀሳቀሳል…?
መንጌ ይስቃል… እርስዎም ይሳቁ፡፡
አቶ ሃይለማሪያም ደሳለኝ የሙዙ ነጋዴ ናቸው፡፡ የሱቁ ባለቤቶች “እስቲ ደግሞ ለአኬር፤ ሙዝ አትፍዘዝ ተንቀሳቀስ” ይበሉ … ብለዋችው ይሁን; በራሳቸው ተነሳሽነት እንጃ ሞዛዞቻቸውን ቦታ አቀያይረዋቸዋል፡፡ (ሙዛ ሙዞቻቸውን ማለቴ ነው….)
አቶ ሬድዋን የኮሚኒኬሽን ሚኒስቴር… ተደርገዋል፡፡ የምርም ስለ ኢህአዴግዬ ዋይ ዋይ ለማለት እርሳቸው ሳይሻሏት አይቀሩም፡፡  ምክንያቱም አቶ በረከት ስምዖን ቻርጅ እንዳለቃቸው በጣም ያስታውቃሉ፡፡ (ጢን… ጢን.. ማለት ከጀመሩ ቆይተዋል) ስለዚህ ነጋ ጠባ ስለ ድርጅታቸው በየአደባባዩ እየተከሰቱ “በላውድ ስፒከር” ሊጮሁላት አይቻላቸውም፡፡ እናም፤ ባትሪ ፉሉ አቶ ሬድዋን መተካታቸው ለዚህ ቦታ ትክክል ይመስለኛል፡፡
አቶ ወርቅነህ ገበየሁ የትራንስፖርት ሚኒስቴር… ይሄኛው ያስቃል፡፡  የሰውዬው የስራ ልምድ እኮ አስተኳሽነት ነው፡፡ እንግዲህ በዚህ የስራ ልምዳቸው እንደ ጥይት የሚተኳኮስ የትራንስፖርት ስርዓት ይዘረጉልናል፡፡ ብለን ተስፋ እናድርግ እንዴ…!
በእውነቱ ቀልድ በብዛት የሆነበት ፓርላማ ነውኮ ያለን! ለአስፋልቱ የተሸለ ስርዓት ዝርጋታ “የሰው ያለህ” በሚለው የትራንስፖርት ችግር ላይ፤ የሰው ልጅን አስፋልት ላይ በጥይት ሲዘረጉ የነበሩ ሰውዬ ሲሾሙ አስደናቂ ታሪክ ላይ መመዝገብ ያለበት ታሪክ ነው!
አቶ ሽፈራው ሽጉጤ የማፈናቀል ጥበባቸውን  ለምን እንደተፈለገ እንጃ ይዘውት ወደ ትምህርት ሚኒስቴርነት ከች ብለዋል፡፡ ይቺ ስልጣን ከአቶ ደመቀ በምን ምክንያት “መንጩ” እንደተደረገች እንጃ… አቶ ደመቀ ስራ በዝቶባቸው ይሆናል እንዳንል… እርሳቸው ለራሳቸው አንድ ሶስተኛ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ናቸው፡፡ እንኳንስ ለአንድ ሶስተኛ ምክትልነት እና ያኔ አቶ ሃይሌ ብቻቸውን ሙሉ ምክትል  ጠቅላይ ሚኒስቴር ሆነው እየሰሩ፤ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትርነቱንም “ቀጥ” አድርገው ይዘውት ነበር፡፡  ታድያ አንድ ሶስተኛ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስቴርነትና የትምህርት ሚኒስቴርነት ምን አላት…
የሆነ ሆኖ የትምህርት ሚኒስቴርነቱን ቦታ አቶ ሃይሌ ለአቶ ሽፈራው ሽጉጤ እነሆ በረከት ብለዋቸዋል፡፡ እኛም እየጠየቅን እንገኛለን፤ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ባለፈው በክልላቸው ያማረሯቸውን እና ከክልላቸው ያባረሯቸውን ሰዎች እያስታወስን፤
የትምህርት ሚኒስቴርነት ብቃት የሚለካው በማማረር ወይስ በማባረር… ! ? እንላለን፡፡
ችግሩ መንግስታችን የፈለገ ጥያቄ ቢጠየቅ መልስ መስጠት መልስ የመጥራት ያክል ይከብደዋል እና መልሱ “መ” ነው፡፡  መ- መልሱ የለም፡፡
አረ እረስቼያቸው እኒያ ፍትህ ሚኒስቴርም በምን እንደወረዱ ሳይነገረን ሌላ በምን እንደመጡ የማናቃቸው ሰውዬ ተሸሙብን አይደል!
ለማንኛውም ሹመኞቹ ቢቀያየሩም ባይቀያየሩም ዋናው የድርጅታችን ልብ መግዛት ነው እና ድርጅታችን ኢህአዴግ እኛን ቦንድ ግዙ እንደምትለን ሁሉ፤ እኛም እባክሽ ልብ ግዢ እንላታለን! ቦንዱ ለራሳችሁ ብዬ ነው እንደምትለንም ሁሉም፤ እኛም ልብ ግዢ ማለታችን ለራስሽ ብለን ነው እንላታለን!

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር