“ኢህአዴግ ጠንካራ የተቃዋሚ ፓርቲ ለማግኘት አልታደለም”


  • በግጥም ምሽቶች መታደም ትልቅ ደስታ ይሰጠኛል------
  • ኢህአዴግ ለተቃዋሚዎች ድጋፍ ነፍጓል ብዬ አላስብም-----
  • ኢትዮጵያ ከፓርቲዎች ፖለቲካ በላይ ልትወሰድ ይገባል-----
አቶ ህላዌ ዮሴፍ በብአዴን መስራችነታቸው፣ በትጥቅ ትግሉ ወቅት ድርጅቱ ለቅስቀሳ ይጠቀምባቸው የነበሩትን መዝሙሮች ግጥምና ዜማ በመድረስ እንዲሁም በበርካታ ቀስቃሽና ወቅታዊ የግጥም ሥራዎቻቸው ይታወቃሉ፡፡ የአማራ ልማት ማህበርን (አልማ) ለሃያ አመታት በሥራ አስኪያጅነትና በቦርድ ሊቀመንበርነት አገልግለዋል፡፡ በአምባሳደርነት ተመድበው ከሚሰሩበት እሥራኤል አገር ፤ ለብአዴን ድርጅታዊ ስብሰባና ለዘጠነኛው የኢህአዴግ ጉባዔ ወደ አገራቸው በመጡበት ወቅት ከጋዜጠኛ መታሰቢያ ካሳዬ ጋር በባህርዳር ከተማ ቃለምልልስ አድርገዋል፡፡ ብአዴን በቅርቡ ባካሄደው ድርጅታዊ ስብሰባ ወቅት ያደረገው መሰረታዊ ለውጥ አለ? በድርጅቱ ውስጥ በፖሊሲ፣ በፖለቲካ አቋምና መስመሮች ዙሪያ የተደረገ ለውጥ የለም፡፡
በአመራር ደረጃ ከነበሩት 65 የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት መካከል 20 የሚሆኑትን ቀይረናል፡፡ ይህ ደግሞ ሁሌም በጉባኤው ወቅት የሚከናወን ጉዳይ ነው፡፡ በተረፈ ድርጅቱ በሥራ አፈፃፀሙና አባላቱን በማጠናከሩ ረገድ ራሱን እያሻሻለ መሄዱንና በአስተማማኝ ጥንካሬ ላይ መድረሱን አረጋግጠናል፡፡ በአንዳንድ ጉዳዮች ዙሪያ መሻሻልና መስተካከል ይገባቸዋል ያልናቸውን ጉዳዮችም አንስተን ተወያይተናል፡፡ በመልካም አስተዳደር ረገድ በፌደራል ደረጃ በተደጋጋሚ እንደሚነሳው፣ በአማራ ክልልም አንዳንድ ትኩረት ሰጥተን ልናያቸው የሚገቡ ጉዳዮች እንዳሉም አይተናል፡፡ በእኔ አስተያየት ድርጅቱ በጤናማ አቅጣጫ እየተጓዘ ነው፡፡ ስለመጪው ምርጫ ምን አስተያየት አለዎት? ኢህአዴግ ምርጫውን ህዝብ የሚያምንበት ምርጫ ያደርገዋል የሚል እምነት አለኝ፡፡
ግምት አይደለም እምነት ነው ያለኝ፡፡ ካለፉት ውጤቶች ብዙም የተለየ ነገር ይመጣል ብዬ አልገምትም፡፡ ከፍተኛውን ድምፅ አግኝተን እንመረጣለን ብዬ አስባለሁ፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ገዢው ፓርቲ አላሰራ እንዳላቸውና የፖለቲካው ምህዳሩ እየጠበበ መምጣቱን ይናገራሉ፡፡ እርስዎ በዚህ ጉዳይ ምን ይላሉ? ተቃዋሚ ፓርቲዎቹ ኢህአዴግ የፈለጉትን ያህል ቢደግፋቸው፣ሁኔታዎችን ቢያመቻችላቸው፣ እንደምንጣፍ ቢነጠፍላቸው ውስጣቸውን እንዴት አድርገው ማጠንከር እንዳለባቸው ካልተገነዘቡ ዋጋ ቢስ ጉዳይ ነው፡፡ ወሳኙ ነገር ራሳቸውን ማጠንከራቸው ነው፡፡ ኢህአዴግ ድጋፍ ነፍጓቸዋል ብዬም አላስብም፡፡ ኢህአዴግ እንደአለመታደል ሆኖ ካጣቸው ፀጋዎች መካከል ጠንካራ የተቃዋሚ ፓርቲ አንዱ ነው፡፡ በጭፍን ለተበላሸ ማንኛውም ነገር ሁሉ ኢህአዴግን ተጠያቂ ማድረግ ይፈልጋሉ፤ በሰሜን ለነፈሰው ንፋስ፣ በምሥራቅ ለጣለው ዝናብ ሁሉ ተጠያቂው ኢህአዴግ ነው ብለው ያስባሉ፡፡ መልካም ነገር ሲሰራ ግን እነዚያን መልካም ነገሮች መመልከቻ አይን ያጣሉ፡፡ አንዳንደቹ ደግሞ ተቀራርቦ ለመሥራት ይሞክሩና አቅም ያጣሉ፡፡ ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ በማግኘቱ ረገድ ኢህአዴግ ያን ያህል የተሳካለት ነው ብዬ አልገምትም፡፡
መልካሙን ነገር በመልካምነቱ እየወሰዱ ኢህአዴግ መወቀስ ባለበት ጊዜ ደግሞ ጠንከር ብለው (ክሪቲካሊ) እየወቀሱ ተባብሮ መስራቱ ዋንኛ ጉዳይ መሆን ይገባው ነበር፡፡ ዞሮ ዞሮ ኢትዮጵያ ከፓርቲዎች ፖለቲካ በላይ ልትወሰድ ይገባል፡፡ ከጠባብ የፓርቲ ፍላጐቶች በላይ ትልቅ አገር አለን ብሎ የማሰብ ነገር ይጐድላል፡፡ በህጋዊና በሰላማዊ መንገድ ተቃዋሚዎቹ በምርጫውም ሆነ በአገሪቱ የፖለቲካ ጉዳዮች ውስጥ ቢሳተፉ ደስ ይለኛል፡፡ አንሳተፍም ካሉ ደግሞ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡ ፈረስን ወንዝ ይወስዱታል እንጂ አስገደድው ማጠጣት አይቻልም፡፡ ከአቶ መለስ ህልፈት በኋላ አብዛኛው ባለሥልጣን ዘንድ አንድ የተለመደ አባባል አለ - “የአቶ መለስን ራዕይ ለማስፈፀም…. በአቶ መለስ ሌጋሲ እየተመራን…” ሲባል ምን ማለት ነው ? የአቶ መለስ ራዕይ ብለን የምናስቀምጣቸው ግልፅ የሆኑት ነገሮች ምን ምንድናቸው? አቶ መለስ በህይወት በነበረበት ወቅት ይህቺን አገር ከችግር አረንቋ ውስጥ ለማውጣት የነበረው እሳቤ ሰፊ መሆኑን የሚያመለክቱ፣ በጣም ግልፅ የሆኑ ፖሊሲና ስትራቴጂዎችን ነድፏል፡፡ ከእነዚህ መካከል ጥቂቶቹን ለመግለፅ ያህል አገሪቱ በአንድ ወቅት በስልጣኔና በታሪኳ የገነነች አገር ነበረች፡፡ ቀጥላም ከመሬት በታች የወደቀች ደካማ አገር ሆናለች፡፡ ህዝቦቹም አሳፋሪና አዋራጅ በሆነ የድህነት ሁኔታ ውስጥ ገብተዋል፡፡ ይህ መለወጥ አለበት፡፡
መለወጥም ይችላል፡፡ ለዚህም ጠንክረን መስራት አለብን፡፡ ከድህነት ጋር እንድንቆራረጥ ያስቀመጣቸው ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ዋነኞቹ ናቸው፡፡ የገጠርና ግብርና ልማት ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች እሱ የነደፈው ነው፡፡ የኢንዱስትሪ ልማት ፖሊሲው፣ የአቅም ግንባታ ፕሮግራሞችና ስትራቴጂዎች፣ የውጭ ጉዳይና የደህንነት ፖሊሲዎች፤ ኢትዮጵያ ምን አይነት ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ሊኖራት ይችላል የሚሉት ሁሉ እሱ ነው የቀረፃቸው፡፡ እነዚህ በመሰረቱ ኢትዮጵያ ካለችበት ጐስቋላ ሁኔታ አውጥተው ከሌሎች ያደጉ አገራት ተርታ እንድትሰለፍ የሚያስችሏት ነገሮች ናቸው፡፡ ሁለተኛ ጠንካራ የሥራ ባህል እንዲኖር፣ በአዲስ መንገድ ማሰብ እንድንችል ማድረጉ ማንነቱን የሚገልፁ ሁኔታዎች ናቸው፡፡ ህዝቡ በተደራጀ ሁኔታ በስፋት እንዲንቀሳቀስ፣ ስራ እንዲለምድ፣ ዲሲፒሊን እንዲለምድ መለስ በጣም የተለየ አርአያ የሚሆን ሰው ነው፡፡ በስራ ባህርይው፣ አለምን ለማወቅና ለመገንዘብ ባደገው ጥረት፣ በተመራማሪነቱ፣ ከአሁን ቀደም ከነበሩ የኢትዮጵያ መሪዎች ይለያል፡፡ ከዚህም በላይ በአለም ደረጃ ካሉና ጥቂት ምርጥ ተብለው ከሚጠቀሱ ተርታ የሚሰለፍ መሪ ነው፡፡ ህልፈቱም ድንገት የመጣ ነገር ነው፡፡
ቀደም ብለሽ እንደጠየቅሽኝ ኢህአዴግ ውስጥ ባለ ባህልና እሱም ስለራሱ የመፃፍ ፍላጐት ያልነበረው ሰው ስለነበር፣ የመለስ ጉዳዮች በደንብ ጐልተው አልወጡም፡፡ ስለዚህም ሰው አጠቃላይ ግንዛቤ ይዞ “የመለስን ሌጋሲ ይዘን እንጓዛለን” በማለት በሚፈለገው ደረጃ ሊተረጉመው ባይችልም አይፈረድበትም፡፡ በተገቢው መንገድ ባይገልፀውም ግን ዘርዘር አድርጐ ትውልዱ እንዲያውቅ መደረግ አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ የኢትዮጵያና የእስራኤል ግንኙነት ምን ይመስላል? የሁለቱ አገራት ግንኙነት በጥሩ ሁኔታ ላይ ነው ያለው፡፡ በእነሱም ሆነ በእኛ በኩል ለሺህ አመታት የቆየ ትስስር እንዳለን እናምናለን፡፡ ኢትዮጵያ በምሥራቅ አፍሪካ ብሎም በአፍሪካ አህጉር ሰፊ ሚና እንዳላት ይቀበላሉ፡፡ እኛም በበኩላችን እስራኤል ምንም እንኳን ከፍልስጥኤማውያን ጋር ያላት ችግር አሁንም ያልተፈታ ቢሆንም ይህ ጉዳይ መፍትሄ ካገኘ፣ አገሪቱ ለአለም ልታበረክት የምትችለው አስተዋፅኦ ከፍተኛ እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡ በዚህ ሁኔታ ተረዳድተን መቀጠል የምንችልበትን ሁኔታ እያመቻቸን መሄድ እንዳለብን አውቀን እየሰራን ነው፡፡ ከዚህም በላይ ደግሞ እኛንና እነሱን የሚያቆራኘን የቤተእስራኤላውያኑ ጉዳይ አለ፡፡ ቤተእስራኤላውያኑ አሁን በምን ሁኔታ ውስጥ ነው ያሉት? አገራችን ብለው በእስራኤል ውስጥ እየኖሩ ነው፡፡ ሁለት ነገሮች እነሱን ይገልጿቸዋል፡፡
ብዙዎቹ ከኢትዮጵያ ጋር ላላቸው ቁርኝትና ትስስር ትልቅ ቦታ ይሰጣሉ፡፡ ሁለተኛ ደግሞ ለይሁዲ ማንነታቸው ደግሞ የሚሰጡት ቦታ እንደዚሁ ትልቅ ነው፡፡ በየትኛውም አገር እንደሚታየው ሁሉ እነሱም አልተፈቱልንም የሚሏቸው ችግሮች አሏቸው፡፡ እንገለላለን፣ ሙሉ እድል አናገኝም የሚሉ ነገሮች ይሰማሉ፡፡ ነገር ግን እስራኤል ዲሞክራት አገር ስለሆነች እነዚህን ጥያቄዎቻቸውን በዲሞክራሲያዊ መንገድ አቅርበው ከመንግስታቸው ጋር እየተወያዩና እየፈቱ ይኖራሉ፡፡ አልፎ አልፎ ደግሞ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ብቅ የሚሉ ፖለቲከኞች አሉ፡፡ ኢትዮጵያውያን በተለያዩ ዘርፎች እየተሳተፉ ነው፡፡ አሁን ኢትዮጵያ ውስጥም ያሉት የእስራኤል አምባሳደር ኢትዮጵያዊ ይሁዲ ናቸው፡፡ በፓርላማ ውስጥ የተመረጡም አሉ፡፡ እየተሳካላቸው ያሉም አሉ፡፡ በየትኛውም አገር እንዳለው በአማካይ የኑሮ ደረጃ ውስጥ ያሉም አሉ፡፡ የሥነፅሁፍ ሰው ነኝ ብለው ያስባሉ? ብዙ ሰዎች እንደዛ ብለው ያስቡኛል፡፡
እኔ ግን ራሴን እንደዛ አልገልፀውም፡፡ ራሴን ያን ያህልም እንደፀሐፊ ወይም እንደሥነፅሁፍ ሰው አልወስደውም፡፡ እኔ ራሴን እንደገጣሚ ወይንም እንደፀሐፊ ከቆጠርኩኝ ትላልቆቹን ምን ብለን ልንጠራቸው ነው፡፡ ግን እሞክራለሁ፡፡ ወይም ሞክሬአለሁ ብል ይቀለኛል፡፡ በምን ዙሪያ መፃፍ ይወዳሉ? ግጥሞችን ነው እፅፍ የነበረው፡፡ መደበኛ ግጥሞችንና የመዝሙር ግጥሞችን ፅፌአለሁ፡፡ በትጥቅ ትግሉ ወቅት በጣም ለአጭር ጊዜ ነበር እፅፍ የነበረው፡፡ ከ1974 እስከ 70ዎቹ መጨረሻ አካባቢ ባሉት ጊዜያት በስፋት እፅፍ ነበር፡፡ ከሥራዎችዎ መካከል ለህትመት የበቁ አሉ? ከግጥሞቼ አንዳንዶቹ “ሶረኔ” የሚል ርእስ ባላት መፅሀፍ ላይ ከሌሎች ታጋይ ገጣሚያን ግጥሞች ጋር ታትመውልኛል፡፡ ከእነፍሬህይወት አያሌው፣ ከነመዝሙር ፈንቴ፣ ከነታደሰ ካሳ ግጥሞች ጋር ማለት ነው፡፡ የዘፈንና የመዝሙር ግጥሞቹ ደግሞ “73” በምትል አንዲት ትንሽ የኪስ መፅሃፍ የዛሬ 10 አመት ገደማ ወጥቷል፡፡
ምን ያህል የመዝሙር ግጥሞች ፅፈዋል? ሃያ አምስት አካባቢ ይሆናሉ፡፡ የመዝሙርና የዘፈን ግጥሞቼ፡፡ የራስዎን ሥራዎች ለማሳተም ሃሳብ የለዎትም? ከተሳካ በዚህ አመት መጨረሻ ካልሆነልኝም በቀጣዩ አመት መጀመሪያ ላይ ለማሳተም አስቤአለሁ አሁንስ ይፅፋሉ? አሁን አልፅፍም፡፡ ለምን? እነዛን ግጥሞችና መዝሙሮች የፃፍኩበት ጊዜ በጣም የተለየ ወቅት ነበር ለእኔ፡፡ አንድን ወቅት ሊገልፁ የሚችሉ ግጥሞችና መዝሙሮች ናቸው፡፡ ያ ወቅት ለእኔ በጣም የተለየ ትርጉም ነበረው፡፡ አሁን ያኔ የነበረው መንፈሴ ተመልሶ ይመጣል ብዬ አላስብም፡፡ ስለዚህ ብልጭ ብሎ እንደጠፋ ነገር አድርጌ ነው የምወስደው፡፡ ሙሉ በሙሉ ጠፍቷል አይደለም፡፡ ውስጤ አለ፡፡ ግን ያኔ ከነበረው በላይ እሰራለሁ ብዬ አልገምትም፡፡ ግን ደግሞ የዚህ ፍርሃት ብቻም አይደለም፤ ዛሬ የማያፅፈኝ ትንሽ ስንፍናና ዳተኝነትም ሳይሆን አይቀርም፡፡
ከአገር ሲርቁ ብቸኝነቱ እንደው በል በል… ፃፍ ፃፍ የሚል ስሜት አያሳድርም? ብዙ ታላላቅ ፀሐፊዎች በዲፕሎማትነት ዘመናቸው ብዙ ነገር ፅፈዋልና… ሰው ከውጭ እንደሚያስበው የእኛ ሥራ ያን ያህልም ብቸኝነትን የሚያሳስብሽና የሚያዝናና ጊዜ እንዲኖርሽ አያደርግም፡፡ እንደሚታወቀውና አሁን እንዳልሽው የእኛ ታላላቅ ፀሐፊዎቻችን ዲፕሎማት ሆነው ውጪ አገር በነበሩባቸው ጊዜያት ፅፈዋል፡፡ ከእነሱ ጋር ራሴን ለማወዳደር ሳይሆን የአሁኑ የሥራ ባህርይ ከቀደምቱ በጣም የተለየ መሆኑን ለመግለፅ ነው፡፡ በአሁኑ ዘመን ከዚህ አገር አምባሳደር ወይም ዲፕሎማት ሆኖ ወደ ውጪ አገር የሚላክ ሰው ዘና ብሎ ብዙ ጊዜ ተርፎት የሚኖር አይደለም፡፡ በጣም ውጪ ነፍስ ግቢ ነፍስ ያለበት ህይወት ነው፡፡ በእርግጥ አገር ውስጥ ያሉት ወንድሞቻችን በሚደክሙት መጠን እንደክማለን ማለት ላይሆን ይችላል፡፡ ግን ያን ያህል የሚያላውስ ጊዜ የለም፡፡
የምናመጣው ውጤት በስኒም ይሁን በእንቅብ፣ ቋቱ ቢሞላም ባይሞላም ላይ ታች ስንል ነው የምንውለው፣ ኢንቨስትመንት ማምጣት አለብን፣ የቴክኒክና የፋይናንስ ድጋፍ ለማግኘት ጥረት ማድረግ አለብን፣ ከተመደብንበት አገር መንግሥት ጋር የአገራችን ግንኙነት እንዲጠናከር መሥራት አለብን፣ በውጭ አገር ያሉ ኢትዮጵያውያንን ለታላቁ ህዳሴ ግድብ ማስተባበር ወዘተ. በርካታ ነገሮች አሉ፡፡ በሥራ አይን እንደ አገር ውስጥ ከባድ ነው ባይባልም የሚያዝሃና ትርፍ ጊዜ አለ ብሎ ማሰብ አይቻልም፡፡ እዛ ላይ ደግሞ ሁሌም የማትቀረው ያቺ ዳተኝነትም አለች፡፡ ያም ሆኖ ግን ማሰቤ አልቀረም፡፡ ቅድም እንዳልኩሽ ከቻልኩ በዚህ ዓመት መጨረሻ፣ ካልሆነልኝም በቀጣዩ አመት መጀመሪያ ላይ ቢያንስ እነዚህን ግጥሞችና መዝሙሮች ሰብስብ አድርጌ አወጣቸዋለሁ ብዬ አስባለሁ፡፡ የራስዎን ታሪክ ለመፃፍ ሃሳብ የለዎትም? የራሴን ታሪክ የመፃፍ ጉዳይ ያን ያህልም የሚያሳስበኝ አይደለም፡፡ የራሴን ታሪክ የመፃፍ ፍላጐቱም የለኝም፡፡ እኔ የግሌ የምለው ታሪክ የለኝም፡፡ አንዳንድ ጊዜ በእርግጥ አንዳንዶቹ የራሳቸውን ታሪክ በተለየ በራሳቸው መንገድ ሲፅፉት የተለየ ስሜት ይሰጣል፡፡ ምክንያቱም ራሳቸውን ከማንም በላይ መግለፅ የሚችሉት ራሳቸው ናቸውና፡፡
የራስን ምስክርነት መስጠት ጠቀሜታ ይኖረዋል፡፡ ነገር ግን ሁላችንም ታጋዮች ስለራሳችን ከምንፅፈው ይልቅ ስለትግላችን ብንፅፍ የበለጠ የህይወታችንን ትልቁን ክፋይ ማሳየት እንችላለን ብዬ እገምታለሁ፡፡ ያንን የሚፅፉ ሰዎች ተሳስተዋል ለማለት አይደለም፤ ሊፅፉ ይችላሉ፡፡ ምርጫቸው ነው፡፡ ጥሩም ነው፡፡ እኔ ግን እንደዛ አልመርጥም፡፡ ምናልባት በታሪኩ ውስጥ ስለማንነቴ ሊገለፅ ይችላል ብዬ እገምታለሁ፡፡ ወቅታዊ ሁኔታዎችን በሥነፅሁፍ በማሳየቱ ረገድስ፣ ችግሮችን በኪነጥበባዊ መንገድ ለመግለፅ --- አይሞክሩም? አንድ ወጣት ተማሪ በ18 እና በ19 አመቱ ከሌሎች ወንድም እህቶቹ ጋር በጣም ትልቅ ሃሳብ ይዞ እህቶቹን ወንድሞቹን፣ ወላጆቹን፣ ዘመድ ጓደኞቹን ትቶ፣ ሁሉም ይቅርብኝ፣ ይህንን አስከፊ ስርዓት መታገል አለብኝ ብሎ፣ ከተማውን ጥሎ ገጠር ከገባ በኋላ፣ ሁሉንም ነገር አጥቶ ትምህርቱን የቤተሰብ ፍቅር፣ ትዳሩን… ሊመጣ የሚችለውን የወደፊት ተስፋውን ሁሉ አጥቶ፣ተስፋዬ የሚገኘው በዚህ ትግል አማካኝነት ከአስከፊው ሥርዓት ነፃ ከሚወጣው ህዝብ ጋር ነው ብሎ ባሰበበት ወቅት… ሁሉ ነገር እንደ ሸክላ ፍርክስክስ ሲል እና ተስፋ ሲታጣ፤ ይህ ቀን ያልፋል ምናልባትም ወደፊት ብሩህ ቀን ይኖራል የሚል መንፈስ ስለነበረኝ፣ ያኔ የተለየ አቅም (ኢነርጂ) ነበረኝ፡፡
በእርግጥ ደርግን ከማቸነፍ የበለጠ ትልቅ ነገር አለ፤ አሁንም ቢሆን ድህነቱ ብዙ ያፅፋል፡፡ ይህቺን አገር ከአለም አገራት እኩል እንድትሆን የማድረጉ ጉዳይ ብዙ ያፅፋል፤ መፃፍም ይገባል ብዬ አስባለሁ፡፡ እናስ ምን እንጠብቅ? በዛ ታሪካዊ ወቅት ፍንጥቅ ብለው ወጥተው፣ ሰው የወደዳቸውን አንዳንድ ግጥሞችና መዝሙሮችን ያየ ሰው ቢጠብቅ ላይገርም ይችል ይሆናል፡፡ ሰዎች ምን እንጠብቅ ሲሉ፤ እመጣላችኋለሁ ይህንን ጠብቁ ማለቱ ትንሽ ከመጠናችን በላይ የሆነ ጫማ ማድረግ ይሆናል፡፡ የእኛ አገር የትሁት ህዝብ አገር ነች፡፡ አንዳንዴ ደግሞ ስድስት መስመር ግጥም ፅፎ የፃፈበትን ዘመን ራሱ እንኳን በማያስታውስበት ሁኔታ ውስጥ እያለ ለምን ደራሲ ወይም ፀሐፊ ተውኔት አላላችሁኝም እያለ የሚፎክር ብዙ ሰው አለ፡፡ ስለዚህ ከእኛ በበለጠ የሚጠበቅባቸው ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እኛም ደግሞ በአቅማችን ወይም በልካችን የምናደርገው ነገር ይኖር ይሆናል፡፡
የእኔ ጉዳይ ቅድም እንዳልኩሽ ነው፤ አንድ ወቅት የፈጠረው ነገር ነው፡፡ ከቻልኩ አደርገዋለሁ፤ ካልቻልኩ ደግሞ ከእኔ የተሻለ ማድረግ የሚችሉ ብዙ ሰዎች ስላሉ እነሱ ያደርጉታል ብዬ አስባለሁ፡፡ አሁንም ፃፍ ፃፍ ማሰኘቱ ግን አይቀርም፡፡ ብዙ ሊፃፍበት የሚገባ ጥሬ ሀብት እንዳለንም ይሰማኛል፡፡ ለራሴ እየፃፍኩ የማስቀምጣቸው ትናንሽ ነገሮችም አሉኝ፡፡ ምናልባት እነሱ ተጠረቃቅመው አንድ ነገር ይሆኑ ይሆናል፡፡ እንግዲህ ወደፊት… በራስ ሆቴል በሚካሄዱ የግጥም ምሽቶች ላይ አልፎ አልፎ ይታዩ ነበር፡፡ ሌሎች የኢህአዴግ ባለስልጣናት በእንዲህ አይነት ኪነጥበባዊ ፕሮግራሞች ላይ ይሳተፋሉ? በግጥም ምሽቶች ላይ ጊዜውና ሁኔታው በፈቀደልኝ ጊዜ ሁሉ መሳተፍ ደስ ይለኛል፡፡ እንዳልሽው በራስ ሆቴል ፕሮግራሞች ላይ አልፎ አልፎ የመሳተፍ እድሉን አግኝቼአለሁ፡፡ በጓድ መለስ ህልፈት ወቅት ወደ ኢትዮጵያ መጥቼ ቶሎ ተመልሼ አልሄድኩም ነበር፡፡
እናም በዛን ወቅት በነበሩኝ ጊዜያት እነዚያን የግጥም ምሽቶች ታድሜባቸው ነበር፡፡ እነጌትነት እንየው፣ እነነቢይ መኮንን… የመሳሰሉ ታላላቅ ገጣሚያንን ግጥሞች ለመስማት እድሉን አግኝቼአለሁ፡፡ እንደውም ግጥሞቹን በሞባይሌ ቀርጬ አሁን አንዳንዴ እየሰማሁ እዝናናባቸዋለሁ፡፡ በግጥም ምሽቶች ላይ መገኘት ለእኔ ትልቅ ደስታን ይሰጠኛል፡፡ አንዳንድ የድርጅቱን ባለስልጣናትና አመራሮች በፕሮግራሞች ላይ እንዲገኙ በመጋበዝ ይዣቸው የሄድኩበት አጋጣሚ ነበር፡፡ ሌሎቹም ባላቸው አነስተኛ የእረፍት ጊዜም ቢሆን ቤተሰቦቻቸውን እየያዙ በእንዲህ አይነት ኪነጥበባዊ ፕሮግራሞች ላይ ቢሳተፉ ጥሩ ነገር ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ ለብዙዎቹም ይህንኑ ሃሳቤን አካፍላለሁ፡፡ ኢህአዴግ በኪነጥበቡ ዘርፍ ያለውን አቋም እንዴት ይገልፁታል? ኢህአዴግ በተለይም በትጥቅ ትግሉ ወቅት የነበሩትና ትግሉን የጀመሩት እንደነ ህወሐት፣ ብአዴን፣ በኋላም ኦህዴድ በእርግጠኝነት እንደማውቀው በውስጣቸው እጅግ ከፍተኛ የሆነ የኪነጥበብ ንቅናቄ የነበራቸው ድርጅቶች ናቸው፡፡ በትጥቅ ትግሉ ወቅት ለቅስቀሳ የምንጠቀምባቸው ግጥሞችና መዝሙሮች በወቅቱ ይፈጥሩት የነበረውን ስሜት መግለፁ ከባድ ነው፡፡ በትግል ወቅት በየጊዜው ስብሰባዎችን ስናካሂድ፣ በስብሰባው ማጠቃለያ ወቅት የተለያዩ ስሜት ቀስቃሽ ግጥሞችና መዝሙሮች ይቀርቡ ነበር፡፡
ይህ ሁኔታ ድርጅቱ ለኪነጥበቡ ዘርፍ ያለውን ፍቅርና ስሜት ያሳያል ብዬ አስባለሁ፡፡ ድርጅቱ አሁንም ለኪነጥበቡ ዘርፍ ያለው አቋም ጥሩና ዘርፉን ለማሳደግ የሚረዳ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ ሳላደርገው ቀረሁ ብለው የሚቆጩበት ነገር አለ? በሥራ ረገድ ከትጥቅ ትግሉ ጀምሮ የምችለውን አስተዋፅኦ ሁሉ አድርጌ አለሁ የሚል ግምት አለኝ፡፡ አልማን ለ20 አመታት በሥራ አስኪያጅነትና በቦርድ ሊቀመንበርነት አገልግዬ ውጤታማ ተግባር አከናውኛለሁ፤ ግን የሚቆጭህ ካልሽኝ ብዙ ማንበብ ነበረብኝ ብዬ አስባለሁ፡፡ እዚህ አካባቢ ቅር ይለኛል፡:

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር