የአውሮፓ ህብረት ባለስልጣናት በኢትዮጵያ የህዝቡ ነጻነት እንዲከበር ጠየቁ


ሚያዚያ  ፲፪ (አስራ ሁለት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የአውሮፓ ህብረት የፓርላማ መሪ ማርቲን ሹልትዝ ፣ የኮሚሺኑ ፕሬዚዳንት ሚስተር ጆሴ ማኑኤል  የጎበኙት ጠ/ሚኒስትር ሀይለማርያም ደሳለኝ ባሮሶ እና የካውንስሉ ፕሬዚዳንት ሚ/ር ቫን ሩምፒ፣ ኢትዮጵያ በእሰር ላይ የሚገኙትን ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋንና ርእዮት አለሙን ጨምሮ ሌሎች የፖለቲካ እስረኞች እንዲፈቱ፣ በአገሪቱ ውስጥ የሀዝቡ ነጻነት እንዲከበር፣ የጸረ ሽብር ህጉ እንዲሻሻል፣ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን ለመቆጣጠር የወጣው ህግ እንዲከለስ ለጠ/ሚ ሀይለማርያም ደሳለኝ ጥያቄ አቅርበዋል። ባለስልጣናቱ ጥያቄውን ያቀረቡት አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ የአውሮፓን ህብረት በጎበኙበት ወቅት ነው።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ሰላም ለማስከበርና ሽብረተኝነትን ለመዋጋት እንዲሁም ድህነትን ለመቅረፍ ለማታደርገው ጥረት እውቅና እንደሚሰጡ የገለጡት ባለስልጣናቱ፣ ይሁን እንጅ  ትክክለኛ ልማት የሰው ልጆች ነጻነት ሳይከበር የሚመጣ ባለመሆኑ ፣ መንግስት የዜጎቹን ነጻነት እንዲያከበር ጠይቀዋል።
የኮሚሺኑ ፕሬዚዳንት ሚ/ር ባሮሶ የሰብአዊ መብቶች ሁሉም የሰው ልጆች ሊያገኙዋቸው የሚገቡ አለማቀፍ መብቶች መሆናቸውን ለአቶ ሀይለማርያም ገልጸውላቸዋል። የካውንስሉ ፐሬዛድንት በበኩላቸው “ የማህበራዊ ልማት ስኬት የሚለካው በጠንካራና ግልጽ በሆነ ማህበረሰብ እንዲሁም መሰረታዊ የሆኑ የሰው ልጆች መብቶች ሲከበሩ ነው በማለት ተናግረዋል፡
አቶ ሀይለማርያም በኢትዮጵያ ውስጥ ዲሞክራሲያዊ ስርአት እንዲሰፍን፣ የዜጎች መብቶች አንዲከበሩና የሲቪክ ማህበረሰቡ ሚና አንዲጎለብት ጥረት እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።
ሶስቱም የ አውሮፓ ህብረት ባለስልጣናት በኢትዮጵያ የዲሞክራሲና የሰብአዊ መብቶች አያያዝ ችግሮች ላይ ተመሳሳይ አቋም መያዛቸው  በኢትዮጵያ ውስጥ ለሚካሄደው የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ትኩረት መስጠት መጀመሩን እንደሚያመለክት የፖለቲካ ተንታኞች ይናገራሉ። ከአሁን በፊት የህብረቱ ኮሚሽንና ካውንስሉ በኢትዮጵያ ለሚፈጸሙ የሰብአዊ መብቶች ትኩረት ሰጥተው እንደማያውቁ የሚታወቅ ሲሆን፣ ሚስ አና ጎሜዝ የሚሳተፉበት ፓርላማ በተደጋጋሚ የሚያወጣቸውን መግለጫዎች በተለይ ኮሚሽኑ  ውድቅ ሲያደርጋቸው ቆይቷል። ከአቶ ሀይለማርያም ጋር በነበረው ስብሰባ ሶስቱም የህብረቱ የስልጣን አካላት አንድ አይነት አቋም ማራመዳቸው ለሰብዊ መብቶች ተከራካሪ ድርጅቶች ስኬት ለኢትዮጵያ መንግስትም ከእንግዲህ የሰብአዊ መብቶችን እየጣሱ  ዝም ብሎ ሊታለፍ እንደማይችል ትምህርት የሚሰጥ ነው በማለት አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ።

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር