የመለስ ዜናዊ ፋውንዴሽን መሥራች ጉባዔ በተደበላለቀ ስሜት ተካሄደ

-    ፋውንዴሽኑ የሚገነባበት ቦታ ቢለይም ዲዛይኑ አልተጠናቀቀም
-    ፋውንዴሽኑ ከ50 ሚሊዮን ብር በላይ ስጦታ አግኝቷል
-    ለቤተሰቦቻቸው መኖሪያ ቤት ለመገንባት ዲዛይኑ እስከሚፀድቅ እየተጠበቀ ነው

ከሰባት ወራት በፊት በሞት የተለዩት የቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ መታሰቢያ “መለስ ዜናዊ ፋውንዴሽን” መሥራች ጉባዔ መጋቢት 29 ቀን 2005 ዓ.ም. በአፍሪካ ኅብረት የመሰብሰቢያ አዳራሽ በተደበላለቀ ስሜት ተካሄደ፡፡
ፋውንዴሽኑ የአቶ መለስ ዜናዊ እሴቶችና መርሆዎች፣ በቀጣይነት ከትውልድ ትውልድ ይሰርፁ ዘንድና ቀጣይነት እንዲኖራቸው፣ ሐሳቦችና ፕሮግራሞች የሚፈልቁበት ህያው ማዕከል ሆኖ እንዲያገለግል “መለስ ዜናዊ ፋውንዴሽን” በሚል ስያሜ፣ በተወካዮች ምክር ቤት ጥር 17 ቀን 2005 ዓ.ም. በአዋጅ እንዲቋቋም መደረጉ ይታወሳል፡፡

በመሆኑም ፋውንዴሽኑን በአዋጅ ለማቋቋም ላለፉት ሰባት ወራት ሒደቱን የሚመራና የሚያስተባብር የሌጋሲ ኮሚቴ እንዲቋቋም ተደርጎ፣ የተለያዩ ሥራዎችን በመሥራት፣ አዋጁ ከፀደቀ በኋላ መሥራች ጉባዔውን ለማካሄድ መቻሉን የገለጹት፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔና የሌጋሲው ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ካሣ ተክለብርሃን ናቸው፡፡

በአጭር ጊዜና ዝግጅት፣ በአገር ውስጥ ከአርሶ አደር እስከ ከፍተኛ ባለሥልጣናት፣ እንዲሁም ከአፍሪካ እስከ ዓለም ድረስ ላሉ የአቶ መለስ ወዳጆችና አድናቂዎች፣ የተደረገላቸውን ጥሪ አክብረው በፋውንዴሽኑ መሥራች ጉባዔ ላይ በመገኘታቸው ምሥጋናቸውን የገለጹት አቶ ካሣ፣ አቶ መለስ በሥራቸው በአኅጉር አቀፍና በዓለም አቀፍ ደረጃ ሲታወሱ እንደሚኖሩ ገልጸዋል፡፡ በእሳቸው የሕይወት ዘመን በአመራር ቦታ ላይ ለመድረስ የቻሉ ሰዎች ልብ ሊሉት የሚገባው ነገር እሳቸው በዘፈቀደ የደረሱበት ሳይሆን፣ በጥልቅ ጥናትና በማይቆም ከፍተኛ ምርምርና በየዕለት እንቅስቃሴዎቻቸውን ወደ ተግባር በመመንዘር መሆኑን የገለጹት፣ በፋውንዴሽኑ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ሲሆኑ፣ “የመለስን ራዕይ ጠንቅቆ መረዳት አሁን ላለነው የኢሕአዴግ አመራሮች ዝም ብሎ የተሰጠን ውርስ እንዳልሆነ ላሳስብ እፈልጋለሁ፤” ብለዋል፡፡

አቶ መለስ የንድፈ ሐሳብ ቀማሪና ቀያሽ ብቻ ሳይሆኑ፣ ሐሳቦችን በድርጅታቸው በተግባር ማዋል የቻሉ የምጡቅ ሐሳብ ባለቤት መሆናቸውን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም፣ ከትጥቅ ዘመን አንስቶ በፓርቲውና በመንግሥት ውስጥ ያከናወኗቸው ስፍር ቁጥር የሌላቸው አኩሪ ተግባራት መሆናቸውንና አስተምህሮዎቻቸውን ዘርዝሮ ማስቀመጥ አስቸጋሪ መሆኑን አውስተዋል፡፡ ከለጋ ዕድሜ አንስቶ ሕይወታቸው እስካለፈበት ዕለት ድረስ ምንም ዕረፍት የማያውቁት አቶ መለስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረግ በሚችሉበት ዘመናቸው ላይ ሕይወታቸው ማለፉ አይደለም ኢትዮጵያውያንንም ሆነ የዓለምን ሕዝብ ያሳዘነ በማለት የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በርካታ አኩሪ ተግባራትን መፈጸማቸውን፣ ታግለው ማታገላቸውን፣ መምራታቸውን፣ አገርና ሕዝብን ከዴሞክራሲ ዕጦትና ድህነት የሚወጡበትን መንገድ ቀይሰው ያለፉ መሪ እንደነበሩ ተናግረዋል፡፡

አቶ መለስ ለሰፊው ሕዝብ ጥቅም የቆሙ በመሆናቸው፣ ኪራይ ሰብሳቢነትን አምርረው የታገሉና በድርጅትም ሆነ በሕዝብ ዘንድ ተቀባይነት በማግኘታቸውም በላይ በዕውቀት፣ በጥበብና ፍፁም በሆነ ዴሞክራሲያዊነት በመመሥረት በሰጡት አመራር እጅግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርከተው ያለፉ መሪ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ተዝቆ የማያልቀውን ዕምቅ ዕውቀት ለቀጣይ ታሪክ ምርምር ለማዋል ፋውንዴሽኑን መመሥረት አስፈላጊ በመሆኑ ተግባራዊ መደረጉንም አቶ ኃይለ ማርያም አክለዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም የመክፈቻ ንግግራቸውን አድርገው ሲያበቁ፣ በዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል የተዘጋጀ የሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የሕይወት ዘመን ትውስታ ከሕፃንነት እስከ ግባተ መሬት ድረስ የነበረውን ዘጋቢ ፊልም ሲታይ በታዳሚዎች ላይ የተደበላለቀ ስሜት ሲፈጠር ተስተውሏል፡፡ በተለይ በዘጋቢ ፊልሙ የአቶ መለስ አስከሬን ከቤልጂየም ብራሰልስ በኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን አዲስ አበባ ቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርስና ቤተሰቦቻቸው ከአውሮፕላኑ ሲወርዱ፣ አስከሬኑ ከቦሌ ወደ መኖሪያ ቤታቸው ቤተ መንግሥት ሲጓዝ፣ የቀብራቸው ዕለት በመስቀል አደባባይ አስከሬናቸውን የያዘው ሳጥን ሲቀመጥና ከፍተኛ ዝናብ እየጣለ አስከሬኑ በሰረገላ ሆኖ ወደ ቅድሥት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ሲያመራ የሚያሳየውን ፊልም የተመለከቱ በአፍሪካ ኅብረት የታደሙ ሰዎች፣ ከንፈራቸውን ከመምጠጥ እስከ እንባ ማፍሰስ ድረስ በሐዘን ስሜት ውስጥ ገብተው ተስተውሏል፡፡ ሌላው አዳራሹን ለተወሰኑ ደቂቃዎች የሐዘን ድባብ ውስጥ የከተተ ክስተትም ተፈጥሮ ነበር፡፡ ዘጋቢ ፊልሙን ከሚመለከቱ ታዳሚዎች መካከል የነበሩት የአቶ መለስ እህቶች ድምፅ አውጥተው ለቅሶ በመጀመራቸው፣ ከሰባት ወራት በፊት የነበረውን የሐዘን ሁኔታ ያስታወሰና የሁሉንም ታዳሚዎች ቀልብ የሳበ ሆኖ ነበር፡፡

ታዳሚዎች ድንገት በተቀሰቀሰው የሐዘን ድባብ ውስጥ ባሉበት ሁኔታ፣ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር፣ የጂቡቲው ፕሬዚዳንት፣ የሱዳን ፕሬዚዳንት፣ የኡጋንዳ ፕሬዚዳንት፣ የሶማሊያ ጠቅላይ ሚኒስትር፣ የናይጄሪያ የቀድሞው ፕሬዚዳንት፣ ፕሮፌሰር አንድሪያስ እሸቴ፣ የምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዶ/ር ጌታቸው በትሩ፣ እ.ኤ.አ. ከ1992 እስከ 1998 በኢትዮጵያ የነበሩት የዓለም ባንክ ዳይሬክተርና ሌሎች የተለያዩ አገሮች ተወካዮች፣ ስለ አቶ መለስ የሰላም አባትነት፣ የልማት ጀግናነት፣ አስተዋይነት፣ ብልህነት፣ አርቆ አሳቢነትና ስለማይተካው የአፍሪካና ዓለም አቀፍ መሪነታቸው በየተራ ንግግር አድርገዋል፡፡ ረዘም ያለ ጊዜ ወስደው ስለ አቶ መለስ ንግግር ያደረጉት ዘግይተው ጉባዔውን የተቀላቀሉት የኡጋንዳው ፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ፣ ለፋውንዴሽኑ 300 ሺሕ ዶላር መለገሳቸውን አስታውቀዋል፡፡ እሳቸውን ተከትለው የጂቡቲው 500 ሺሕ ዶላር፣ የደቡብ ሱዳን አንድ ሚሊዮን ዶላር፣ የሱዳን ሁለት ሚሊዮን ዶላር ለግሰዋል፡፡ ፋውንዴሽኑ በድምሩ ከ50 ሚሊዮን ብር በላይ ማግኘቱም ታውቋል፡፡

የመለስ ዜናዊ ፋውንዴሽን አልፋና ኦሜጋ ዕውቀትን፣ ሕዝባዊ ታማኝነትንና ፅናትን፣ በሌሎች ሳይሆን በራስ አቅምና እጅ የተወለደ የዴሞክራሲና የልማት ሥርዓትን ተግባራዊ ከማድረግ ውጭ አለመሆን የተናገሩ የአቶ መለስ ባለቤት ወይዘሮ አዜብ መስፍን ሲሆኑ፣ የመለስ ፋውንዴሽን መገለጫ ግዑዝ ከሆነው ድንጋይና እምነበረድ ድርድር በላይ አስተሳሰቡና ራዕዩ ትውልድ ተሻጋሪ ኃያልነትን እንዲጎናጸፍ ማስቻል መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ፋውንዴሽኑ የመለስን ፅኑ እምነትን የሚያንፀባርቅ፣ ኢትዮጵያን ከድህነት በማውጣት ሁሉም የሚኮራበትና ኢትዮጵያን መልሶ ለመገንባት የሚያስችል ቋሚ ሐሳብና ፕሮግራም ማፍለቂያ ማዕከል እንደሚሆንም አክለዋል፡፡

ነፍስ ካላወቁ ሕፃናት በስተቀር መላው ኢትዮጵያውያን በአንድ እግር፣ በአንድ ግብ፣ በአንድ ዓይን ያለ እስከሚመስሉ ድረስ፣ በአንድ ላይ እምባቸውን ለመሪያቸው ፍቅር ያሳዩበትን ዕለት ተመልሰው እንዲያስታውሱ የጉባዔውን ታዳሚ የጠየቁት ወይዘሮ አዜብ፣ “የመለስ ሞት ከተነገረበት ዕለት አንስቶ እስከ ግባተ መሬቱ ድረስ የኢትዮጵያ ሕዝብ ያሳየው የማይነጥፍ ልዩ ድጋፍና ፍቅር ልቤን ነክቶታል፡፡ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ያለን ክብርና ምሥጋና ከቃላት በላይ ነው፡፡ ምንም ማለት አልችልም፡፡ ማለት የምችለው ምሥጋናችን ይድረሳችሁ ብቻ ነው፤” ብለዋል፡፡ ከሞትና ከተፈጥሮ የተሟገተ፣ የሕዝብ ቃላት አልበቃ ያሉት የሐዘን ቀን፣ ከመለስ ራዕይ የተጠቀሙም፣ ያልተጠቀሙም፣ ከጎጆ ቤት እስከ ቤተ መንግሥት፣ ከማጀት እስከ አደባባይ፣ የመንግሥት መሥሪያ ቤት ብቻ ሳይሆን የምሽት ጭፈራ ቤቶች ሳይቀሩ የሁሉንም ጓዳ ያንኳኳ የሐዘን ጊዜ እንደነበር ያስተወሱት ወይዘሮ አዜብ፣ ለሁሉም ምሥጋና አቅርበዋል፡፡

ለሙሉ ቀን የዋለው የመለስ ዜናዊ ፋውንዴሽን መሥራች ጉባዔ ከሰዓት በኋላ በነበረው ውሎው በአቶ አዲሱ ለገሰ የሌጋሲ ኮሚቴ ሪፖርትን በማቅረብ የተጀመረ ሲሆን፣ አቶ አዲሱ ባቀረቡት ባለ 19 ገጽ ሪፖርት በርካታ ሥራዎች መሠራታቸውን ጠቁመዋል፡፡ እንደ አቶ አዲሱ ማብራሪያ አቶ መለስ በድንገትና ባልታሰበ ሁኔታ በመሞታቸው፣ ቤተሰቦቻቸው ለ21 ዓመታት ይኖሩበት ከነበረው ቤተ መንግሥት፣ በፍጥነት ለመልቀቅ አለመቻላቸውን ተናግረዋል፡፡ ምክንያቱም ቤት ማፈላለጉ ጊዜ በመውሰዱ ነው፡፡ ሆኖም የተገኘው ቤት እንዲታደስ ተደርጎ በጊዜያዊነት እንዲገቡ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡ ለአቶ መለስ ቤተሰቦች ቋሚ መኖሪያ ቤት ለመገንባት ቦታ መገኘቱን፣ ሥራውን የሚመራ መመደቡንና ግንባታ ለመጀመር የቤቱን የመጨረሻ ዲዛይን እየተጠባበቁ መሆኑን አቶ አዲሱ ገልጸዋል፡፡ ሌላው አቶ አዲሱ በሪፖርቱ የገለጹት፣ የመለስ ዜናዊ ፋውንዴሽን የሚገነባበት ሥፍራ ሰፋ ያለና ብዙ ነዋሪዎችን በማያፈናቅል ሁኔታ ሆኖ አመቺ ቦታ መመረጡን ነው፡፡ በፈቃደኝነት ዲዛይን ያቀረቡና ሌሎች ዲዛይኖችም ቀርበው በመታየት ላይ መሆናቸውንና የትኛው እንደተመረጠ ገና አለመወሰኑን አስረድተዋል፡፡

በጉባዔው ማጠናቀቂያና የጉባዔው የመጨረሻ መርሐ ግብር የነበረው የፋውንዴሽኑን ቦርድ መሰየም ነበረ፡፡ በመሆኑም ከመከላከያ ሚኒስቴር ጄኔራል ሳሞራ የኑስ፣ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም፣ ከገንዘብና ኢኮኖሚ ሚኒስቴር አቶ ሱፍያን አህመድ፣ ከኢሕአዴግ አባል ድርጅት አቶ ቴዎድሮስ ሐጎስ፣ አቶ ሙክታር ከድር (በኋላ በወይዘሮ አስቴር ማሞ ተተክተዋል) አቶ ሽፈራው ሽጉጤ፣ አቶ ካሣ ተክለብርሃን፣ አቶ አብዱ አህመድ፣ አቶ አህመድ ናስርና አራት ሰዎች ደግሞ ከአቶ መለስ ቤተሰቦች በዕጩነት ቀርበዋል፡፡ የቀረቡት ዕጩዎች ሁሉም የፓርቲ አባላት ብቻ መሆናቸውን በመቃወም ከንግዱ፣ ከኪነ ጥበብና ከሌሎቹም የኅብረተሰቡ ክፍሎች መካተት እንዳለባቸው የተለያዩ አስተያየት ሰጪዎች ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ በተለይ የመከላከያ ውክልናን በሚመለከት “ለምን?” የሚል ጥያቄ ከመቅረቡም በተጨማሪ፣ ሁሉም የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች ውክልና ቀርቶ ሲቪል ማኅበረሰቡ እንዲካተት የአቶ መለስ ቤተሰቦች ጭምር ሐሳብ አቅርበው ነበር፡፡

የተነሱት አስተያየቶችና ጥያቄዎች ተገቢ ቢሆኑም ቦርዱ መቋቋም ያለበት በአዋጁ መሠረት በመሆኑና ከአዋጁ ውጪ ምንም ማድረግ ስለማይቻል፣ የሚሰየመው ቦርድ በቀጣይ አዋጁ የሚስተካከልበትንና የቦርድ አባላት በስፋት የሚካተቱበት ሁኔታ እንደሚኖር በመግለጽ የቀረበው ጥቆማ እንዲፀድቅ አቶ አዲሱ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ የጉባዔው ታዳሚዎች ያነሱትን ጥያቄና አስተያየት ተከትሎ፣ አቶ ካሣ ተክለብርሃን በራሳቸው ላይ ተቃውሞ በማቅረብ በእሳቸው ምትክ ሌላ ሰው እንዲተካ ቢጠይቁም ድጋፍ በማጣታቸው ተቀባይነት አላገኙም፡፡ በመሆኑም አቶ አዲሱ የሰጡትን አስተያየት አቶ በረከት ስምኦንና ወይዘሮ አዜብ በመደገፋቸው የቀረበው አስተያየት ተቀባይነት አላገኘም፡፡ በመጨረሻም ወይዘሮ አዜብ መስፍን የፋውንዴሽኑ ፕሬዚዳንት ሲሆኑ፣ አቶ ካሣ ተክለብርሃን ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነዋል፡፡ 
http://www.ethiopianreporter.com/index.php/news/item/1409-%E1%8B%A8%E1%88%98%E1%88%88%E1%88%B5-%E1%8B%9C%E1%8A%93%E1%8B%8A-%E1%8D%8B%E1%8B%8D%E1%8A%95%E1%8B%B4%E1%88%BD%E1%8A%95-%E1%88%98%E1%88%A5%E1%88%AB%E1%89%BD-%E1%8C%89%E1%89%A3%E1%8B%94-%E1%89%A0%E1%89%B0%E1%8B%B0%E1%89%A0%E1%88%8B%E1%88%88%E1%89%80-%E1%88%B5%E1%88%9C%E1%89%B5-%E1%89%B0%E1%8A%AB%E1%88%84%E1%8B%B0

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር