ተቃዋሚዎች የአየር ሰአት ድልድሉ ፍትሃዊ አይደለም አሉ


የአካባቢና ማሟያ ምርጫ ተወዳዳሪ ፓርቲዎች ራሳቸውን ለመራጩ ህዝብ እንዲያስተዋውቁ በሚል በምርጫ ቦርድ እና በኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን የተደለደለው የቴሌቪዥንና የሚዲያ የአየር ሰአት ፍትሃዊ አለመሆኑን ፓርቲዎች ገለፁ፡፡ የኢትዮጵያ ራዕይ ፓርቲ (ኢራፓ)፣ የኢትዮጵያ ፌዴራሊስት ዴሞክራሲያዊ ሃይሎች ግንባር (ኢፌዲሃግ) እና የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) አመራሮች እንደሚሉት፤ ለኢህአዴግ የተሰጠው የቴሌቪዥን የአየር ሰአት በአጠቃላይ 210 ደቂቃ ሲሆን ለእያንዳንዱ ተቃዋሚ ፓርቲ በኢቲቪ 1 እና ኢቲቪ 2 በእያንዳንዳቸው 10 ደቂቃ ብቻ የተሰጠ ሲሆን ይሄም ገዥው ፓርቲ በተቆጣጠረው ሚዲያ ሰፊ የአየር ሽፋን ማግኘቱን እንደሚያመለክት ገልፀዋል፡፡
የአየር ሰአት ድልድሉ በተለይ ፓርቲዎቹ የሚያቀርቧቸው እጩዎች ብዛት እና በ2002 ዓ.ም በተደረገው ምርጫ ፓርቲዎቹ ባገኙት የፓርላማ ወንበር መሆኑ የድልድሉን ፍትሃዊ አለመሆን ያጐላዋል ያሉት አመራሮቹ፤ እነዚህን መስፈርቶች ብቻ መመዘኛ ከማድረግ ይልቅ ሌሎች የዲሞክራሲ ሂደቱን ሊደግፉ የሚያስችሉ አማራጭ መስፈርቶችም ሊካተቱበት ይገባ ነበር ብለዋል፡፡ ፓርቲያቸው የአየር ሰአት ድልድሉ ፍትሃዊ ነው ብሎ ባያምንም ላለመግባባት መግባባት የሚለውን መርህ በማንገብ አብሮ በሰላምና በመግባባት መስራት የፓርቲያቸው ተቀዳሚ አላማ በመሆኑ እንደተቀበሉት የተናገሩት የኢራፓ ሊ/መንበር አቶ ተሻለ ሰብሮ፤ ለእያንዳንዱ ፓርቲ 10 ደቂቃ ብቻ በቴሌቪዥን መሰጠቱ፣ በተቃራኒው ለኢህአዴግ 210 ደቂቃ መመደቡና የ2002 ምርጫ ውጤትንና የእጩ ብዛትን እንደመስፈርት መውሰዱ የአየር ሰዓት ድልድሉ ፍትሃዊ አለመሆኑን ይጠቁማል ብለዋል፡፡
ኢዴፓ ሊቀመንበር አቶ ሙሼ ሰሙ በበኩላቸው፤ ለድልድሉ የቀረበው ደቂቃ ለፓርቲያቸው ምንም ጥቅም እንደሌለው፣ የፓርቲውን ፖሊሲ፣ ፕሮግራም እና ስለፓርቲው ለማስተዋወቅ እንኳ በቂ እንዳልሆነ አስታውቀው፣ ድልድሉ ዘግይቶ መካሄዱም ማህበረሰቡን በበቂ ሁኔታ ተደራሽ ለማድረግ ስለማያስችል ፓርቲያቸው እንደማይቀበለው ገልፀዋል፡፡ የኢፍዴሃግ ዋና ፀሐፊ አቶ ገረሱ ገሣ፤ ድልድሉ ምን ያህል ፍትሃዊ ነው የሚለውን ከስራ ባልደረቦቻቸው ጋር እየመከሩበት መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ኢህአዴግ ለፓርቲዎቹ ለመስጠት ቃል የገባውን 2 ሚሊየን ብር በተመለከተ ኢራፓ እና ኢፍዲሃግ ገንዘቡ እስካሁን በእጃቸው ባይገባም ለምርጫው አጋዥ ሊሆናቸው እንደሚችል አመራሮቹ ተናግረዋል፡፡ “ገንዘቡን ማንም ይስጥ፤ ይህ ገንዘብ የዜጐቻችን አንጡራ ሃብት ነው፡፡
ኢህአዴግ ይህን ገንዘብ ስለሰጠ ፖሊሲያችንና አቅጣጫችንን ጠምዝዞ አያስለውጠንም” የሚሉት አቶ ተሻለ፤ ሌላ የገቢ ምንጭ ስለሌለን በገንዘቡ እንጠቀምበታለን ብለዋል፡፡ የኢዴፓ ሊቀመንበር አቶ ሙሼ ሰሙ በበኩላቸው፤ አስቀድሞ ገንዘቡ ሊሰጥ ይገባል የሚለውን ሃሳብ የፓርቲዎቹ የጋራ ምክር ቤት ለምርጫ ቦርድ እንዳቀረበ፤ ነገር ግን ኢህአዴግ በመግለጫው “በምርጫው ለሚሳተፉ” ፓርቲዎች የሚለውን መስፈርት ብቻ ተገን አድርጐ ገንዘቡን ለመስጠት መወሰኑን ፓርቲው እንደማይቀበለው፤ ነገር ግን የገንዘቡን መሰጠት እንደማይቃወሙ አስታውቀዋል፡፡ “እኛ ያነሳነው የመርህ ጉዳይ ነው” ያሉት አቶ ሙሼ፤ ኢህአዴግ “በምርጫው ለሚሳተፉ” ብቻ ገንዘቡን እንደሚሰጥ መግለፁ ለወደፊትም ለምርጫ እጩ ካላቀረባችሁ ድጋፍ አላደርግም የሚለውን መልዕክት እንደሚያስተላልፍ፣ ይህ ደግሞ በሃገሪቱ የምርጫ ዲሞክራሲያዊ ሂደት ላይ ተጽእኖ እንደሚኖረው ተናግረዋል፡፡

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር