የጠቅላይ ሚኒስትሩ አዲሱ የካቢኔ አደረጃጀት እያነጋገረ ነው



-    ካቢኔው በሕገ መንግሥቱ መሠረት አንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ይኖረዋል
-    የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ ያላቸው ሁለት ባለሥልጣናት ተሹመዋል
-    አዲሱ አደረጃጀት ከሌሎች ሕጐች ጋር ተቃርኖ አለው እየተባለ ነው

በዮሐንስ አንበርብር
የሥራ አስፈጻሚውን ከፍተኛ ሥልጣን በማግኘት አገሪቱን መምራት ከጀመሩ ሁለት ወራት ከቀናት ያስቆጠሩት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ሰሞኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በመቅረብ ካቢኔያቸውን በአዲስ መልክ እንዳደራጁ አስታውቀዋል፡፡ በዚህም መሠረት የሁለት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮችንና የሌሎች ሚኒስትሮችን ሹመት አፀድቀዋል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩ አዲሱ የካቢኔ አደረጃጀትም መነጋገሪያ ሆኗል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመሩት የሚኒስትሮች ምክር ቤት (ካቢኔ) በሕገ መንግሥቱና በመመሥረቻ አዋጁ የተጣለበትን ኃላፊነቶች በብቃት ለመወጣትና የአስፈጻሚነት ሚናውን በአግባቡ እንዲወጣ ለማድረግ፣ እንደ አዲስ በሦስት ዘርፎች መዋቀሩ አስፈላጊ መሆኑን ለፓርላማው አስታውቀዋል፡፡

በዚህም መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የዲፕሎማሲ፣ የደኅንነት፣ የመከላከያ እንዲሁም ከፍተኛና ግዙፍ (ሜጋ) ፕሮጀክቶችን በቀጥታ እንዲከታተሉ ተደርጓል፡፡ ከዚህ ውጪ ያሉ አስፈጻሚው የሚከታተላቸውን ተግባራት በብቃት ለመምራት የሚኒስትሮች ምክር ቤት በሦስት ዘርፎች እንዲዋቀር መደረጉን ገልጸዋል፡፡ ማኅበራዊ ጉዳዮችን፣ መልካም አስተዳደርና ረፎርምን፣ ፋይናንስና ኢኮኖሚን የሚመለከቱ ሦስት የሥራ ዘርፎች በአዲሱ የካቢኔ መዋቅር የተፈጠሩ ሲሆን፣ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የትምህርት ሚኒስትሩ ደመቀ መኮንን የማኅበራዊ ዘርፉን የሚመሩ መሆኑ ታውቋል፡፡

ከዚህ ቀደም የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤትና የካቢኔ ጉዳዮች ቢሮን በሚኒስትር ማዕረግ ሲመሩ የነበሩት አቶ ሙክታር ከድር በአዲሱ የካቢኔ መዋቅር መሠረት በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የመልካም አስተዳደርና ሪፎርም ዘርፍን እንዲያስተባብሩና እንዲከታተሉ ተሹመዋል፡፡ በሽብር ተግባር ከተከሰሱት ባለቤታቸው ጉዳይ ጋር በተያያዘ ከኦሕዴድ ሥራ አስፈጻሚ አባልነታቸው የተወገዱት አቶ ጁነዲን ሳዶ የሚመሩትን የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስቴርን በሚኒስትርነት እንዲመሩም ተሹመዋል፡፡

በቅርቡ የሕወሓት ምክትል ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡት ዶ/ር ደብረፅዮን ገብረ ሚካኤል ከመገናኛና ኢንፎርሜሽን ሚኒስትርነታቸው በተጨማሪ፣ የካቢኔውን የፋይናንስና ኢኮኖሚ ዘርፍ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ እንዲከታተሉና እንዲያስተባብሩ ተሹመዋል፡፡

ያልተጠበቁ ሹመቶች
የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን ሕልፈት ተከትሎ የሥራ አስፈጻሚውን ሥልጣን ማን ይይዛል በሚል በርካታ አስተያየቶች ሲሰነዘሩ መቆየታቸው ይታወሳል፡፡ በኢሕአዴግ መተካካት ፖሊሲ መሠረት የፓርቲው ምክትል ሊቀመንበር የነበሩት አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ሥልጣን እንደሚይዙ በመንግሥት በኩል ቢገለጽም፣ ተግባራዊነቱ በመዘግየቱ ለጥርጣሬዎችና ለተለያዩ መላምቶች ክፍት እንደነበር ይታወሳል፡፡

አቶ ኃይለ ማርያም በጠቅላይ ሚኒስትርነት ከተሾሙ በኋላ ቀደም ሲል ይመሩት የነበረው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ላለፉት ሁለት ወራት በተጠባባቂ ሚኒስትሩ መመራቱ ለተመሳሳይ መላምቶች ሰለባ ሆኗል፡፡ ይሁን እንጂ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታው አምባሳደር ብርሃነ ገብረ ክርስቶስ ተጠባባቂ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው እንዲሠሩ መደረጉ፣ በቀጣይነት የሙሉ ሚኒስትርነት ሹመት ይሰጣቸዋል የሚለውን ግምት አጠናክሯል፡፡ በተለይም አምባሳደር ብርሃነ ገብረ ክርስቶስ በውጭ ግንኙነትና ዲፕሎማሲ የረጅም ዓመታት ልምድ ማካበታቸው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሥልጣንን በርካቶችን ከእሳቸው ውጭ ማንም አይወስድም የሚል ግምት እንዲኖራቸው አድርጓል፡፡

ይሁን እንጂ ሰሞኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም የጤና ጥበቃ ሚኒስትሩን ዶክተር ቴዎድሮስ አድሀኖንም በውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት በማሾም በርካቶችን አስገርመዋል፡፡

ዶ/ር ቴዎድሮስ በጤናው ዘርፍ ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ አድናቆት የተቸራቸው ናቸው፡፡ በጤናው ዘርፍ ከሚፈለገው የውጭ ግንኙነት አንፃርም በቂ የሆነ ተደማጨነትን አግኝተዋል፡፡ የወባ በሽታን ለማጥፋት በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚደረገውን ርብርብ የሚመሩት ዶ/ር ቴዎድሮስ መሆናቸው የዚህ አንድ ማሳያ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ኢትዮጵያ ከምትገኝበት የአፍሪካ ቀንድ የሰላምና የፀጥታ አስቸጋሪነት፣ እንዲሁም በዚህ ዘርፍ ምንም ዓይነት ልምድ የሌላቸው ከመሆኑ አንፃር ሲገመገም፣ አሁን የተሾሙበት የሥራ ኃላፊነት አስቸጋሪ ሊሆንባቸው ይችላል የሚሉ አስተያየቶች እየተደመጡ ነው፡፡ በተቃራኒው ደግሞ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በበለጠ ሁኔታ ተጠናክሯል የሚሉ አስተያየት ሰጪዎችም ይገኛሉ፡፡ ለዚህ ምክንያታቸው አምባሳደር ብርሃነ ገብረ ክርስቶስ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሥልጣናቸው ላይ እንዲቆዩ መደረጉ ዶ/ር ቴዎድሮስ በጤናው ዘርፍ የውጭ ግንኙነት መስክ ካተረፉት ተደማጭነት ጋር ተዳምሮ ትልቅ ጉልበት ሊሆን እንደሚችል ነው፡፡

የአቶ ሙክታር ከድር በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርነት ማዕረግ ለመልካም አስተዳደርና ሪፎርም፣ እንዲሁም አቶ ጁነዲንን ተክተው ለሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትርነት ተሹመዋል፡፡ በወቅቱ ብቸኛው የተቃዋሚ ፓርቲ የፓርላማ አባል አቶ ግርማ ሰይፉ አቶ ጁነዲን በተነሱበት ምክንያት ላይ ማብራሪያ የጠየቁ ቢሆንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግን ምላሽ ሳይሰጡ ዘለውታል፡፡ 

የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል በጉዳዩ ላይ ተጠይቀው፣ ኦሕዴድ አቶ ጁነዲንን ከሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባልነታቸው በማውረድ ተራ አባል እንዲሆኑ በማድረጉና ከባለቤታቸው ጋር በተያያዘ ለመገናኛ ብዙኅን በሰጡት አስተያየትም በመተቸታቸው፣ ይህንኑ ያገናዘበ ዕርምጃም በኢሕአዴግና በመንግሥት በኩል ሊወሰድ እንደቻለ ተናግረዋል፡፡

የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ዴኤታ በመሆን ሲያገለግሉ የነበሩት ዶ/ር ከሰተብርሃን አድማሱ የዶ/ር ቴዎድሮስን መዛወር ተከትሎ በጤና ጥበቃ ሚኒስትርነት የተሾሙ ሲሆን፣ ላለፈው አንድ ዓመት ያህል በንግድ ሚኒስትርነት ሲሠሩ የነበሩት አቶ ከበደ ጫኔ በዚሁ ሥልጣን ላይ እንዲቀጥሉ ተደርጓል፡፡

አቶ ከበደ ጫኔ በሚኒስትርነት እየሠሩ የነበረ ቢሆንም፣ የሚኒስትርነታቸውን ሥልጣን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያላፀደቀው በመሆኑ ይህንኑ ለማሟላት ብቻ ሹመታቸው ወደ ፓርላማው ሊቀርብ ችሏል፡፡

የሕግ ጉዳይ
በአዲሱ የካቢኔ አወቃቀር መሠረት ሦስት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች እንዲኖሩ መደረጉ ከሕገ መንግሥቱ ጋር ይጋጫል የሚሉ የተቃውሞ አስተያየቶች እየተሰሙ ነው፡፡ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ግን ሕገ መንግሥቱ ስለ ብዛት አያወሳም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ያሾማል ነው የሚለው በማለት አስተያየቱን ውድቅ አድርገውታል፡፡ ሌሎች አስተያየት ሰጪዎች ግን አሁንም የአገሪቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን ናቸው ይላሉ፡፡ ለዚህ የሚሰጡት ምክንያት ራሳቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሌሎቹን ተሿሚዎች ያቀረቡት በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርነት ማዕረግ ነው በሚል ነው፡፡

‹‹..ይህ ውሳኔ በሕገ መንግሥቱ መሠረት ከዚህ ቀደም ለምክር ቤቱ አቅርቤ ካፀደኩት የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ሹመት በተጨማሪ ሁለት የኢሕአዴግ ከፍተኛ ባለሥልጣናትን በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርነት ማዕረግ መሾም አስፈልጓል፤›› በማለት ነበር ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ለፓርላማው ያስረዱት፡፡

ይሁን እንጂ አሁንም ሹመቱ ከተለያዩ የአገሪቱ ሕጐች ጋር ተቃርኖ እንዳለው ሌሎች አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ፡፡ ለአብነትም የብሔራዊ ባንክና የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ተቋማትን ማቋቋሚያ አዋጅ ይጠቅሳሉ፡፡

ነሐሴ 5 ቀን 2000 ዓ.ም. የተሻሻለው የብሔራዊ ባንክ ማቋቋሚያ አዋጅ ክፍል ሁለት አንቀጽ 3(4) የብሔራዊ ባንክ ተጠሪነት ለኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ጠቅላይ ሚኒስትር ይሆናል በማለት ያስረዳል፡፡ በመሆኑም በአዲሱ የካቢኔ መወቅር መሠረት የፋይናንስና የኢኮኖሚ ጉዳዮችን እንዲከታተሉ ዶ/ር ደብረፅዮን በመሾማቸው፣ ከተጠቀሰው አንቀጽ ጋር የሚቃረንና ብሔራዊ ባንክም ከተቋቋመበት አዋጅ ውጭ ለዶ/ር ደብረፅዮን ሪፖርት እንዲያደርግ ያስገደድዋል ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

በተመሳሳይ የፀረ ሙስናና ሥነ ምግባር ኮሚሽንም በመቋቋሚያ አዋጁ መሠረት ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሆንም፣ በአሁኑ መዋቅር መሠረት ግን ለአቶ ሙክታር ከድር ሪፖርት እንዲያደርግ ይገደዳል ብለዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ከፍተኛና ግዙፍ (ሜጋ) ፕሮጀክቶችን ራሳቸው ለመከታተል በአዲሱ መዋቅር ኃላፊነት የወሰዱ ቢሆንም፣ እነዚህ ፕሮጀክቶች ከፋይናንስና ከኢኮኖሚ ጉዳዮች ጋር በቀጥታ የሚገናኙ በመሆኑ ፕሮጀክቶቹን ነጥሎ መከታተል አዳጋች እንደሚሆን ያስረዳሉ፡፡ 

ከዚህ በተጨማሪም የአሁኑን ሹመትና ምደባ በሌላ መንገድ የሚመለከቱ ወገኖች አሉ፡፡ እነሱ እንደሚሉት፣ የኢሕአዴግ አራቱ አባል ድርጅቶች በአዲሱ አመራር ሥልጣኖችን ተከፋፍለዋል፡፡ ደኢሕዴን የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ቦታ ሲይዝ፣ የተቀሩት ማለትም ሕወሓት፣ ኦሕዴድና ብአዴን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርነትን ተከፋፍለዋል ይላሉ፡፡ በዚህ መደባ መሠረት ደግሞ ሕወሓት የፋይናንስና የኢኮኖሚ ዘርፍን፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርን፣ የኢንፎርሜሽንና ኮሙዩኒኬሽን ሚኒስቴርን በመያዙ ከሌሎቹ በተሻለ ሁኔታ ሥልጣን ማግኘቱን ይተቻሉ፡፡ 
 http://ethiopianreporter.com/news/293-news/8738-2012-12-01-11-22-47.html

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር