ፓርላማው መደበኛ ስብሰባዎቹን እያካሄደ አይደለም


-    ከ18 መደበኛ ስብሰባዎች ስድስቱን ብቻ ተሰብስቧል
በዮሐንስ አንበርብር

በመስከረም ወር የመጨረሻ ሳምንት የሦስተኛ ዓመት የሥራ ዘመኑን የጀመረው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት (ፓርላማ) በሳምንት ሁለት ጊዜ ማክሰኞና ሐሙስ ማካሄድ የሚገባውን መደበኛ ስብሰባዎች በአብዛኛው አላካሄደም፡፡ በምክር ቤቱ የአሠራር ሥነ ሥርዓት ደንብ መሠረት የምክር ቤቱ መደበኛ ስብሰባዎች በሳምንት ሁለት ጊዜ መካሄድ ይገባቸዋል፡፡ በዚህም መሠረት ምክር ቤቱ ሥራውን ከጀመረበት የመስከረም ወር መጨረሻ አንስቶ እስከ ታህሳስ ወር የመጀመሪያ ሳምንት ድረስ 18 መደበኛ ስብሰባዎች መካሄድ ነበረባቸው፡፡ ይሁን እንጂ እስካሁን ያደረገው ስድስት መደበኛ ስብሰባዎችን ብቻ ሲሆን፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በምክር ቤቱ ከሁለት ሳምንት በፊት ተገኝተው ያፀደቁት አዲስ የካቢኔ አወቃቀርና የሚኒስትሮች ሹመት የመጨረሻው ወይም ስድስተኛው መደበኛ ስብሰባው ነበር፡፡

ኅዳር 20 ቀን 2005 ዓ.ም. ከተካሄደው ከዚህ መደበኛ ስብሰባ በኋላ እንኳን አራት የመደበኛ ስብሰባ ቀናት ቢኖሩትም፣ “ዛሬ ይካሄድ የነበረው መደበኛ ስብሰባ የማይካሄድ መሆኑን ከይቅርታ ጋር እንገልጻለን” የሚሉ ማስታወቂያዎችን የምክር ቤቱ አባላት መኖሪያዎች አካባቢ በሚገኙ የማስታወቂያ ሰሌዳዎች፣ እንዲሁም በምክር ቤቱ ሰሌዳዎች ላይ በመለጠፍ የመደበኛ ስብሰባ ፕሮግራሞቹን መዝለል የተለመደ እየሆነ መጥቷል፡፡

የምክር ቤቱ ዋና ሥልጣንና ተግባሮች የሚቀርቡለትን ረቂቅ አዋጆች ተወያይቶ ማፅደቅና አስፈጻሚውን ወይም ራሱ የሚያመነጫቸውን የመንግሥት አካላት መቆጣጠር ናቸው፡፡

እስካሁን ካካሄዳቸው ስድስት መደበኛ ስብሰባዎች መካከል የመጀመሪያው ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደጊዮርጊስ የዚህን ምክር ቤትና የፌዴሬሽን ምክር ቤት የሥራ ዘመን መጀመርን አስመልክተው መንግሥት በዓመቱ ትኩረት ሊያደርግባቸው ይገባል በሚል ያቀረቡት ንግግር ሲሆን፣ ሁለተኛው ስብሰባ በዚሁ የፕሬዚዳንቱ የመክፈቻ ንግግር ላይ የተነሱ ጥያቄዎችን ተንተርሶ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም የመንግሥታቸውን አቋም ያብራሩበት ነው፡፡

ቀሪዎቹ ሌሎች ስብሰባዎች ተደራራቢ ግብርን ለማስቀረትና ለመንገድ ግንባታ በተገኘ ብድር ዙሪያ የተደረጉ ስምምነቶች ናቸው፡፡ ምክር ቤቱ በአስፈጻሚው የመንግሥት አካል አመንጭነት ከሚቀርቡለት አዋጆች ውጭ በራሱ ሕግ የማመንጨት ሥልጣን ቢኖረውም፣ ላለፉት ዓመታት ያለው ታሪክ በጣት የሚቆጠሩ ሕጎች በፓርላማው መመንጨታቸውን ነው፡፡ ለአብነት ያህልም በሦስተኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመጨረሻ የሥራ ዘመን አካባቢ የፀደቀው የሰንደቅ ዓላማ አዋጅ ተጠቃሽ ነው፡፡

ካለፉት ልምዶች መረዳት የሚቻለው በአስፈጻሚው አካል የሚቀርቡ አዋጆች ከሌሉ የፓርላማው መደበኛ የስብሰባ ጊዜያት ጥያቄ ውስጥ መሆናቸውን ነው፡፡ ይሁን እንጂ ምክር ቤቱ በማናቸውም ጉዳዮች ላይ ጥያቄ ካለው ጠቅላይ ሚኒስትሩን በወር አንድ ጊዜ ጠርቶ የመጠየቅ ሥልጣን ሲኖረው፣ በተመሳሳይ መንገድ የተለያዩ የዘርፉ ሚኒስትሮችን በሳምንት አንድ ጊዜ በመጥራት ስለ ሥራ አፈጻጸም ክዋኔያቸውና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች መጠየቅ ይችላል፡፡

ነገር ግን ባለፉት ወራት ምክር ቤቱ አንዳቸውንም ሳያደርግ መደበኛ ስብሰባዎቹን እያስተላለፈ የግማሽ ዓመቱን የአንድ ወር ዕረፍት በየካቲት ወር ለመውሰድ አንድ ወር ከቀናት ዕድሜ ቀርቶታል፡፡

የምክር ቤቱ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ በጉዳዩ ላይ ተጠይቀው ለምክር ቤቱ የቀረቡት ረቂቅ አዋጆች ጥቂት መሆናቸውን፣ በዚህም ምክንያት መደበኛ ስብሰባዎች እንዳልተካሄዱ፣ ነገር ግን የምክር ቤቱ ቋሚ ኮሚቴዎች በየዘርፋቸው የሚገኙ ተጠሪ አስፈጻሚ መሥሪያ ቤቶችን በመቆጣጠር ሥራ መጠመዳቸውን ገልጸዋል፡፡

ረቂቅ አዋጆችን ከመመልከት በተጨማሪ የተመረጡ አስፈጻሚ መሥሪያ ቤቶችን የሥራ አፈጻጸም ሪፖርቶች በመደበኛ ጉባዔው የማዳመጥ ኃላፊነት ያለበት ሲሆን፣ ከጥር ወር በኋላም እነዚህ መሥሪያ ቤቶች የግማሽ ዓመት ሪፖርታቸውን እንደሚያቀርቡ ገልጸዋል፡፡

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር