በሀይማኖት ተቋማት እና በግለሰብ እጅ ያሉ ጥንታዊ ፅሁፉችን የማሰባሰብና የማጥናት ስራ እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ
የተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት የኢትዮጵያን 12 ጥንታዊያን መጽሀፍትና የነገስታት ደብዳቤዎችን በዓለም የስነ ፁሑፍ ቅርስነት መዝግቦታል፡፡
አሁንም ኢትዮጵያን ጨምሮ ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በአለም እውቅና ያላገኙትን የስነ ጽሁፍ ቅርሶች ለማስመዝገብና መስፈርቶቹን ለማወቅ የሚያስችላቸው ስልጠና በአዲስ አበባ እየተሰጠ ነው፡፡
ቅርሶቹ በአለም ቅርስነት ለመመዝገብ ዋነኛው መስፈርት አለም አቀፍ ይዘት ያላቸው ሊሆኑ ይገባል፡፡ በዩኔስኮ የአለም የስነ ጽሁፍ ቅርስ ፕሮግራም ማናጀር ጆይ ስፐሪንግ የአፍሪካ መገለጫ የሆኑ ቅርሶች ተጠብቀው ሊቆዩ ይገባል ይላሉ፡፡
ኢትዮጵያ ውያን የራሳቸው የሆኑ ፊደል፣ ቁጥር እና የአጻጻፍ ስሌት ካላቸው ጥቂት የአፍሪካ ሀገራት መካከል አንዷ ናት፡፡ የተለያዩ የስነ ጽሁፍ ቅርሶችም ባለቤት ነች፡፡
ቅርሶች የአፍሪካ ትውስታ፣ ታሪክ፣ ባህልና ማንነት መገለጫ ናቸው፡፡ አፍሪካን አፍሪካ የሚያደርጓት ባለፉት ትውልዶች የተቀመጡ ታሪካዊ ዳራዎችና ቅርሶችን ለመጪው ትውልድ ማስተላለፍ ስትችል ነው፡፡ ይህን ማድረግ የሚቻለው ደግሞ ቅርሶቹን በሚገባ ጠብቆ ማቆየት ሲቻል ነው፡፡
የኢትዮጵያ ቤተመዛግብትና ቤተ መጽሀፍት ዋና ዳይሬክተር አቶ አብርሃም ሞቶሽ በሀይማኖት ተቋማት እና በግለሰብ እጅ ያሉ ጥንታዊ ጽሁፉችን የማሰባሰብና የማጥናት ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡
በጊዜ ብዛት ይዞታቸውን ለመልቀቅ የተቃረቡትን ደግሞ በዘመናዊ የመረጃ አያያዝ ስርዓት እየተቀየሩ መሆኑን ይገልጻሉ፡፡
ለ3 ቀናት የሚቆየውን ስልጠና በዩኔስኮ የደቡብ ኮሪያ ብሄራዊ ኮሚሽን እና የኮሪያ ባህላዊ ቅርሶች አስተዳደር ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ቤተመዛግብትና ቤተ መጻህፍት ኤጀንሲ ጋር በትብብር አዘጋጅተውታል፡፡
http://www.ertagov.com/amerta/component/content/article/48-erta-tv-today-top-news-addis-ababa-ethiopia/2587-2012-12-10-17-28-57.html
Comments
Post a Comment