ከመፈክር ይልቅ ዲሞክራሲ!

ሰላም! ሰላም! ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ላላችሁ በሙሉ። አንድ ወዳጄ ይኼንን የአቅጣጫ ሰላምታ እንደማይወደው አጫውቻችሁ አውቃለሁ? ለምንድን ነው ስለው ‹‹የሰው ልጅ እንደ ንፋስ በአቅጣጫ ላይ ተመሥርቶ ሰላምታ ሲለዋወጥ እበሽቃለሁ፤›› አይለኝ መሰላችሁ? የዘንድሮን ሰው የሚያበሽቀውን ነገር ብዛት ቆጥረን መጨረስ አቃተን! ግን ግን ንፋስን ለምንከተል የዘመኑ ሰዎች ይህ ሰላምታ ካልተሰጠ ለማን ይሰጥ? ለራስ ብቻ የሚሮጥበት ዘመን መሆኑን ካየን ዘንዳ ከዚህ ሌላ ምን ይባላል? አንዳችን ያለ ሌላችን መኖር እንደማንችል እያወቅነው ‘እኔ’ን ብቻ ላማከለ ነፍስ መሮጣችን ይገርመኛል። የሚገርማችሁ ደግሞ አባባልን እንኳ መርጠን አለመጠቀማችን ነው። ለምሳሌ ‹‹ዘመኑ የውድድር ነው›› የሚለውን አባባል ለተቀደሰ ይሁን ለረከሰ ተግባር እንደምንጠቀምበት ሳንለይ ለሁለቱም እንዳሻን እንገለገልበታለን። አሁንማ ሙሰኛውም በሰሞነኛ ተቆጣጣሪዎች ሲያላግጥ ‘ዘመኑ የውድድር ነው’ ማለት ጀምሯል አሉ። ‹‹ውድድሩ ጤናማ ዕድገት ለማስመዝገብ ነው? ወይስ እንደተለመደው ጠልፎ ለመጣል ነው?›› ይሉኝ ነበር ባሻዬ ይኼን ጉድ ቢሰሙ፡፡

ሌባ ቀጪ አጥቶ ለሕዝብ አገልግሎት በሚውል ገንዘብ ደልቦ ሲንጎማለል ይውላል። ተጠቂው ሰፊው ሕዝብ አቧራ ለብሶ ለዕለት ጉርሱ ይማስናል። ፍትሕ የናፈቃት ዓለም። በየጥጋጥጉ ዲስኩር ብቻ ተለጥፎ ይነበባል! ይነበነባል! የባሻዬ ልጅ፣ ‹‹አሁንማ የሰለቸኝ መፈክር ማንበብ ነው፤›› አለኝ፡፡ ‹‹ለምን?›› ብለው፣ ‹‹በመፈክር ውስጥ የተሸጎጡ በርካታ ውሸቶች አሉ፤›› ሲለኝ የገዛ ሳቄ ጆሮዬን አደነቆረው፡፡

ባለፈው ሰሞን አንድ የመንደራችን ጎበዝ ተማሪ ‹‹እኔ ከእንግዲህ ወዲያ ትምህርት የሚባል በቃኝ አቅለሸለሸኝ፤›› ብሎ አቆመው ተብሎ ሲወጣ ሲገባ የሠፈሩ መጠቋቆሚያ መሆኑን ሰማሁ። አንድ ቀን ከባሻዬ ልጅ ጋር ሆነን ልጁ ከሩቅ ሲመጣ አየነውና ጨዋታ ጀመርን። ‹‹ይኼ ልጅ በቃ ትምህርቱን ተወው?›› አልኩት የባሻዬን ልጅ። ሽምግልና የተላከው እሱ ስለሆነ ሚስጥሩን ማወቁ አይቀርም በሚል። በነገራችን ላይ ምሁሩ የባሻዬ ልጅ ይኼን ለመሰለው ነገር የሠፈሩ ቀንደኛ ተመራጭ መካሪና አግባቢ ነው። አሳክቶ መናገሩን ይችልበታል። አሳክቶ መናገሩን እየቻሉበት ስንቱን ከገደል አፋፍ መመለስ የሚችሉ እያሉ በዝምታቸው ምክንያት ስንት ትውልድ ጠፋ ይሆን? ‹‹አይ አንቺ አገር! ይብላኝልሽ ወልደሽ የወላድ መካን እንደሆንሽ ሁሉ ልጆችሽ እያሳመሙሽ ስትኖሪ። ስንቱ በላዩ ላይ በሩን ዘግቶ ተኝቷል መሰለህ አንበርብር? የጋን መብራቱን አትቁጠረው፤›› ይሉኝ ነበር ባሻዬ። ባሻዬ ኢትዮጵያ በምሁር ልጆችዋና በተፈጥሮ ሀብት ክምችቷ ምንም አልተጠቀመችም ከማለት ቦዝነው አያውቁም። እውነታቸውን አይደል ታዲያ? አውቃለሁ ባይ እንጂ እስቲ እንሰማማ የሚል የለም። ቆርጦ ቀጥል ተሰብስቦ ዕውቀት አሳፋሪ መስሏል። በአስተሳሰብ ድህነት ስንጠወልግ ግድ የሚለው መጥፋት ነበረበት? ኧረ ወዴት ነው እየተጨካከንን የምንጓዘው? አንድ የማውቀው ሰው፣ ‹‹አንበርብር ነዳጅ ላይ ተቀምጠን የምንራበው እኮ አገሪቱ ላቧን ጠብ አድረጋ ያስተማረችው ስለተኛ ነው፤›› ያለኝን አልረሳውም፡፡

እናም የባሻዬ ልጅ እንዲህ አለኝ። ‹‹የትምህርት ቤት ዲስኩር ሰልችቶኛል። ተግባር ላይ የማይውል ቢቀር ምን ይጎዳል? ህሊናዬን እየኮሰኮሰኝ ለአገር ዕድገት የማይጠቅም ትምህርት ከምማር ድንጋይ መፍለጥ ይሻለኛል ብሎ አመፀ፤›› ሲለኝ ገረመኝ። ጎበዝ! እንዲህ ያሉ ጠያቂ ታዳጊዎችን እንዴት እያስተናገድናቸው ይሆን? ነገሮችን አብራርተን በማስረዳት ወይስ ‘ለራስህ ስትል ተማር’ እያልን? የባሻዬ ልጅ እንደሚያጫውተኝ ከሆነ ይኼን መሰል ጥያቄ የሚያነሱ ንቃተ ህሊናቸው ከፍ ያለ ተማሪዎች በአግባቡ ከተያዙ ዛሬ አለ የሚሉትን ችግር ነገ አድገው መቀየራቸው እንደማይቀር ነው። ለውጥን በአንድ ጀንበር ካላደረግን ብለው ሲያደናብሩን ስንቶች ወደ ኋላ ጎተቱን መሰላችሁ? ትውልድ ቀርፆ በትውልድ ውስጥ የነገዋን እናት አገር ሰፋ አድርጎ ተመልካቹ ጠፋ። ‹‹ለነገሩ ማንቸስተርና አርሰናል የዘመኑ መላዕክት ሆነው ሌላ መመልከት ይቻል ኖሯል?›› ያለኝ ደላላ ጓደኛዬን አልረሳውም፡፡ ‹‹የዛሬን አያድርገውና በፊት የአርሰናል ደጋፊዎች ሲሸነፉ እሪ ብለው ያለቅሱ ነበር። ያውም በባላንጣቸው ማንቸስተር። ዛሬ ሲለምዱት እንኳን ለቅሶውን ቁጭቱንም ተውት፤›› ብሎኛል አንድ የማንቸስተር ደጋፊ ወዳጄ። ‹‹ሥራ እንዴት ነው?›› ብዬ ስጠይቀው ከልቡ አልሰማኝም መሰል፣ ‹‹ማንቼ ፕሪሚየር ሊጉን እየመራ ነው፤›› አለኝ፡፡ ወይ አገሬ!

አንዳንዴ የእኛን ነገር ሳስበው እንዴት አድርጌ መሰላችሁ? በአንድ ክንፍ ብቻ እንደሚበር አውሮፕላን ነው። በአጋጣሚም ይሁን በታሪክ በአንድ ክንፍ የበረረ አውሮፕላን ሰምታችኋል!? አዎ! ታዲያ ይኼ አጋጣሚና ታሪክ ለእኛም ደረሰን። እንዴት? ብትሉኝ ነገሮችን ሚዛናዊ አድርገን ከመጓዝ ፅንፈኛ ሆነንና ለሚመቸን ነገር ብቻ ማድላት ሥራችን ስለሆነ ነው። ምሳሌ ልስጥ መሰል? አዎ! ለምሳሌ የቁስ እንጂ የሐሳብ አልሆን ብለናል። ለሚታየው ነገር እንጂ ለማይታየው ዋጋ መስጠት እየተውን እንደመጣን እስኪ በእኔ ይሁንባችሁና ታዘቡ። ማንጠግቦሽ አንድ ማለዳ በሬዲዮ የሚተላለፈውን ማስታወቂያ እየሰማች አንበርብር ‹‹ትሰማለህ ጉዳችንን?›› አለችኝ። ‹‹ምን?›› ስላት  ‹‹አዲስ የፊልም ማሳያ ነው መሰል መጣ ተብሎ በአፍሪካ ብቸኛዋ አስመጪና ቀዳሚ አገር ሲባል? መዝናናቱስ ይሁን። ግን በሥልጣኔ ቀደምት ነን ባልንበት አፋችን ለመፍዘዝ መቅደማችንን ማወጃችን አያበሳጭም?›› ስትለኝ ነው ይኼ ስላችሁ የነበረው በአንድ ክንፍ የመብረር ነገር ወደ አዕምሮዬ የመጣው። ለባሻዬ ልጅ ማንጠግቦሽ ያለችውን እነግረዋለሁ፣ ‹‹አንዳንዴ እኮ ሚዲያዎቻችን የሚሠሩትን የሚያውቁ አይመስለኝም። ጐን ለጐን የሚባለውንና የማይባለውን ቢለዩ ጥሩ ይመስለኛል። አይደለም እንዴ?›› አለኝ፡፡ በማከልም፣ ‹‹የእያንዳንዳችን ትንሽ የሚባል ድርጊት ሕፃናትን በተዘዋዋሪ መተንኮሱ አይቀርም። መልዕክት ስናስተላልፍ ሕፃናትን እናስብ፤›› ብሎ ዝም አለ። ይኼ የአንደኝነት አባዜ የት እንደሚየደርሰን እንጃ፡፡ እኔ ደላላው አንበርብር ምንተስኖት የፈራሁት ነገር ቢኖር በመፈክር ብቻ አንደኛ ሆነን ይኼንንም ለዓለም እንዳናስተዋውቅና እንዳንዋረድ ነው፡፡

እስኪ ትንሽ ስለ ሥራ ደግሞ እናውራ። የቢዝነስ ሰው ሆኖ መክሰርን የማይፈራ ያለ አይመስለኝም። ቢሆንም ቢሆንም ከአደጋው ጋር እየተጋፈጡ ካልሠሩ ደግሞ የት ይደረሳል? ይኼን ሰሞን ስንቱ ግዥና ሽያጭ እየተፋረሰ በወጣሁበት አዙሮ ቤቴ አስገባኝ መሰላችሁ? ውዷን ማንጠግቦሽን እላችኋለሁ አንዳንዴ አልፋረስ ብሎ የፀናው የእኔና የማንጠግቦሽ ፍቅር ብቻ ይመስለኛል። ‹‹ማንጠግቦሽ?›› ስላት ‹‹እህ? ደግሞ ምን ሆንክ?›› ትለኛለች። ማንጠግቦሽ ዘንድ ‘አርቴፊሺያል’ ፈገግታ የሚባል ነገር ቦታ የለውም። ‹‹እንዲያው የእኔና ያንቺ ነገር አይገርምሽም ግን?›› ስላት፣ ‹‹ኤድያ አንተ ደግሞ ነገር መደጋገም ትወዳለህ፤›› ስትለኝ፣ ‹‹ይኼ የምን ነገር ነው አንቺ የፍቅር ወግ ነው እንጂ፤›› ስላት፣ ‹‹ኡኡቴ!›› ብላ ለዛ ባለው የኃፍረት ሳቅ ፍርስ ትላለች። ልቤ በስስት አብሯት ይፈርሳል። በተረፈ ውል የሚይዘው፣ ሊሻሻጥ የሚደራደረው፣ አከራይና ተከራዩ፣ ሰውና ቃሉ እየተፋረሰ አስቸግሯል። አንዳንዴ አገሪቷ በመልሶ መገንባት ውስጥ ያለች ‹‹ጥንታዊ ከተማ›› ትመስለኛለች። መፋረስ ሲበዛ እኮ ሰላም መደብዘዙ አይቀርም። ሰላም ከሌለ ምን አገር አለ? እንዴ ለእያንዳንዳችን ወጥተን ለመግባታችን ዋስትናው በስምምነትና በመቻቻል ላይ የተመሠረተ ሰላም ነው። ‘ሰላም ለሰው ልጆች ሁሉ’ ያለው ማን ነበር? ትራንስፎርሜሽኑም እኮ በመፋረስ አይሳካም። ‹‹ትራንስፎርሜሽኑን ለማሳካት የሚቻለው በዕቅድ ላይ የተመሠረተ ተግባር ሲከናወን ነው፤›› እያለ ሬዲዮኑ ሲናገር የሰሙት ባሻዬ፣ ‹‹መጀመርያ ራስህ መፈክር ከመደርደር ተላቀቅ፤›› ሲሉ ሳቄን መቆጣጠር አቃተኝ፡፡ 

እናማ ‹‹ሥራ ለሠሪው እሾህ ላጣሪው›› እንደሚባለው ሆኖ እንዲህ በሳምንት አንዴ ብቻ ያገናኘናል። ሠርቶ የሚያርፈውን ወይም አውርቶ የሚያርፈውን ግን ዕለተ እሑድ ትቁጠረው። በየቢሮው ተወዝፎ የሚውለውን፣ ሥራ ሳይሠራ የሚውለውን፣ ፌስቡክ ላይ ተጥዶ እንቅልፍ የሚይዘውን፣ ከገባበት እስከወጣበት ሰዓት ድረስ ስልክ ላይ የሚለጠፈውን፣ ወዘተ ስትታዘቡ አገሪቱ ህዳሴ ላይ ሳይሆን ፅሞና ላይ ያለች ይመስላችኋል፡፡ ትልቅ ግድብ የምትሠራ አይደለም የጭቃ ቤት የምትለስን አትመስልም፡፡ አገር መንደሩ ተደበላልቆ ደህናው ከብልሹው አልለይ ብሎ ስንታይ ያስፈራል፡፡ ቆይ ግን መንግሥት የሆነ ማጣሪያ ነገር ቢያዘጋጅ ጥሩ አይመስላችሁም? ኦኦ ረስቼው። ለካ እዚህ አገር ሥራ አላሠራ ያለው ይኼ አጣሪ ኮሚቴ የሚባል የተተበተበ ቢሮክራሲ ወላጅ አባት ነው። ትርፉ ድካም ነው። ግን እስከ መቼ አይጥ በበላው ዳዋ እየተመታ እንደምንዘልቅ አይገባኝም። ፍርደ ገምድልነት ስንቱን ትኩስ ነፍስ አቀዘቀዘው መሰላችሁ? ይኼንን መቼም እንደ እኔ ደላላ ሆናችሁ ዞር ዞር ስትሉ ነው የምታውቁት። በትኩስ ኃይሉ ለአገሩ፣ ለወገኑና ለራሱ የሚተጋውን ከአጥፊ ጋር አብሮ እየተወቃ ከሩጫው ጋብ ብሎ እናየዋለን። እኔ ደላላው አንበርብር በምዞርበት ቦታ ሁሉ የምታዘበው ላቡን ጠብ የሚያደርገው ሳይሆን የማያላግጠው ሲበለፅግ ነው፡፡ ኧረ በሕግ!

በነገራችን ላይ ሰሞኑን ጥሩ አቋም ላይ ያለ ዩሮ ትራከር አሻሽጬ ነበር። ታዲያ ጠቀም ያለ ረብጣ ቆጥሬያለሁ። ‹‹አንዳንዴ በጀቱ ከሰማይ ሲለቀቅ እኮ ከምድር ለመሰብሰብ ቀላል ነው ልጅ አንበርብር፤›› አሉኝ ባሻዬ አንዲት ኪሎ ሥጋ ገዝቼ ብወስድላቸው። ፈጣሪ እንደገና እንዲጎበኘኝ ምርቃታቸውን አዥጎደጎዱት። ለምን እንደሆነ አላውቅም ምርቃትና አድናቆት ረዘም ላለ ጊዜ ሲቆይ እፈራለሁ። ስንቱ በአድናቆትና በምርቃት ሲኩራራ እንዳይሆን ሲሆን ስላየሁ ነዋ። ስንቱን መሰላችሁ ይኼ ሥራዬና ዕድሜዬ የሚያሳየኝ። የባሻዬን ልጅ ሥጋቴን ብነግረው፣ ‹‹አዎ ልክ ነህ። ገዢው ፓርቲንም አሁን ያልከውን ነገር እሰጋለታለሁ፤›› አለኝ። ‹‹እንዴት?›› አልኩት ወሬውን እዚያ ላይ የማድረሱ ፍጥነት አስገርሞኝ። ‹‹አየህ ገዢው ፓርቲ በአሁኑ ሰዓት ሕዝብ ከእኔ ጋር ነው፤ ሕዝብ ያምነኛል፤ ይወደኛል ብሎ በእርግጠኝነት አምኗል። በዚህ ያልተረጋገጠ አድናቆት ታውሮ ማስተካከል ያለበትን ነገር እየረሳው ያለ ይመስላል። ሙስና፣ የመልካም አስተዳደር እጦት፣ የዲሞክራሲያዊና የሰብዓዊ መብት ፈተናዎች፣ ድህነት፣ የፍትሕ እጦት፣ ወዘተ ሕዝቡን የፊጥኝ ይዘውት የሕዝብ ድጋፍ አለኝ እያሉ መደስኮር ዋጋ ያስከፍላል፤›› አለኝ፡፡ ያለው ሁሉ ልክ ስለነበር አንገቴን እያወዛወዝኩ አዳመጥኩት፡፡ ‹‹አንበርብር›› ብሎ ስሜን ጠራው። ‹‹አቤት?›› አልኩት እንደገና፣ ‹‹ይኼ ዘመን በፍቅር እንጂ በኃይል የትም አይደረስበትም፤›› ሲለኝ መልዕክቱ በደንብ ገባኝ፡፡ የገባችሁ ይግባችሁ፣ ያልገባችሁ ልቦና ይስጣችሁ ከማለት ሌላ ምን ይባላል?

እንደተለመደው ወደ ግሮሰሪያችን ‘ዋን’ ‘ዋን’ ልንል ተጓዝን። እኔም እሱም ጥማችንን የሚቆርጠውን አዝዘን ጨዋታችንን አሜሪካ ላክነው። ‹‹ለመሆኑ ኦባማ በማሸነፋቸው ምን ተሰማህ?›› አልኩት። ‹‹‘እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው’ ሲባል አልሰማህም? ማንም ቢመረጥ ከብሔሪዊ ጥቅማችን ጋር የሚሄድ ፖሊሲ ካለው ይመቸኛል፤›› አለኝ። በዝምታ ትንሽ በየራሳችን ዓለም ሰጠምን። እንዲህ በፍጥነትና በቅልጥፍና ግልጽ የሆነ ምርጫ ለማድረግ ስንት ዓመት ይፈጅብን ይሆን? እያልን ራሳችንን አስጨነቅነው። ‹‹ለመሆኑ አንበርብር ኦባማ ካሸነፉ በኋላ የተናገሩትን ሰምተሃል?›› አለኝ። ‹‹በምን አባቴ የቋንቋ ችሎታ እሰማለሁ ብለህ ነው? አዳሜ የተሰባበረ እንግሊዝኛ ላያችን ላይ እየለቀቀብን የምንችለው እንኳ ይጠፋብን ጀመር፤›› ስለው ከት ብሎ ሳቀ። ሳቁን ሲያባራ፣ ‹‹ምን አሉ መሰለህ? ‘ዛሬ ዋናው ነገር ኦባማን ወይንም ሚት ሮምኒን መምረጣችሁ ሳይሆን በድምፃችሁ ልዩነት መፍጠራችሁ ነው’ ያሉት ንግግር ውስጤ ቀረ፤›› ካለኝ በኋላ ትንሽ አሰብ አድርጎ፣ ‹‹ሥልጣን የሕዝብነቱ ተረጋግጦ በድምፃችን ልዩነት ለማምጣት የዲሞክራሲ ጉዞ ምንጊዜም ወሳኝ ነው፤›› ሲለኝ ተቀበልኩት። ልዩነት በድምፅ ብቻ ይፈጠር ዘንድ ለአገሬ ተመኘሁ። በመፈክር ሳይሆን በተግባር የሚረጋገጥ ዲሞክራሲ ማን ይጠላል? ከመፈክር ይልቅ ዲሞክራሲ ናፈቀኝ፡፡ መልካም ሰንበት! 
http://www.ethiopianreporter.com/component/content/article/304-delalaw/8443-2012-11-10-09-07-38.html

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር