መንግሥት ሃይማኖታዊ መልዕክቶችን የሚከለክል ሕግ ለማውጣት እያሰበ ነው

በዮናስ አብይ

በአገሪቱ ውስጥ በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፉና ሃይማኖታዊ ግጭቶችን እየፈጠሩ ነው የሚባሉ ማናቸውም ሃይማኖታዊ መልዕክቶችን የሚያስተላልፉ ምስሎች፣ ጥቅሶች፣ ድምፅን የሚበክሉ የጐዳና ላይ ስብከቶችና መዝሙሮች፣ ከሕዝባዊ ቦታዎች የሚከለክል አዲስ ሕግ አውጥቶ በሥራ ላይ ለማዋል እየተንቀሳቀሰ መሆኑን መንግሥት አስታወቀ፡፡ ሃይማኖታዊ ጉዳዮች የሚመለከቱት የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር፣ ሃይማኖት ጥልቅና ጥንቃቄ የሚያሻው ጉዳይ በመሆኑ፣ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በጥልቀት እየመረመረው መሆኑንም ገልጿል፡፡ 

በፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ የሆኑት አቶ አበበ ወርቁ በተለይ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ መንግሥት በአሁኑ ጊዜ ሃይማኖታዊ መልዕክት ያላቸውን ይዘቶች በተመለከተ፣ የአምልኮ ሥርዓት ምን መምሰል እንዳለበትና የድምፅ ብክለትን ጨምሮ የሚፈጠሩ ችግሮችን ከሕዝባዊ ቦታ እንዴት ማራቅ እንደሚቻል፣ ሕግ እንደሚያስፈልግ ከምንጊዜውም በላይ እያሰበበትና እየተዘጋጀ ነው፡፡

“በማናቸውም አገልግሎት መስጫ ተቋማት እንደ ታክሲ፣ ሆቴሎች፣ ሕዝባዊ ተቋማትና አደባባዮች ላይ የሚለጠፉ ሃይማኖታዊ ነክ መልዕክቶችን፣ ሕዝብን ከሕዝብ፣ ሃይማኖትን ከሃይማኖት ሊያጋጩ የሚችሉ በኤሌክትሮኒክስ የሚተላለፉ መልዕክቶች በሙሉ በሕግ ተደንግገው የሚከለከሉበት ሥራ በመሠራት ላይ ነው፤” ብለዋል አቶ አበበ፡፡ 

“የሃይማኖት ጉዳይ ጠለቅ ያለ ነገር ስለሆነ ጠለቅ ያለ ሕግና ደንብ ያስፈልገዋል፡፡ ስለሆነም የአዋጁንና የደንቡን ይዘት እያዘጋጀን ለሚመለከታቸው አካላት እያሳየን ነው፡፡ የድምፅ ብክለትን በተመለከተ አዋጁና ደንቡ በማውጣት ሥርዓት ለማስያዝ እየተሠራ ነው፤” ሲሉ አስረድተዋል፡፡

ነገር ግን እስካሁን ድረስ ቃል በቃል የሚጠቀስ ዝርዝር ይዘት ያለው ረቂቅ ሕግ ወይም አዋጅ ገና እንዳልተዘጋጀ አቶ አበበ ለሪፖርተር አስታውቀዋል፡፡ 

“ለምሳሌ ታክሲዎችንና ሆቴሎችን ብናይ የሕዝብ ተቋማት እንደሆኑ ይታወቃል፡፡ አገልግሎታቸውም ለሁሉም የኅብረተሰብ ክፍሎች መሆኑ እየታወቀ በውስጣቸው የአንድን ሃይማኖት ፍላጐት ብቻ የሚያንፀባርቁ መልዕክቶች ይተላለፍባቸዋል፡፡ እነዚህ አገልግሎቶች የሕዝብ መጠቀሚያ እንጂ የማንም ሃይማኖት ተከታይ መጠቀሚያ ብቻ መሆን የለባቸውም፡፡ በእነዚህ ቦታዎች የሚለጠፉ መልዕክቶች የአንዱን ሃይማኖት ከፍ አድርገው የሌላውን ማንኳሰስ የሚታይባቸው ነው፡፡ በመሆኑም ከፈቃድ አሰጣጥ ጀምሮ ሕዝብን ከሕዝብ ሊያጋጩ በማይችል ሁኔታ አገልግሎት እንደሚሰጡ መታሰብ አለበት፤” ሲሉ አስረድተዋል፡፡ 
http://www.ethiopianreporter.com/news/293-news/7931-2012-10-03-05-49-47.html

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር