መድኃኒትና ንብረት የዘረፉ ክስ ተመሠረተባቸው



ፈንድ አቅርቦት ኤጀንሲ የሃዋሳ ቅርንጫፍ የጥበቃ ሠራተኛ የነበረው ግለሰብና ሌሎች ስድስት ግለሰቦች በመመሳጠር ከኤጀንሲው የመድኃኒት ማቆያ መጋዘን ውስጥ ከ1ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት መድኃኒት በመዝረፍ በከባድ የእምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል ተከሰሱ።
የፌዴራል የሥነ ምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በግለሰቦቹ ላይ የመሠረተው ክስ እንደሚያመለክተው የኤጀንሲው የጥበቃ ሠራተኛ የነበረ 1ኛ ተከሳሽ የመንግሥትን ንብረት እንዲጠብቅ የተሰጠውን ኃላፊነት ወደጎን በመተው ተገቢ ያልሆነ ጥቅም ለራሱ እና ለግብረ አበሮቹ ለማስገኘት በማሰብ ለሕዝብ አገልግሎት ይውሉ የነበሩትን መድኃኒቶች፣ ኬሚካሎች፣ የሕክምና መሣሪያዎች እንዲዘረፉ በማድረጉ ከባድ የእምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል ፈጽሟል።
የኤጀንሲው ሠራተኞች ያልሆኑት ከ2ኛ እስከ 6ኛ ያሉ ተከሳሾች ከ1ኛ ተከሳሽ ጋር ተመሳጥረው መድኃኒት የተከማቸበትን መጋዘን ቁልፍ በመስበር መድኃኒቱ የሚጫንበትን ተሽከርካሪ በማዘጋጀት መድኃኒቱን ከመጋዘን አውጥተው በመጫን እንዲሁም መድኃኒቱ የሚራገፍበትን ቦታ በማመቻቸት በወንጀሉ ድርጊት ሙሉ ተሳታፊና በወንጀሉ የተገኘውን ውጤት ተካፋይ መሆናቸውን የክስ መዝገቡ ያስረዳል።
7ኛ ተከሳሽ የሆነው የኤጀንሲው የጥበቃ ተከሳሽ ዘረፋው በተፈጸመበት ዕለት ተረኝነቱን ሳይጠብቅና የሙያ ግዴታውን በአግባቡ ሳይፈጽም ሌሊቱን ጥበቃ ላይ የነበረ በማስመሰል በሰዓት መቆጣጠሪያ ላይ በመፈረሙ በፈጸመው የሥራ ኃላፊነትን ባለመወጣት የሙስና ወንጀል ተከስሷል።
በአጠቃላይ ሁሉም ተከሳሾች በግብረአበርነት በፈጸሙት የሙስና ወንጀል ግምቱ 1ነጥብ7ሚሊዮን ብር የሚያወጣ መድኃኒት ኬሚካሎች ሰፕላይስ እና የሕክምና መሣሪያዎችን በመዝረፋቸው ኮሚሽኑ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 1ኛ ወንጀል ችሎት መጋቢት 16 ቀን 2004 ዓ.ም ክስ መስርቶባቸዋል።
ፍርድ ቤቱም የክስ ሂደቱን ከመረመረ በኋላ መጋቢት 28 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት 7ኛ ተከሳሽ ጥፋተኛ የተባለ ሲሆን፤ ሌሎቹ ተከሳሾች ምስክር እንዲያሰሙ ፍርድ ቤቱ ለሚያዝያ 30 ቀን 2004 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል። 

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር