የኢትዮጵያ ዋነኛ ቡና ገዥዎች ለመንግሥት ተቃውሟቸውን አሰሙ


-    ቡና ላኪዎች ለጠቅላይ ሚኒስትር መለስ አቤቱታ ሊያቀርቡ ነው

የኢትዮጵያ ቡና ገዥ ከሆኑት መካከል በዋነኝነት የሚጠቀሱት የስዊዘርላድንና የጀርመን ኩባንያዎች በማኅበሮቻቸው በኩል ለኢትዮጵያ ኤምባሲዎች፣ ለውጭ ጉዳይና ለንግድ ሚኒስቴር የተቃውሞ ደብዳቤ መጻፋቸው ታወቀ፡፡
የእንግሊዝ ኩባንያዎችን ጨምሮ አሥር ታዋቂ የኢትዮጵያን ቡና የሚገዙ ማኅበራት በብትን እንደማይገዙ ያሳወቁ ሲሆን፣ ፊታቸውን ወደ ሌሎች ቡና ሻጮች ማዞራቸውም እየተነገረ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት የኮሎምቢያና የኬንያ ቡና ላኪዎች የአረቢካ ቡና ገበያን ሊቆጣጠሩት እንደቻሉ፣ በዚህ ሳምንት ብቻ ኢትዮጵያ ልትሸጥ የሚገባት 30 ሺሕ ቶን የሚገመት ቡና ሳይሸጥ መቅረቱን ምንጮች ይናገራሉ፡፡

ንግድ ሚኒስቴር ከህዳር 1 ቀን 2004 ዓ.ም. ጀምሮ ያወጣው መመርያ ቡና ገዥዎች እንደተቃወሙትና በኮንቴይነር በብትን እንዲላክልን አንፈልግም ብለውናል በማለት የኢትዮጵያ ቡና ላኪዎች ያቀረቡትን ሐሳብ ሚኒስቴሩ ሊቀበለው ባለመቻሉ፣ ለጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የአቤቱታ ደብዳቤ ለማቅረብ መገደዳቸውንና በነገው ዕለትም ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤት እንደሚያስገቡ ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ ከህዳር 1 ቀን ጀምሮ ሁሉም ላኪዎች ቡና በብትን በኮንቴይነር እንዲልኩ የወጣውን መመርያ ቡና ገዥዎች እንዳልተቀበሉት፣ በጆንያ የማይላክላቸው ከሆነ ከኢትዮጵያ ቡና አንገዛም ማለታቸውን ለሚኒስቴሩ ቢያሳውቁም፣ ሳይቀበላቸው በመቅረቱ አሳምናችሁ በብትን እንዲገዙ አድርጉ በማለት ኃላፊነቱን ጥሎባቸዋል፡፡

ከፍተኛ የታጠበ ቡና በጥርና በካቲት ወራት ተጓጉዞ ለዓለም ገበያ እንዲቀርብ አሁን ውል ሊፈጸም ይገባ እንደነበር የሚገልጹት ቡና ላኪዎች፣ አሁን በሚታየው የዓለም የኢኮኖሚ መዋዠቅ የቡና ኤክስፖርት መቀነሱን ይናገራሉ፡፡ ገዥዎች እምቢ ከማለታቸው ጋር ተያይዞ ቡናው በመጠንና በገቢ ደረጃ በከፍተኛ ሁኔታ ማሽቆልቆሉን፣ ወደፊትም ከዚህ የበለጠ ሊቀንስ እንደሚችልና የአገሪቱን የወጪ ንግድ ገቢ እጅግ የሚጎዳ አሳሳቢ ችግር መፈጠሩን ገልጸዋል፡፡

ሆኖም አንዳንድ ላኪዎች በብትን እየላኩ እንደሚገኙ፣ ጥቂቶችም መመርያውን ወደ ጎን በማለት በጆንያ እየላኩ መሆኑን፣ ይህን በማድረጋቸው የሚደርስባቸው ነገር ካለም ‹‹የሚመጣውን ለመቀበል ተዘጋጅተናል›› የሚሉ አልጠፉም፡፡

‹‹የኢትዮጵያ ቡና ራስን በራስ የማጥፋት ዕርምጃ ተወስዶበታል፤›› ሲሉ አንዳንድ  የቡና ላኪዎች የገለጹ ሲሆን፣ የንግድ ሚኒስቴር ያወጣውን መመርያ አስመልክቶ የተቃውሞ ፊርማ እየተሰባሰበ እንደሚገኝም ለማወቅ ተችሏል፡፡

Comments

Popular posts from this blog

ፓርቲው ምርጫ ቦርድ ከተፅዕኖ ነፃ ሳይሆን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ተቃወመ

የሐዋሳ ሐይቅ ትሩፋት

በሲዳማ ክልል የትግራይ ተወላጆች ምክክር